Wednesday, June 19, 2019

ሰኔ 13 እና 14


አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን

<3 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it)

ሰኔ 13 እና 14

+ ከታላቁ ጻድቅ ከቅዱስ ኤጲፋንዮስ ጋር በታናሽነቱ በአባ ኤስድሮስ ገዳም መንኩሶ በታላቅ ተጋድሎ የኖረው የኢየሩሳሌሙ ቅዱስ አባ ዮሐንስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ዮሐንስም በሹመቱ ሳለ ገንዘብን በመውደድ ጌታችንን ቢያሳዝነው ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዐይኖቹን አሳውሮ በኋላም እንደገና መልሶ አንድ ዐይኑን በማብራት በተአምራት ወደ ንስሓ የመለሰው ነው፡፡

+ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት የሄኖስ ልጅ ቃይናን የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ቃይናንም 170 ዓመት ኖሮ መላልዔልን ወደለደው፡፡ መላልዔልንም ከወለደው በኋላ 740 ዓመት ኖረ፡፡ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ፡፡ የቃይናንም መላ ዘመኑ 910 ዓመት ሲሆነው በዚህች ዕለት ዐረፈ፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡

+ + + + +
አቡነ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም፡- ይኸውም ቅዱስ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ሲሆን ከታላቁ ጻድቅ ከአቡነ ኤጲፋንዮስ ጋር በታናሽነቱ በአባ ኤስድሮስ ገዳም መንኩሶ በታላቅ ተጋድሎ ይኖር የነበረ ነው፡፡ የእርሱም ደግነቱ፣ ትሩፋቱ፣ ቅድስናውና ታላቅ ተጋድሎው በቦታው ሁሉ ተሰማ፡፡ ከዚህም በኋላ አቡነ ኤጲፋንዮስን በቆጵሮስ ሀገር ኤጲስቆጶስ አድርገው ሲሾሙት አቡነ ዮሐንስን ደግሞ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አድገው ሾሙት፡፡

አቡነ ዮሐንስም በሹመት በነበረ ጊዜ ሰይጣን በገንዘብ ፍቅርና በዚህ ዓለም ክብር አሳተው፡፡ የቀድሞ ግብሩን እረስቶ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች የማይራራ ሆነና ቁራሽ እንጀራን እንኳን የማይሰጣቸው ሆነ፡፡ ይልቁንም ለራሱ ብዙ ገንዘብ ሰብስቦ ለማዕዱ የሚመገብበትን የወርቅና የብር ሣህን አሠራና በድሎት የሚኖር ሆነ፡፡
አቡነ ኤጲፋንዮስም ይህን በሰማ ጊዜ የአቡነ ዮሐንስን የቀድሞውን ተጋድሎውንና የዓለም መናኒነቱን፣ ፍቅሩንም አስታውሶ እጅግ አዘነ፡፡ እርሱም ከመጀመሪያው ጊዜ ጀምሮ መንፈሳዊ ወንድሙና ወዳጁ ነበር፡፡ ስለዚህም ብፁዕ ኤጲፋንዮስ ከቆጵሮስ ተነሥቶ ወደ ኢየሩሰሌም ወደ አቡነ ዮሐንስ መጣ፡፡ ከስሕተቱ ይመልሰውና በጥበብ ያድነው ዘንድ አስቦ የጌታችን መቃብር ባለበት ቤተ መቅደስ ለመስገድ እንደመጣ ነገረው፡፡ በተገናኙም ጊዜ አቡነ ዮሐንስ አቡነ ኤጲፋንዮስን ወደ ቤቱ አስገብቶ ማዕድ አዘጋጀለት፡፡ በማዕዱም ላይ በወርቅና በብር ያሠራቸውን ሣህኖቹን አስቀመጠ፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስ ከእርሱ ዘንድ ወጥቶ ወደ አንዱ ገዳም ሄዶ አደረ፡፡ ወደ አቡነ ዮሐንስ እንዲህ ብሎ መልእክት ላከ፡- ‹‹ወንድሜ ሆይ ከቆጵሮስ ሀገር ሽማግሎችና የሕዝቡ መምህራን ወደ እኔ መጥተዋልና በእነርሱ ፊት ታከብረኝ ዘንድ ከወርቅና ከብር ያሠራሃቸውን የማዕድ ዕቃዎችህን ይመገቡባቸው ዘንድ እንድትክልኝ›› ብሎ መልእክት ላከበት፡፡ አቡነ ዮሐንስም የከበሩ ዕቃዎቹን ላከለት፡፡

አቡነ ኤጲፋንዮስም የከበሩ የማዕድ ዕቃዎቹን ወስዶ ሸጣቸውና ገንዘቡን ሁሉ ለድኆችና ለምስኪኖች መጸወተው፡፡ ሁለቱም በተገናኙ ጊዜ አቡነ ዮሐንስ ‹‹የላኩልህን የከበሩ የማዕድ ዕቃዎቼን መልስልኝ›› አለው፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስም ‹‹እሺ›› አለው፡፡ በሌላ ጊዜም እስከ ሦስት ጊዜ ደጋግሞ ጠየቀው፡፡ በአንዲት ዕለትም የጌታችን መቃብር ካለበት ቤተ መቅደስ ሲወጣ አግኝቶ ያዘውና ‹‹ንብረቶቼን ካልሰጠኸኝ›› ብሎ ያዘው፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስም ወደ ጌታችን ቢጸልይ የአቡነ ዮሐንስ ሁለት ዐይኖቹ ወዲያው ታወሩ፡፡ እርሱም እጅግ ደንግጦ ይቅር ይለው ዘንድ አቡነ ኤጲፋንዮስን ለመነው፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስም የእውነት መጸጸቱን አይቶ አንዲቱን ዐይኑን አበራለት፡፡ እንዲህም አለው፡- ‹‹ነፍስህን ታስብ ዘንድ አንዲቷን ዐይንህን ዕውር እንደሆነች ትቀር ዘንድ ጌታችን ትቶልሃል›› ብሎ ገሠጸው፡፡ ‹‹እነሆ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የቀድሞ ድካምህንና ተጋድሎን አስቦ እራርቶልሃልና ከስሕተትህም አድኖሃል›› አለው፡፡
ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ አቡነ ዮሐንስ ከእንቅልፉ እንደነቃ ሆኖ የቀድሞ መልካም ሥራውንም መሥራት ጀመረ፡፡ ምንም ሳያስቀር ጥሪቱን ሁሉ አውጥቶ በመሸጥ መጸወተው፡፡ ተጋድሎውንም እንደበፊቱ በጽኑ ጀመረ፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን የመፈወስ ሀብት ሰጠው፡፡ ብዙ አስገራሚ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ብዙ ካገለገለና ጌታችንም ታላቅ ቃልኪዳን ከገባለት በኋላ በዚህች ዕለት በሰላም ዐረፈ፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡
+ + + + +

ሰኔ 14-የከበሩ ቅዱሳን አክራ፣ ዮሐንስ፣ አብጥልማ እና ፊሊጶስ በሰማዕትነት ዐረፉ፡፡ እነዚህም አራት የከበሩ ቅዱሳን በጌታችን ስም ሰማዕት ይሆኑ ዘንድ በምክር ተስማሙ፡፡ አክራና ፊሊጶስ ወንድማማቾች ሲሆኑ እነርሱም የከበሩ ባለጸጎች ናቸው፡፡ ዮሐንስና አብጥልማ ግን የከበሩ ቀሳውስት ናቸው፡፡ አራቱም ሰማዕት ይሆኑ ዘንድ ከተስማሙ በኋላ ቀርጥስ ወደሚባል አገር ሄደው በከሃዲው መኮንንነ ፊት ቆመው የጌታችንን አምላክነት መሰከሩ፡፡ መኮንኑም በቀስት እንዲነድፏቸው አዘዘ፡፡ ነገር ግን ቀስቶቹ ሳይነኳቸው ቀሩ፡፡
ዳግመኛም በእቶን እሳት ውስጥ ጨመሯቸው፣ ጌታችንም መልአኩን ልኮ አዳናቸው፡፡ ከዚህም በኋላ በፈረሶች ጅራት ላይ አሥረው ከቀርጥስ እስከ ይምንሑር አገር ድረስ ጎተቷቸው፡፡ አሁንም ጌታችን ፈውሳቸውና ምንም ጉዳት እንዳላገኛቸው ሆኑ፡፡ ከዚህም በኋላ መኮንኑ ማሠቃየት በሰለቸው ጊዜ ራስ ራሶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘ፡፡ እንደትእዛዙም ከይምንሑር ከተማ አውጥተው በሰይፍ አንገታቸውን ቆረጧቸውና የሰማዕትነታቸው ፍጻሜ ሆነ፡፡ እነርሱም የክብርን አክሊል ተቀዳጁ፡፡
ፃ ከምትባል አገር ሰዎቸ መጥተው የቅዱስ አክራን ሥጋ ወሰዱ፡፡ ከይምንሑር ከተማ የመጡ ሰዎች ደግሞ የቅዱስ ፊሊጶስን፣ የቅዱስ ዮሐንስንና የቅዱስ አብጥልማ ሥጋቸውን ወስደው ለሁሉም የተዋቡ አብያተ ክርስቲያናትን ሠርተውላቸው የሰማዕታትን ሥጋቸውን በውስጣቸው አኖሩ፡፡ ከቅዱሳኑም ሥጋ አስገራሚ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/tewadhdohaimanotachin
https://ttewahdo.blogspot.com/

Sene 12- Enkwan Aderesachu

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን






ሰኔ 12-ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚበር ንሥረ አርያም የሚባል ውዳሴው እንደ ማር የጣፈጠ ንዑድ ክቡር የሆነ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል አፎምያን ያዳነበት ዕለት ነው፡፡ ዳገመኛም ይኽች ዕለት የባሕራንን የሞት ደብዳቤ ቀዶ እርሱን ለታላቅ ክብር ያበቃባት ዕለት ናት፡፡


+ ዳግመኛም ቅዱስ እለእስክንድሮስ አንድን ቤተ ጣዖት አፍርሶ ከቦታው ላይ ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ታቦተ ሚካኤልን አግብቶ በዓሉን በደስታ በሐሴት ያከበረባት ዕለት ናት፡፡


+ ቅዱስ ገብርኤል ወደ ሰማይ ነጥቆ ወስዶ ሰባቱ ሰማያትን ካያሳየውና በጌታችን ፊት አቅርቦት ካስባረከው በኋላ ጌታችንም በቅዱስ ቃሉ ‹‹ሕዝቦቼ የመከራና የሥቃዬን ቦታ ለማየት ኢየሩሳሌም በመሄድ በመንገድ እየቀሩ ስለሆነ አሁን ግን አንተ በሀገረ ሮሀ ኢየሩሳሌምን ትሠራለህ›› በማለት የቤተ መቅደሶቹን አሠራር በዝርዝር የነገረው ጻድቁ ንጉሥ ቅዱስ ላሊበላ ዕረፍቱ ነው፡፡


+ ወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ የክርስትና ጥምቀትን ያጠመቀው በኋላም ዲቁናና ቅስና የሾመው የከበረ አባ ዮስጦስ ዕረፍቱ ነው፡፡ እርሱም በቅዱስ ማርቆስ መንበር ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት 6ኛ ሆነ፡፡


+ + + + +


ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ሚ-መኑ' ካ-ከመ' ኤል- አምላክ ማለት ሲሆን በአንድነት ሲነበብ መኑ ከመ አምላክ (እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው) ማለት ነው፡፡ አንድም ለእግዚአብሔር አሸናፊ ድል አድራጊ የቸርነትና የርህራሄ መገኛ መዝገብ ማለት ነው፡፡


ይህ ታላቅ መልአክ ዮሐንስ ወንጌላዊ በራዕዩ ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙትን ሰባቱን መላእክት አየሁ›› ብሎ ከተናገረላቸው መላእክት ውስጥ የሚመደብ ሲሆን የሰባቱም ሊቃነ መላእክት አለቃ እንዲሆን እግዚአብሔር መርጦ ሹሞታል፡፡ ይህ ታላቅ መልአክ ያደረጋቸው የሠራቸው እጅግ ብዙ የሆኑ ተአምራት አሉት፡፡ ስለዚህ ስለ ታላቁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ክብር፤ ጠባቂነትና አማላጅነት ከአባቶቻቸው የተማሩትን በኑሮአቸው ያዩትን አባቶቻችን ጽፈዋል፡፡ ስለ ቅዱስ ሚካኤል ከጻፉት አባቶች መካከል የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያክል፡- ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ኤዎስጣቴዎስ ዘአንፆኪያ፣ ቅዱስ መቃርዮስ፣ ቅዱስ ያሬድ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እና የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አባዲማቴዎስ ናቸው፡፡ እኛም የአባቶቻችንን አንደበት አንደበታችን አድርገን በኅዳር 12 ክቡር ገናና የሆነ ቅዱስ ሚካኤል ካደረጋቸውና ከሠራቸው ብዙ ተአምራት ውስጥ የተወሰኑትን በመልአኩ ተረዳኢነት እንዲህ ብለን እንናገራለን አንጽፋለን፡፡


ጥንተ ነገሩ እንዲህ ነው፡- ንግስት ክሌዎፓትራ ‹‹ሳተርን›› ለሚባለው ጣዖት የሠራችው ቤተ ጣዖት በእስክንድርያ ነበር፡፡ ይህ ቤተ ጣዖት እስከ እስክንድርያው ፓትርያርክ እለ እስክንድሮስ /312 - 326/ ዘመን ድረስ ነበር፡፡ እለ እስክንድሮስ ሊያጠፋው ሲነሣ ሕዝቡ ከልቡ ገና የአምልኮ ጣዖት ስላልጣፋ "18 ፓትርያርኮች ያልነኩትን አንተ ለምን ታፈርስብናለህ?" ብለው ተቃወሙት፡፡ እለ እስክንድሮስም ሕዝቡን መክሮና አስተምሮ የሳተርን በዓል ይውልበት በነበረው ዕለት የቅዱስ ሚካኤልን በዓል እንዲያከብሩ አውጆ ቤተ ጣዖቱንም በቅዱስ ሚካኤል ስም ሰይሞ ቤተክርስቲያን አደረገው፡፡
ሕዝቡ በየዓመቱ መሥዋዕት እየሠው ተረፈ መሥዋዕቱን እየተመገቡ እየዘፈኑ እያጨበጨቡ ያከብሩ ነበር፡፡ ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ቁስጠንጢኖስ "አብያተ ጣዖታት ይዘጉ አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ" ብሎ ካወጀ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት እለ እስክንድሮስ ቤተ ጣዖቱን አፍርሶ ከቦታው ላይ ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ታቦተ ሚካኤልን አግብቶ በዓሉን በደስታ በሐሴት አሳለፉት፡፡ እለ እስክንድሮስም ሕዝቡን የጣዖቱን በዓል ተው "ይህን የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል አክብሩ" ብሎ በየዓመቱ በዚህ ቀን በዓል እንዲሆን ሥርዓት ሠራላቸው፡፡ ይህንንም የቅዱስ ሚካኤልን በዓል ከሚያከብሩ ምእመናንን አንዱ የባሕራን አባት ነበር፡፡

እርሱም እግዚአብሔርን እጅግ አድርጐ የሚፈራ ወር በገባ በየዐሥራ ሁለቱ ቀን የቅዱስ ሚካኤልን ዝክሩን የሚዘክርና ይልቁንም በኅዳር ዓሥራ ሁለትና በሰኔ ዓሥራ ሁለት ቀን በታላቅ ክብር የሚያከብር አንድ ሰው ነበር። ለዚህ እግዚአብሔርን ለሚፈራ ሰውም ርኅራኄ የሌለው በእርሱም ላይ ጥላቻ ያደረበት አንድ በለጸጋ ጐረቤት ነበረው፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል በሚያከብርበት ጊዜ ሁሉ ይዘብትበት ይሳለቅበት ነበር። ይህ እግዚአብሔርን ለሚፈራ ሰውዬ በዚህ ዓይነት በጐ ሥራ ብዙ ጊዜ ከኖረ በኋላ ከዚህ ዓለም ድካም ያርፍ ዘንድ የሞቱ ጊዜ ቀረበ። ሚስቱንም ጠርቶ "በጐ ስራ ከመሥራት ለድኃ ከመመጽወት ቸል አትበይ የቅዱስ ሚካኤልንም በዓል በየወሩ ከማክበር አትቦዝኝ ይልቁንም በኅዳር ዓሥራ ሁለትና በሰኔ ዓሥራ ሁለት ቀን ከፍ ባለ ሥነ ሥርዓት እንድታከብሪ አደራ እልሻለው" አላት፡፡ በሚሞትበትም ጊዜ ሚስቱ ፀንሳ ነበር። ይህም ደገኛ ሰው በሰላም ዐረፈና ፍጹም መንግሥተ ሰማያትን ወረሰ። 

ከዚህም በኋላ ሚስቱ የመውለጃዋ ጊዜ ተቃርቦ ነበርና ምጥ ይዟት በታላቅ ጭንቅ ላይ እንዳለች "አንተ የእግዚአብሔር መልአክ ሆይ በእኔ ላይ ይቅርታን አውርድ ከዝህ ከደረሰብኝም ጭንቅ ይገላግለኝ ዘንድ ስለኔ እግዚአብሔርን ለምንልኝ አንተ ከእግዚአብሔር ዘንድ ታላቅ ባለሟልነት ተሰጥቶሃልና" እያለች ለመነች። ይህንንም በምትልበት ጊዜ ያለችበት ቤት በብርሃን ተመላ ከጭንቋም ዳነችና መልኩ በጣም ያማረ ልጅ ወለደች። የእግዚአብሔር መልእክተኛ ቅዱስ ሚካኤልም ከሰማይ ወርዶ ያን ሕፃን ባረከውና "ቸርነት ርኅራኄ የሌለውን የዚህን ባለጸጋ ገንዘብና ሀብት እርሻውንም ሁሉ ይህ ሕፃን እንዲወርስ እግዚአብሔር አዟል" አለ። ያን ጊዜ ያ ባለጸጋ በሴትዮዋ ቤት መስኮት አጠገብ ሆኖ ሁኔታውን ሁሉ ይመለከት ነበርና ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ልቡ በታላቅ ኅዘን ተነካ፤ ሕፃኑንም የሚገድልበትን ምክንያት ይፈልግ ጀመር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር በቅዱስ ሚካኤል ጸሎት ብላቴናውን ከክፉ ነገር ሁሉ ይጠብቀው ነበር።

 ብላቴናውም ዓሥር ዓመት በሆነው ጊዜ እናቱ በጣም ችግር ፀናባት፡፡ በዚህን ጊዜ እምነት የጐደለው ያ ባለጸጋ "አንቺ ችግረኛ ስለሆንሽ ይላከኝ ያገለግለኝ ዘንድ ልጅሽን ስጭኝና ምግቡንና ልብሱን ምንም ሳላጐድል ተንከባክቤ አኖረዋለው ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለው" አላት። ይህንንም ባላት ጊዜ ስለ ችግሯ በጣም በመደሰት ልጅዋን ሰጠችውና ሃያውን ወቄት ወርቅ ተቀበለች፡፡ ብላቴናውንም በወሰደ ጊዜ እንግዲህ ሃሳቤ ሁሉ ዛሬ ተፈጸመልኝ እያለ በጣም ደስታ ተሰማው፡፡ ከዚህ በኋላ በልጅ ቁመት ልክ ሳጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሣጥኑ ውስጥ አግብቶ በላዩ ላይ ቆለፈበትና ሣጥኑን ወስዶ ከባሕር ጨመረው፤ እንዲሁም የሣጥኑን ቁልፍ መክፈቻ አብሮ ወረወረው። ነገር ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ያ ሣጥን ሳይሰጥም በባሕሩ ላይ እየተንሳፈፈ ከዚያች አገር ርቃ ወደምትገኝ የባሕር ወደብ ደረሰ።
በባሕሩ አካባቢ በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ያንን ሣጥን ባየው ጊዜ ከባሕሩ አወጣውና ወደ ቤቱ ወሰደው። እቤቱም በደረሰ ጊዜ "ይህን ሣጥን በምን እከፍተዋለሁ?" እያለ ሲያወጣ ሲያወርድ ተመልሶ ወደ ባሕሩ ይሄድ ዘንድ እግዚአብሔር አሳሰበው፤ በሄደም ጊዜ አንድ ዓሣ የሚያጠምድ ሰው አገኘና ዓሣ አጥማጁን "በኔ ስም መረብህን ወደ በሕር ጣልና የተሠገረው ዓሣ ለኔ ይሆናል ዋጋውን ግን እከፍልሃለው" አለው፡፡ ዓሣ አሥጋሪውም እንደ ተነጋገሩት መረብን ከባሕር ቢጥል ታላቅ ዓሣ ተያዘና ለሰውየው ሰጥቶት ዋጋውን ተቀበለ። እሱም ያንን ዓሣ ከቤተሰቦቹ ጋር ጠብሶ ይበላ ዘንድ በችኮላ ወደ ቤቱ ሄደና ያሣውን ሆድ ቢሰነጥቀው የዚያን የሣጥን ቁልፍ መክፈቻ አገኘ፡፡ በዚያን ጊዜ ይህ መክፈቻ የዚህ ሣጥን ቁልፍ መክፈቻ መሆን አለበት ሲል አሰበና ቁልፉን ለመክፈት ቢሞክር ወለል ብሎ ተከፈተ። በዚህም እየተደነቀ ሳለ ሣጥኑን ቢከፍተው ያ ባለ ፀጋ ሊገድለው ያሰበውን ሕፃን በሣጥኑ ውስጥ አገኘው። ባየውም ጊዜ እጅግ ተደስቶ በባሕር ውስጥ ስላገኘው ስሙን "ባሕራን" ብሎ ሰየመውና እንደ ልጁ አድርጐ ይንከባከበው ዘንድ ወሰነ፡፡
ከባሕራን ሀገር የበግ ጠባቂው አገር የዓሥር ቀን ጐዳና የሚያስኬድ ርቀት ነበረው። ከብዙ ዓመታት በኋላ ያ ባለ ጸጋ ሰው ለንግድ ከሀገሩ ወጣ፡፡ በጉዞውም ላይ ሳለ ፀሐይ ስትገባ ከዚያ የበግ ጠባቂው ዘንድ ደረሰ። በግ ጠባቂውንም "ወንድሜ ሆይ ባንተ ዘንድ የማድርበት ቢኖር ታሳድረኝ ዘንድ እለምንሃለው፣ ኪራዩንም እከፍልሃለው" ብሎ ጠየቀውና ያ በግ ጠባቂ ወደ ቤቱ አስገባው። ባለጸጋውም ገብቶ ጥቂት ካረፈ በኋላ በግ ጠባቂው ያን ብላቴና ባሕራን ብሎ ሲጠራው በሰማ ጊዜ "ልጅህ ነውን?" ብሎ ጠየቀው። በግ ጠባቂውም "አዎን ይህ አሁን ጐልማሳ ሆኖ የምታየው ወጣት ገና ሕፃን ሆኖ ሳለ በሣጥን ተከቶ ከባሕር ውስጥ ተጥሎ አግኝቼው ወስጄ አሳድጌዋለሁና ልጄ ነው" አለው። ባለጸጋውም በባሕር ውስጥ የጣለው ሕፃን መሆኑንም ስላወቀ ይህንን ነገር በሰማ ጊዜ ፈጽሞ ደነገጠ፤ ይገድለውም ዘንድ ፈለገ፡፡
በበነጋውም መንገዱን ለመሄድ ሲዘጋጅ ልዩ ልዩ ምክንያት (ሰይጣናዊ ሃሳብ) በመፍጠር በግ ጠባቂውን "ወንድሜ ሆይ አንድ የማስቸግርህ ጉዳይ አለኝ ይኸውም በቤቴ የረሳሁት ነገር ስላለ ዕገሊት ወደ ምትባል ሀገር ሄዶ መልእክት ያደርስልኝ ዘንድ ይህን ብላቴና እንድትሰጠኝ ነው የድካሙንም ዋጋ ሃያ ወቄት ወርቅ እከፍላለሁ" አለው።
ያም በግ ጠባቂ ስለ ወርቁ ስጦታ ደስ በመሰኘት ያን ጐልማሳ ጠርቶ "ልጄ ባሕራን ሆይ ይህ ክቡር ሰው ለሥራ ጉዳይ ወደ ቤቱ ሊልክህ ይፈልጋልና መልእክቱን አድርስለት እግዚአብሔር በሰላም ያግባህ" ሲል ጠየቀው፡፡ ልጁም "እሺ መልካም ነው አባቴ ሆይ ያዘዝከኝን ሁሉ ለመፈጸም ዝግጁ ነኝ" አለው። ከዚህም በኋላ ያ ባለጸጋ "ይህችን የመልእክት ደብዳቤ ይዞ ወደ አንተ የመጣውን ስሙ ባሕራን የተባለውን መልእክቷ በደረሰችህ ጊዜ ፈጥነህ ግደለው ገድለህም ሬሣውን ከጉድጓድ ጣለው እኔ በሰላም ተመልሼ እስክመጣ ድረስ ማንም ማን ይህን ምሥጢር አይወቅ" የሚል ጽሑፍ ለሹሙ ጽፎ አዘጋጀ፡፡ እንዲሁም በሹሙና በእርሱ መካከል የሚተዋወቁበትን ማኅተም በደብዳቤው ላይ አትሞ ለባሕራን ሰጠው፡፡ ለመንገዱም የሚሆነው ስንቅ ሰጥቶ ላከው።

ባሕራንም መልእክቱን ለማድረስ ዘጠኝ ቀን ተጉዞ የአንድ ቀን ጎዳና ሲቀረው እነሆ ክቡር የሚሆን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በንጉስ ጭፍራ አምሳል በፈረስ ተቀምጦ ወደሱ ደረሰና ወዴት እንደሚሄድ ጠየቀው፡፡
ባሕራንም "ከአንድ ባለጸጋ ሰው የተጻፈ ደብዳቤ ይዤ እርሱን ለማድረስ ዕገሊት ወደምትባል አገር እሄዳለሁ" አለው። ንዑድ ክቡር የሚሆን ቅዱስ ሚካኤልም "እስኪ የመልእክቱን ደብዳቤ አሳየኝ?" አለው፡፡ ባሕራንም "ጌታዬ ለማንም አታሳይ ብሎኛል" አለው፡፡ መልአኩም "እሺ ያም ባይሆን እንደተጠቀለለ አሳየኝ" አለው፡፡ ባሕራንም አሳየው፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም በሞቱ ደብዳቤ ላይ እፍ ቢልበት የሞቱን ትእዛዝ አጥፍቶ የሕይወት ትዕዛዝ ጽፎበታል፡፡ በደብዳቤው ላይ የተጻፈውን የሞት መልእክት ደምስሶ "ከእኔ ከባለጸጋ ዕገሌ የተጻፈ" ይልና "ይህን መልእክት ይዞ ለመጣሰው ዕገሊት የምት ባለዋን ልጄን አጋቡት (ዳሩለት) በዱር የተሰማራውን ከብቴን በቤት ያለውን ሀብቴን በጠቅላላው የሚንቀሳቀስና የማይንቀሳቀስ ንብረቴን በሙሉ አውርሼዋለሁና እኔ እስክመጣ ድረስ አትጠብቁ በሄድኩበት ሀገር የምቆይበት ጉዳይ አለኝና፤ በቤቴና በንብረቴ ላይ ሙሉ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና የወደደውን ያደርግ ዘንድ አትከልክሉት ስለዚህም በእኔና በአንተ መካከል የምንተዋወቅበትን ምልክት አድርጌበታለሁ" የሚል ጽሑፍ ጽፎ ሰጠውና "እንግዲህ ወደ ባለጸጋው ቤት ሂድና ይህን መልእክት አድርስ ነገሩ እንዳይገለጽብህ ከእኔ ጋር መገናኘታችንንና የመልእክቱን ጽሑፍ እንደለወጥኩልህ ለማንም አትንገር" ሲል አስጠነቀቀው፡፡ ባሕራንም "እሺ ጌታዬ እንዳዘዝከኝ አደርጋለሁ" ብሎ ጉዞውን ቀጠለና የዚያን የባለፀጋ ቤት እየጠየቀ ከደረሰበት በኋላ ደብዳቤውን ለሹሙ ሰጠው።


ያም ሹም ደብዳቤውን ተቀብሎ ሲያነብ የታተመበት ማኅተም ዕውነተኛ መሆኑን ከአረጋገጠ በኋላ እግዚአብሔር እንዳዘዘው በቤተ ክርስቲያን ደንብ የባለጸጋውን ልጅ በተክሊል አጋባው፣ የሠርጉንም በዓል እስከ ዐርባ ቀን ድረስ በታላቅ ደስታ አከበሩ። ከሠርጉም በዓል ፍጻሜ በኋላ ያ ባለጸጋ ሰው ከሄደበት አገር ወደ ሀገሩ ተመልሶ ገባና በቤቱ አካባቢ ሲደርስ የደስታና የዘፈን ድምፅ ስለሰማ "ይህ የምሰማው ድምፅ ምንድነው?" ሲል ጠየቀ፡፡ ሰዎቹም "ባሕራን የተባለ ጐበዝ ካንተ ዘንድ ልጄን ዳሩለት የሚል ትእዛዝ አምጥቶ ልጅህን አግብቶ በሠርጉ ምክንያት ይዘፍናሉ ይደሰታሉ እነሆ እየበሉና እየጠጡ በቀንና በሌሊት እየዘፈኑ ሲደሰቱ ዐርባ ቀን ሆኗቸዋል በመልእክትህም እንዳዘዝከው ገንዘብህን የወንድና የሴት ባሮችህን በጠቅላላው የሚንቀሳቀስና የማይንቀሳቀስ ንብረትህን ሁሉ በሙሉ አስረክበውታል" አሉት።
ያም ባለጸጋ ያህን ቃል በሰማ ጊዜ ከድንጋጤው የተነሳ በታላቅ ቃል በመጮኽ ከመሬት ላይ ተከስክሶ ሞተና ነፍሱን አጋንንት ተረክበው ወደ ሲኦል አወረዷት። ከዚህም በኋላ ባሕራን የተባለ ያ ጐልማሳ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል በየወሩ እያከበረ ዝክሩን እየዘከረ ይኖር ጀመር። በዚያን ጊዜ በጉዞ ላይ ሳለ ተገልጾለት የሞቱን መልእክት ወደ ሕይወት የለወጠለት ቅዱስ ሚካኤል እንደሆነም አወቀ ተረዳ። ንዑድ ክቡር የሚሆን የመላእክት ሁሉ አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ያደረገው ተአምር ሊቆጥሩት የማይቻል ብዙ ስለሆነ በኛም ላይ ኃይለ ረድኤቱ አድሮብን ይኑር እስከ ዘላለሙ ድረስ አሜን።
+ + +

ቅድስት አፎምያ፡- ቅድስት አፎምያ ሀገሯ ኪልቅያ ነው፡፡ ባለቤቷ አስተራኒቆስ መስፍነ ኪልቅያ ነበረ፡፡ እርሷም በትዳር በነበረችባቸው ዘመናት እግዚአብሔርን ከሚወድ ባለቤቷ ጋር እግዚአብሔርን ስታገለግለው የኖረች ሴት ደገኛ ሴት ናት፡፡ በየወሩ በ29 ቀን የጌታችንን የልደቱን፣ ወር በገባ በ21 የእመቤታችንንና ወር በገባ በ12 የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ እያደረጉ ነዳያንን ይጎበኙ ነበር፡፡

ባለቤቷ አስተራኒቆስ ከዚህ ዓለም የሚያርፍበት ጊዜ እንደደረሰ ባወቀ ጊዜ ይሰጡት የነበረውን ምጽዋት እና የሦስቱን በዓላት መታሰቢያ ማድረግ እንዳታስታጉል ከአደራ ጋር አዘዛት፡፡ እርሷም የመልአኩን የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባለቤቷን ጠይቃ አሠርቶ ሰጣት፡፡ በከበረ ቦታም አኖረችው፡፡ ባሏ ካረፈ በኋላ ያዘዛትን መንፈሳዊ ሥራ ከወትሮው አስበልጣ መሥራት ቀጠለች፡፡ ባሏም ታሞ ሞቶ ከሀብቷ ከንብረቷ እየሰጠች እየመጸወተች በጾም በጸሎት ተወስና ትኖር ነበር፡፡ ሰይጣን ለምቀኝነት አያርፍምና ደግ መነኩሴ መስሎ አጋንንትን መነኮሳይያት አስመስሎ መጥቶ ከደጅ ሆኖ አስጠራት፡፡ እርሷም "ከቤት ገብታችሁ በቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ፊት ጸልዩልኝ" አለቻቸው፡፡ ሰይጣናቱም "እኛማ በነግህ ጸልየናል?" አሏት፡፡ ቀጥሎም ሰይጣን "...እንደው አንቺ ግን ይህ ሁሉ ጾም ጸሎት ምን ያደርገልሻል? ሀብትሽን ሰጥተሸ መጨረስሽስ ስለምንድን ነው? በዚያ ላይ አንቺ ስትደክሚ የሚደግፍሽ ስታረጂ የሚጦርሽ ልጅ የለሽም ሁለተኛ ማግባት ኃጢአት መስሎሻልን? እነ አብርሃም እነ ዳዊ ከብዙ ሴቶች ብዙ ልጆች ወልደው የለምን? አሁንም ቤት ሰሪ ጎመን ዘሪ ልጅ ያስፈልግሻልና ባል አግቢ፣ እሺ በይኝ" አላት፡፡

 ቅድስት አፎምያም "አባ ቆብህ መልካም ነበር ንግግርህ ግን ክፉ ነው፣ አትጹሚ አትጸልዩ ያልከኝ ጌታ ምጽዋት አበድር እመስዋዕት ብሎ የለምን? ሁለተኛ ባል አግቢ ማለትንስ ከምን አገኘኸው? እርግቦች እንኳ ባሎቻቸው ከሞቱባቸው ከሌላ ወንድ አይቀርቡም ታዲያ ጥንቱን በንጽሕና ሊኖር የተፈጠረ ሰው ሁለተኛ አላገባም ቢል ዕዳ ፍዳ ሊሆንበት ነውን?" ብላ ሞገተችው፡፡

 የሰው ልጆች ጠላት የሆነው ሰይጣንም በመልካም አገልግሎት ስትበረታ አይቷታልና ዝም ብሎ ሊተዋት አልወደደም፡፡ ከላይ እንዳየነው በመጀመሪያ ባል ሳታገባ ማገልገሏን ትታ ሌላ ባል አግብታ ልጅ ወልዳ እንድትኖር በብዙ ማባበል ጠየቃት፡፡ ባሏ መንግሥተ ሰማያትን ስለወረሰ ምንም ምጽዋት እንደማይሻ አስመስሎ ነገራት፡፡ ቅድስት አፎምያ ግን ዳግመኛ ትዳር ላለመመሥረት ቃል ኪዳን እንደገባች ርግብንና ዖፈ መንጢጥን አብነት አድርጋ እነርሱ እንኳ በሕይወት ዘመናቸው ከአንድ ባል ውጪ ሌላ ባል እንደማያውቁ በመጥቀስ አሳቡን እንደማትቀበለው ገለጸችለት፡፡ ሰይጣንም አስመሳይ መሆኑ አላዋጣ ሲለው ማንነቱን ቀይሮ ሊያንቃት ቢሞክር የእግዚአብሔርንና የቅዱስ ሚካኤልን ስም ጠርታ አባረረችው፡፡ እርሱም ተመልሶ መጥቶ እንደሚያጠፋት ዝቶባት እንደአቧራ በኖ እንደ ጢስም ተኖ ጠፋ፡፡
በሰኔ 12 ቀን የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ እያዘጋጀች ሳለች ሰይጣን ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እንደሆነ ገልጾ የመጀመሪያውን የመሰለ ከንቱ ምክሩን አሰማምሮ አቀረበላት፡፡ አሳቡንም የእግዚአብሔር ፈቃድና አሳብ እንደሆነ አድርጎ ለማሳመን ሞከረ፡፡ ሰይጣን አስቀድሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በገዳመ ቆሮንቶስ መጻሕፍትን እየጠቀሰ እንደተፈታተነው ሁሉ ቅድስት አፎምያንም ለማሳመንም አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብን፣ ዳዊትን የመሳሰሉ ደጋግ አባቶችን ታሪክ እየጠቀሰ ወደ ትዳር እንድትገባ ደጋግሞ ወተወታት፡፡ ቅድስት አፎምያም በእግዚአብሔር ኃይል ጸንታ በቅዱስ ሚካኤልም ተራዳኢነት ታምና "የእግዚአብሔር መልአክ ከሆንክ መንፈሳዊ ማረጋገጫህ የሆነው የመስቀል ምልክት የታለ?" በማለት በምድራዊ ንጉሥና በጭፍራው መካከል የሚኖርን የጋራ መግባቢያ መንገድ ዋቢ አድርጋ ጠየቀችው፡፡ ለጊዜው "በእኛ በመላእክት ዘንድ እንዲህ አይደለም" ብሎ ሊሸነግላትና አቋሟን ሊያስቀይራት ሞከረ፡፡ ከቤቷ ያለ የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ላይ ያለውን ምልክት አብራርታ የእርሱ ግን ከዛ ጋር አንድነት እንደሌለው አረጋገጠችበት፡፡ በመቀጠልም ከቤቷ ላለው ለቅዱስ ሚካኤል ሥዕል እጅ እንዲነሣ ጠየቀችው፡፡ በዚህ ጊዜ መልኩ ወደ ትክክለኛ ሰይጣናዊ ማንነቱ ተለወጠና ጨለማ ለብሶ እየዛተ አነቃት፡፡ ቅድስት አፎምያም የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤልን "ድረስልኝ" እያለች በጠራችው ጊዜ መልአኩም ፈጥኖ በመድረስ ከሰይጣን እጅ አዳናት፡፡

 የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም ለሰይጣኑ ተገቢውን ቅጣት ሰጥቶ ቅድስት አፎምያን ባረካት፡፡ የዕረፍት ቀኗ በዚህ ቀን መሆኑን ነግሮ ቤቷን እንድታዘጋጅ አዘዛት፡፡ የበዓሉን ዝግጅት አከናውና ሥጋ ወደሙን ተቀብላ ኤጲስ ቆጶሱንና ካህናቱን እንደየመዓርጋቸው ጠርታ በቤቷ አክብራ ተቀበለቻቸው፡፡ ለነዳያንና ለጾም አዳሪዎች በኤጲስ ቆጶሱና በካህናቱ እጅ ገንዘቧን መጽውታ መንገዷን አሳመረች፡፡ ስለ ኃጢአቷ እንዲጸልዩላት ተማፅና በፊታቸው ተንበርክካ ጸለየች፡፡ ባሏ ያሠራላትን የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል አቅፋ ስማ ከተማጸነች በኋላ ሰኔ 12 ቀን በሰላም ዐረፈች፡፡ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፣ በጸሎቷ ይማረን!


እጅግ አስገራሚው የቅዱስ ላሊበላ ሙሉ ገድል በክፍል ኹለት ይቀጥላል....


+ + + + + 

ጻድቁ ንጉሥ ቅዱስ ላሊበላ፡- ቅዱስ ላሊበላ ጌታችን የጠጣውን መራራ ሐሞት በማሰብ ሁልጊዜ ዓርብ ዓርብ ኮሶ ይጠጣ ነበር፡፡ ቅዱስ ገብርኤል ላሊበላን ኢየሩሳሌም ወስዶት በዚያ ያሉ ቅዱሳን መካናትን ሁሉ አሳይቶ አሳልሞታል፡፡ ወደ ሰማይም ነጥቆ ወስዶ ሰባቱ ሰማያትን ያሳየው ሲሆን በጌታችን ፊትም አቅርቦት አስባርኮታል፡፡ ጌታችንም ‹‹ሕዝቦቼ የመከራና የሥቃዬን ቦታ ለማየት ኢየሩሳሌም በመሔድ በመንገድ እየቀሩ ስለሆነ አሁን ግን አንተ በሀገረ ሮሀ ኢየሩሳሌምን ትሠራለህ›› በማለት የቤተ መቅደሶቹን አሠራር በዝርዝር ነግሮታል፡፡ ከነገሠም በኋላ ሱባኤ ገብቶ ቤተመቅደስ የሚሠራበትን ቦታ በጸሎት ሲጠይቅ ዛሬ ቤተ ማርያም ካለችበት ቦታ ላይ የብርሃን አምደ ወርቅ ተተክሎ መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ስላየ ቦታው እግዚአብሔር የፈቀደው መሆኑን አውቆ ሥራውን ጀመረ፡፡ ጌታችን ቀድሞ ‹‹እኔ ራሴ ነኝ እንጂ ቤተ መቅደሶቹን የምትሠራቸው አንተ አይደለህም፣ ነገር ግን በአንተ ስም እንዲጠራ ስለፈቀድኩ ሄደህ ሥራ›› ብሎ እንዳዘዘው ቅዱስ ገድሉ ይናገራል፡፡ ላሊበላ ዓሥሩን ቤተመቅደሶች ሲሠራ እርሱ አንድ ስንዝር ሠርቶ እንደሆነ ሌሊቱን ዓሥር ስንዝር ሆኖ ያገኘው ነበር፡፡ ቀንም ሲሠራ ቅዱሳን መላእክት በማይታወቁ ሰዎች አምሳል ሆነው ይራዱት ነበር፡፡ በመጨረሻም ጌታችን በገሃድ ተገልጦለት በቦታው ላይ እጅግ አስገራሚ ቃልኪዳኖችን ሰጥቶታል፡፡
ከ10ኛው እስከ 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (920-1253 ዓ.ም ድረስ) በላስታ ቡግና ምድር የነገሡ የላስታ ቡግና ተወላጅ የሆኑ የኢትዮጵያ ቅዱሳን ነገሥታት የንግሥናቸው መጠሪያ ‹‹የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት›› ወይም ‹‹የላስታ መንግሥት›› በመባል ይታወቃል፡፡

  የላስታ ነገሥታት የዘር ሀረጋቸው ከንጉሥ ሰሎሞን ዘር ሲያያዝ የመጣ ነው፡፡ ከላስታ (ከዛጉዌ) ነገሥታት መካከል ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ቅዱስ ገብረ ማርያም፣ ቅዱስ ላሊበላና ቅዱስ ነአኵቶለአብ እነዚህ አራቱ ነገሥታት እንደ መልከጼዴቅ (ዘፍ 14፡18) ክህነትን ከንግሥና፣ ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅድስና አገልግለው አልፈዋል፡፡ በንግሥናቸው ሀገራችንን በመልካም ሥራና በቅድስና ከማስተዳደራቸው በተጨማሪ ቅዱሳን ጻድቃን ሆነው እግዚአብሔርን በብዙ ድካም በመልካም ተጋድሎአቸው ያገለገሉና አገልግሎታቸውም ሆነ ቅድስናቸው በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተመሰከረላቸው ጌታችን የሰጣቸውን ቃልኪዳን መሠረት በማድረግ ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ፣ በስማቸው ቤተክርስቲያን አንጻ፣ ጽላት ቀርፃ በዓላቸውን እያከበረች መታሰቢያቸው ተጠብቆ ለዘለዓለም እንዲኖር አድርጋለች፡፡


እኛ ኢትዮጵያውያን የቅዱስ ላሊበላን እጅግ ድንቅ የሆኑ ሥራዎቹን ዓለም ከሚመለከትበት የተለየ መንፈሳዊ ዐይን ሊኖረን ይገባል፡፡ ስለዚህም የቅዱስ ላሊበላን የቅድስና ሕይወትና ከእግዚአብሔር ጋር ስለነበረው ግንኙነት ገድለ ቅዱስ ላሊበላን መነሻ በማድረግ ብዙ ነገሮችን ቀጥሎ እናያለን፡-

1. ቅዱስ ላሊበላ ከአባቱ ዣን ስዩምና ከእናቱ ኪርወርና ጌታችን በተወለደበት ዕለት ታኅሣሥ 29 ቀን 1101 ዓ.ም በላስታ ቡግና ወረዳ ልዩ ስሟ ሮሀ በተባለችው ሥፍራ ተወለደ፡፡ የልደቱን ነገር አስቀድሞ ቅዱስ ሚካኤል ለእናቱ ነግሯት ነበርና በተወለደ ጊዜ ብዙ ነጫጭ ንቦች መጥተው በሰውነቱ ላይ አርፈው እንደ ማር እየላሱት ስለታዩ እናቱ ‹‹ልጄን ንብ ዘበኛ ሆኖ ይጠብቅልኛል›› ስትል ስሙን ‹‹ላል ይበላል›› ብላዋለች፡፡ ላል በአገውኛ ንብ ማለት ነው፡፡ በጊዜ ብዛት በተለምዶ ነው ‹‹ላሊበላ›› ተብሎ መጠራት የተጀመረው፡፡ ንቦቹ ግን ሥጋዊ ንቦች ሳይሆኑ በንብ የተመሰሉ መላእክት ናቸው፡፡ ንጉሥ መሆኑን እያመለከቱ የሃይማኖትና የምግባር ማር ከእርሱ ይቀዳል ሲሉ በንብ ሠራዊት ተመስለው ሰውነቱን ላሱት፡፡ እንደ ዮሐንስና እንደ ኤርምያስም በእናቱ ማኅፀን ሳለ ነው መንፈስ ቅዱስ የሞላበት፡፡
ከዚህ ቀጥሎ በገድሉ ውስጥ የተጠቀሱ አንዳንድ አስደናቂ ነገሮችን እናያለን፡፡ 

2. ቅዱስ ላሊበላ ያነጻቸውን አብያተ ክርስቲያናት መመልከት ያለብን በቅርስነታቸውና በቱሪስት መስህብነታቸው ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ የተገኙ ብቸኛ መንፈሳዊ ሀብቶቻችን መሆናቸውን ነው፡- ስለ ቅዱስ ላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት ከማንሳታችን በፊት በመጀመሪያ እውነተኛ የሕይወት ቃል የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስን መመልከት የግድ ያስፈልጋል፡፡ ቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያ ቀድሞ በሕገ ልቡና ከዚያም በሕገ ኦሪት እግዚአብሔርን ስታመልክ ኖራለች፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ሐዋርያቱ እንኳን ለስብከት ከኢየሩሳሌም ሳይወጡ ነው በ34 ዓ.ም በራሷ ሐዋርያ በጃንደረባው ባኮስ አማካኝነት በክርስቶስ ማመንንና ጥምቀትን ወደ ሀገሯ ያመጣችው፡፡ የዚህ ደግሞ ምስክሩ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ 1ኛ ነገ 10፡1-13፣ ሐዋ 8፡26-40፡፡ በዚህ መረጃ መሠረት ኢትዮጵያውያን ከጥንት ጀምሮ እስከ ሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ ወደ ኢየሩሳሌም እየሔዱ ሃይማኖታዊ ጉዞ ያድርጉ ነበር፡፡

ከ7ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በኋላ ግን ከኢትዮጵያ ተነስቶ በሱዳን በግብፅ አድርጎ ወደ ኢየሩሳሌም በእግርና በእንስሳት ጉዞ ለማድረግ የመንገዱ አድካሚነትና በረሃማነት የሚባክነው ጊዜ እንዲሁም በኢየሩሳሌም ዙሪያ ተሻግሮም እስከ ግብፅና ሱዳን ድረስ የእስልምና ሃይማኖት ስለተጠናከረ ለኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ወደ ኢየሩሳሌም ለመጓዝ አስቸጋሪ ስለሆነባቸው ለሃይማኖታዊ አምልኮና ስግደት ወደ ኢየሩሳሌም የሚያደርጉት ጉዞ ተቋረጠ፡፡ ይህ ሁኔታም ሲያያዝ እስከ ቅዱስ ላሊበላ ዘመን ደርሷል፡፡

ቅዱስ ላሊበላም የኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ወደ ኢየሩሳሌም ያደርጉት የነበረው ጉዞ በመቋረጡ በእጅጉ እያዘነ ተግቶ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ የኢየሩሳሌምንም አምሳያ የሆኑ አብያተ ክርስቲያናትን በሀገሩ ለመሥራት ይመኝ ነበር፡፡ ጥቂት ነገር ሲለምኑት አብዝቶ መስጠት ለእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ነውና ላሊበላ ምድራዊ ኢየሩሳሌምን በሀገሩ ለመሥራት ሲያስብ ልዑል እግዚአብሔር በጥበቡ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ (2ኛ ቆሮ 12፡1-7) ወደ ሰማይ አሳርጎት ሰማያዊት ኢየሩሳሌምን አሳይቶታል፡፡ ጌታችንም ‹‹ሕዝቦቼ የመከራና የስቃዬን ቦታ ለማየት ኢየሩሳሌም በመሄድ በመንገድ እየቀሩ ስለሆነ አሁን ግን አንተ በሀገረ ሮሐ ኢየሩሳሌምን ትሠራለህ›› በማለት የቤተ መቅደሶቹን አሠራር ሁሉ በዝርዝር ነግሮታል፡፡ በሰማያዊት ኢየሩሳሌምም ምሳሌ በሀገሩ ላይ ወጥ ከሆኑ የዓለት ድንጋዮች መላእክት እየተራዱት ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን እንዲያንጽ ነግሮታል፡፡

 3. ጠላት ለክፉ ያሰበውን እግዚአብሔር ለበጎ ያደርገዋል፡- ወደኋላ ተመልሰን የቅዱስ ላሊበላን የልጅነት ሕይወቱን እናንሳ፡- ቅዱስ ላሊበላ እናትና አባቱ ከሞቱበት በኋላ ወደ ጎጃም በመሄድ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን፣ ብሉይና ሐዲስን በደንብ ተምሮ ከጨረሰ በኋላ ወደ ደብረ ሮሐ ተመልሶ መጥቶ ነግሦ ከነበረው ከወንድሙ ከገብረ ማርያም ዘንድ ተቀመጠ፡፡ ‹‹ከገብረ ማርያም ቀጥሎ የሚነግሠው ላሊበላ ነው›› ተብሎ ትንቢት ስለተነገረ ሊያጠፋው ምክንያት ይፈልግበት ነበር፡፡ ለዐፄ ገብረ ማርያም በእናትም በአባትም እኅት የምትሆነው ለላሊበላ ግን በአባት ብቻ እኅት የሆነችው ዮዲት ላሊበላን ለመግደል በማሰብ ቀን ከሌሊት አጋጣሚን ትጠብቅ ነበር፡፡ ቅዱስ ላሊበላም ጌታችን መራራ ሐሞት መጠጣቱንም እያሰበ ሁልጊዜ ዓርብ ዓርብ ከጾምና ጸሎት በኋላ መራራ ኮሶ ይጠጣ ነበርና ይህን አጋጣሚ በመጠቀም አንድ ቀን እንደጠማው አውቃ በጠላ ውስጥ መርዝ ጨምራ ሰጠችው፤ ቅዱስ ላሊበላም መርዝ የተቀላቀለበትን ጠላ ጠጣው፡፡ እርሱ ከመጠጣቱ በፊት ያገለግለው የነበረው ዲያቆን ቀምሶት ወዲያው ሲሞት አየ፡፡ ዲያቆኑ ያስመለሰውን የጠጣው ውሻም ወዲያው ሞተ፡፡ ቅዱስ ላሊበላም ይህን ሲመለከት በሐዘንና በፍጹም ፍቅር ሆኖ ‹‹አገልጋዬ ለእኔ የተዘጋጀውን መርዝ ጠጥቶ እንደሞተ ሁሉ እኔም መሞት ይገባኛል›› በማለት ያን መርዝ ስለወዳጁ ፍቅር ሲል ጠጥቶ ለመሞት ቆረጠና ጠጣው፡፡ ጌታችን በወንጌሉ ስለራሱ ‹‹ስለ በጐቹ ቤዛ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ የሚሠጥ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም›› (ዮሐ 15፡13) ብሎ የተናገረውን ቃል ቅዱስ ላሊበላም ስለ ወዳጁ ሞት ሲል ራሱን ለሞት አሳልፎ ሰጠ፡፡ ነገር ግን መርዙ እንኳን ሊጎዳው ይቅርና በሆዱ ውስጥ ከልጅነቱ ጀምሮ የነበረበትን የሆድ ሕመም ነቅሎ አወጣለት፡፡ በዚህም ጌታችን በወንጌሉ ‹‹የሚገድል መርዝም ብትጠጡ ምንም አትሆኑም›› (ማር 16፡18) ያለው ቃል ተፈጽሞለታል፡፡ መርዙ ለበጐ ሆኖለት ከሆዱም ውስጥ የነበረው ጥፍሮች ያሉት አውሬ መሰል ፍጡር ወጣለትና የሆድ ሕማሙ ፈጽሞ ተወው፡፡ ያን ጊዜም ቅዱስ ላሊበላ በወቅቱ ለሦስት ቀንም ያህል እንደሞተ ሆኖ የቆየ ቢመስልም ቅዱስ ገብርኤል ግን በመንፈስ ወደ ሰማይ ነጥቆ ወስዶ ሰባቱ ሰማያትን ያሳየው ሲሆን በጌታችን ፊትም አቅርቦት አስባርኮታል፡፡ ጌታችንም ቅብዓ መንግሥት ቀብቶት ትልቅ ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡ 

ጻዲቁ ንጉሥ ቅዱስ ላሊበላ ቅድስናን ከንግሥና፣ ክህነትን ከንጽሕና፣ ጥበብ መንፈሳዊን ከጥበብ ሥጋዊ ጋር አንድ አድርጐ አስተባብሮ የያዘ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራ፣ ቅዱሳን መላእክትም ይራዱት እንደነበርና ጌታችንም ትልቅ ቃልኪዳን እንደሰጠው ከቅዱስ ገድሉ ላይ እናገኛለን፡፡ ከጌታችን ዘንድ የተሰጠውንም ቃልኪዳን በሦስት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ በዚህም መሠረት፡- 

1ኛ. መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ላሊበላን እየመራው ከላስታ ወደ አክሱም ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም አድርሶ በዚያ የሚገኙትን ቅዱሳት መካናት ሁሉንም ካሳየው በኋላ ‹‹ወደ ሀገርህ ሮሐ ተመልሰህ በእነዚህ ምሳሌ ታንጻለህ›› ብሎታል፡፡ ወደ ሀገሩም ተመልሶ በአሽተን ማርያም ተራራ ላይ ሱባኤ ይዞ በጾም ጸሎት ተወስኖ ሳለ እግዚአብሔር የሚሠራቸውን መቅደሶች በግልጽ በራእይ አሳይቶታል፡፡ 

2ኛ. ከላይ እንዳየነው ለሞት ተብሎ የተሰጠው መርዝ ለሕይወት ሆኖለት በመሬት ላይ ወድቆ ሳለ በነፍስ መልአክ ነጥቆት እስከ ሰባተኛው ሰማይ ጽርሐ አርያም ድረስ ደርሶ በጌታ ፊት ቀርቦ ከጌታ ዘንድ ‹‹እኔ አከበርኩህ ቃሌ አይታበይም፣ ከአንድ ቋጥኝ እነዚያን በራእይ ያሳየሁህን አብያተ ክርስቲያናት ታንጻለህ›› የሚል ቃልኪዳን ተቀብሏል፡፡



 3ኛ. ከኢየሩሳሌምም ተመልሶ የንግሥናውን ዙፋን ከቅዱስ ገብረ ማርያም ከተረከበ በኋላ በተሰጠው መንፈሳዊ ሀብትና ባየው ራእይ መሠረት አብያተ ክርስቲያናቱን አንጾ ከጨረሰ በኋላ በቀኝና በግራው ዓሥር ዓሥር ኪሎ የሚመዝን የዓለት ድንጋይ ተሸክሞ ለ7 ዓመት ሲጾም ሲጸልይ ጌታችን ተገልጦለት ‹‹…ያነጽካቸውን ቤተ መቅደሶች የተሳለመውን ኢየሩሳሌምን እንደተሳለመ አድርግለታለሁ›› የሚለውን የመጨረሻውን ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡ (ይህን ቃልኪዳኑን መጨረሻ ላይ በዝርዝር እናየዋለን) እነዚህን ሦስት ዋና ዋና ቃልኪዳኖቹን በቅድሚያ ማንሳት የፈለኩበት ምክንያት ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት ስለ ቅዱስ ላሊበላ ድንቅ ሥራዎች ከማሰባችንም ሆነ ከመናገችን በፊት በቅድሚያ ስለ ራሱ ስለ ቅዱስ ላሊበላ የቅድስና ሕይወቱና ከእግዚአብሔር ጋር የነበረውን ግንኙነት ማወቁ የግድ አስፈላጊ መሆኑን ለመጠቆም ነው፡፡ አሁን አሁን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሆን ተብሎ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ውቅር አብያተ ክርስቲያናቶቹ በቱሪስት መስህብነታቸው ብቻ እየታዩ የቅድስና ታሪካችንም እየተጨፈለቀና መንፈሳዊ እሴቶቻችንንም ለማጥፋትም ጥረት እየተደረገ ስለሆነ እውነተኛውን ነገር በደንብ ማወቅና በእጅጉ መጠንቀቅ ስላለብን ነው ይህን የማነሳው፡፡ ስለዚህ የቅዱስ ላለበላን የቅድስና ሕይወትና ከእግዚአብሔር ጋር የነበረውን ግንኙነት ስንረዳ እነዚያ እጅግ ድንቅ የሆኑ ሥራዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ኃይልና በሰማያውያን መላእክት እርዳታ የተሠሩ መሆናቸውን እንረዳለን፤ እግዚአብሔርም ለእኛ የሰጠንን ድንቅ የምሕረትና የቃልኪዳን ስጦታዎቻችን መሆናቸውን እንረዳለን፡፡ ያንጊዜም ውቅር አብያተ ክርስቲያናቶቹን ዓለም ከሚመለከትበት የተለየ መንፈሳዊ ዐይን ይኖረናል፡፡ የቃልኪዳኑም ተጠቃሚዎች ለመሆን መንፈሳችን ይነሳሳል፡፡ በዚህ ደግሞ አሁን ያለውም ሆነ ወደፊት የሚመጣው ትውልድ ታሪኩን ከማጉደፍና ከጥፋት ይጠበቃል፣ አኩሪ ታሪኩንም ጠንቅቆ ለማወቅ መንፈሳዊ ቅናትም ስለሚያድርበት ራሱንም ከውጪው የባሕል ወረራና ጥቃት ይጠብቃል፡፡ በሀገራችን ያሉትን እጅግ ጥልቅ የሆኑ ሃይማኖታዊና ባሕላዊ ምሥጢሮችን ጠንቅቀው የተረዱት እነ ፕሮፌሰር ፓንክረስት ‹‹ክርስቶስ ከነጮች ይልቅ ለኢትዮጵያውያን ቅርበት አለው›› በማለት ምስክርነታቸውን እየሰጡ ባለበት ወቅት የዘመኑ የሀገራችን ወጣት ማንነቱን ጠንቅቆ ቢያውቀው ኖሮ የእነርሱን (የነጮቹን) ባሕል ለመከተል ባልዳዳው ከዘመናዊ ባርነትም ራሱን በጠበቀ ነበር፡፡


4.መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለቅዱስ ላሊበላ ስለ ቤተመቅደሶቹ አሠራር በዝርዝር እንዳስረዳው፡- በተራ ቁጥር ሁለት ላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው በቅዱስ ገድሉ ላይ ከገጽ 117-127 ድረስ በጣም በስፋትና በዝርዝር እንደተጠቀሰው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ላሊበላን እስከ ሰባተኛው ሰማይ ድረስ በመላእክት ተነጥቆ በፊቱ እንዲቆም ካደረገው በኋላ ቤተ መቅደሶቹን እንዴት እንደሚያንጽ ቃል በቃል ነግሮታል፡፡ እግዚአብሔር ለኖህ መርከቡን እንዴት እንደሚሠራ ከነልኬቱ ጭምር በዝርዝር እንደነገረው ሁሉ ለቅዱስ ላሊበላም ዝርዝር ሁኔታዎችን ጭምር እንዲህ በማለት ትእዛዝ ሰጥቶታል፡- ‹‹መልአኩም ክብሩ ከሰማያት ሁሉ ክብር ወደሚበልጥ ወደ ሰባተኛው ሰማይ አደረሰው፣ ቅዱስ ላሊበላም ይህንን አይቶ በግንባሩ ተደፋ፣ ከኪሩቤል ዘንድ ይነሳ የሚል ቃል ተሰማና አንዱ ሱራፌል መጥቶ አነሣው፡፡ ልቡንም አጽንቶ አቆመው…እግዚአብሔርም ተናገረው፡- ‹በምድር ላይ ቤተመቅደስ ትሠራልኝ ዘንድ የማሳይህን አስተውል፤ እዝነ ልቡናህንም ግለጥ፡፡ ከሰው ጋር ስለምኖር በሰማያት የምትኖር አባታችን እያሉ ከሚጠሩኝ በሃይማኖት ከተጐናፀፈኝ ስሜን ከሚያመሰግኑ ከመረጥኳቸው ከሕዝብ አንደበት በምመሰገንበት ገንዘብ እኔ ፈጥሬያቸዋለሁና፡፡

ከመጀመሪያይቱ ድንኳን ውስጥ በተሣለው ላይ ምስላቸው የተሠራ ከሚንቀሳቀሱ ከኪሩቤል አምሳል ለሙሴ እንደተናገርኩት አይደለም፡፡ ወዳጄ ሙሴ የመጀመሪያይቱን ድንኳን አርአያ በደብረ ሲና እንዳሳየሁት ድንኳንን እንደሠራ ሁሉ እንደሁ አንተም እንዳሳየሁህ ትሠራ ዘንድ ዕወቅ፣ አስተውል፣ ተጠንቀቅም፡፡ የማሳይህ ግን ለሙሴ እንዳሳየሁት አይደለም፤ መቅደሴን የምትሠራልኝም ሙሴ እንደሠራው አይደለም፤ ሙሴስ ከተፈተለ ልብስና ከእንጨት ድንኳን ሠራ፤ አንተ ግን ለምሰሶውም ሆነ ለመቀኑ ለመድረኩ እንጨትን የምትፈልግ አይደለህም፤ ለጠፈራቸው መማገሪያ ገመድ የምትሻ አይደለህም፣ እንጨትንም ለማገር፣ ለምሰሶዋቸውም ገበታ፣ ለዙሪያቸውም ለማያያዣ ጭቃን የምትፈልግ አይደለህም፡፡ የቤተመቅደሶችን ፈቃድ ሁሉ ከአንድ ቋጥኝ ድንጋይ ትፈጽማለህና፡፡ የማሳይህ እኚህ የቤተ መቅደሶች አኗኗር ከምድር ልብ ውስጥ እስከዛሬ አለ፡፡ ከአሁን ጀምሮ በእጅህ እስኪገለጡም ድረስ በምድር ልብ ይኖራሉ፡፡ በሰው ልጅ ጥበብ ያይደለ በእኔ ሥልጣን ከምድር ልብ ውስጥ ታወጣቸው ዘንድ መረጥሁህ፡፡ ሕዝቦቼ ተወልጄ አድጌ ሞቼ ተቀብሬ ከሞትም የተነሳሁባትን ሀገር ለማየት ኢየሩሳሌም በመሄድ ግማሹም በበረሃ ይቀር ነበር አሁን ግን አንተ ኢየሩሳሌምን በሀገርህ ትሠራለህ፡፡ በማንም እጅ ዳግመኛ ሊሠሩ የማይችሉ ቤተ መቅደሶቼን እንዳሳየሁህ ትሠራለህ፡፡ አንተም እንዳሳየሁህ በልብህ ውስጥ አኑራቸው፡፡ ስትሠራቸውም እየልካቸው ይሁን፤ ከእርዝመታቸውም በላይ ቢሆን፣ ከወርዳቸውም በላይ ቢሆን፣ በመወጣጫቸውም ላይ ቢሆን አንዳች እንዳትጨምር፡፡ ያሳየሁህ እሊህ ዐሥሩ መቅደሶች ከአንዲት ቋጥኝ ድንጋይ ሲወጡ አይተሃልና….› እያለ ጌታችን ሲነግረው ጻዲቁ ንጉሥ “ይህ እንዴት ይሆናል?” በማለት ይጠይቃል፡፡ ጌታም እውነት እልሃለሁ እነዚህ ያሳየሁህ መቅደሶች በሰው ኃይል የሚሠሩ ሆነው አይደለም፤ ጀማሪያቸው ሠሪያቸውና ፈጻሚያቸው እኔ ነኝ ነገር ግን ኃይሌ በአንተ እጅ እንዲገለጽ ለምክንያት ተልከሃል፤ አንተ አነጽካቸው እየተባለ እስከ ዕለተ ምፅዓት ድረስ ስምህ ይጠራባቸዋል…›› እያለ ይቀጥላል የቅዱስ ላሊበላ ገድል፡፡ ቤተ መቅደሶቹንም ለመሥራት ቦታውን ያውቅ ዘንድ ሱባኤ ገብቶ ሳለ ዛሬ ቤተ ማርያም ካለችበት ቦታ ላይ ቅዱሳን መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ታይተውት በቦታው ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ መቅደሱን መሥራት ጀመረ፡፡ ዓሥሩን ቤተ መቅደሶች ሲሠራ እርሱ አንድ ክንድ ሠርቶ እንደሆነ ሌሊቱን አድሮ በቀጣዩ ቀን አሥር ክንድ ሆኖ ያገኘው ነበር፣ ቀንም በማይታወቁ ሰዎች አምሳል እየተገለጡ መላእክት ይራዱት ነበር፡፡

5. አንዳንድ ነገሮች ስለ ቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፡- ቅዱስ ላሊበላ ዓሥሩም ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በጣም በሚያስገርም ሁኔታ በውስጥና በውጭ ያሉት ብዙ ቅርጾች ነገረ ድኅነትን በምሳሌ እንዲወክሉ አድርጎ ነው ያነጻቸው፡፡ የክርስቶስን መከራና በእርሱም የተገኘውን ፍጹም ዘላለማዊ ድኅነት በእያንዳንዱ ቤተ መቅደስ ውስጥ እንዴት አድርጎ በምሳሌ እንዳስቀመጠው እጅግ አስገራሚ ነው፡፡

በላስታ ቅዱስ ላሊበላና አካባቢው የሚገኙ ሌሎች አስደናቂ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፡- ከአሥሩ የቅዱስ ላሊበላ አስደናቂ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በተጨማሪ የቅዱስ ነአኵቶለአብና የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ አብያተ ክርስቲያናት እንዲሁም አሸተን ማርያም በዋናነት ሕዝበ ክርስቲያኑ የሚጐበኛቸው ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡ በላሊበላና አካባቢው ግን እጅግ ጥንታዊና አስደናቂ የሆኑ በጣም በርካታ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል ሣርዝና ሚካኤል፣ ብልባላ ቂርቆስ፣ ብልባላ ጊዮርጊስ፣ አርባዕቱ እንስሳ፣ ትርኩዛ ኪዳነምሕረት፣ ገነተ ማርያም፣ ቀንቀኒት ሚካኤል እነዚህ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ሲሆኑ እንዲሁም ዋልድቢት ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም፣ አቡነ ዮሴፍ ገዳም፣ ገብረ ክርስቶስ ዋሻ ቤተክርስቲያን፣ ቅድስት አርሴማ ቤተክርስቲያን፣ ቀደሊት ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ እመኪና መድኃኔዓለምና እመኪና ልደታ፣ ማውሬ እስጢፋኖስ፣ የቅዱስ ገብረ ማርያም ቤተክርስቲያን፣ ማይ ማርያም ቤተክርስቲያን፣ ተከዜ ኪዳነምሕረትና መድኃኔዓለም አንድነት ገዳም ከብዙ በጥቂቱ ይጠቀሳሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዳንዶቹ ከ485-536 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ በዐፄ ካሌብ ዘመነ መንግሥት የታነጹ ናቸው፡፡ ሌሎቹንና በሰሜን ላስታ ያሉትን ደግሞ እነ ላሊበላና ይምርሃነ ክርስቶስ አንጸዋቸዋል፡፡

ቅዱስ ላሊበላ እኛ ከምናውቃቸው ከድንቅ ሥነ ሕንፃዎቹ ሥራ በተጨማሪ ከሺህ ዓመታት በፊት በሥዕል፣ በሥነ ጽሑፍ፣ በሃይማኖት፣ በኢኮኖሚ፣ በውጭ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙትና በመሳሰሉት ሁሉ እጅግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ከሺህ ዓመታት በፊት አዳራሾችን፣ ፎቆችን፣ የውስጥ ለውስጥ መተላለፊያዎችን፣ የእንግዳ መቀበያዎችን፣ የሕፃናት ማሳደጊያዎችን፣ የሕሙማን መፈወሻዎችን፣ የሕንፃ መሳሪያዎችን፣ የትምህርት ማዕከሎችን፣ የመደጎሻ ቦታዎችን ያቋቋመ መሆኑን የብራና ገድሉ እንደሚናገር የደብሩ አባቶች ይገልጣሉ፡፡ ወደፊት ተርጎመው እንሚያቀርቡልን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ከዚህ በተጨማሪ የግእዝ ቋንቋን በጽሑፍ አበልፅጎ ያቆየ ባለውለታ ነው፡፡ ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ውጭ ሌሎችንም በርካታ ቤተ መቅደሶች ሠርቷል፤ ከሀገራቸንም አልፎ በሱማሌ ሞቃዲሾ ላይ መቅደሰ ማርያም የተባለች ቤተክርስቲያን ሠርቷል፡፡ ክርስትናን ከግብፅ ምድር ጨርሰው ለማጥፋት ተንባላት በተነሡ ጊዜ ዓባይን ሊያግድባቸው ሲነሣ በብዙ ምልጃና ልመና ስለማራቸው በሀገሪቱ ውስጥ ክርስትና እስካሁን እንዲቆይ የራሱን ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ በአጠቃላይ ቅዱስ ላሊበላ ነቢይም ሆኖ፣ ሐዋርያም፣ ጻዲቅም፣ ሰማዕትም ሆኖ ጥበብ መንፈሳዊንና ጥበብ ሥጋዊን ከእግዚአብሔር ተሰጥቶት ንግሥናንና ክህነትን፣ ቅድስናንና ንጽሕናን በሚገባ አስተባብሮ በማያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅንነት ሲያገለግል ኖሮ ሰኔ 12 ቀን 1197 ዓ.ም ከፈጣሪው ታላቅ ቃልኪዳን ተቀብሎ በዝማሬ መላእክት፣ በመዝሙረ ዳዊት ቅድስት ነፍሱ ከሥጋው ተለይታ ሰማያዊ ክብርን ወርሷል፡፡ ክቡር ሥጋውም ራሱ ባነጸው ቤተ ሚካኤል መቅደስ ሥር በክብር ዐርፏል፡፡

6.መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለቅዱስ ላሊበላ የገባለት ልዩ ቃልኪዳን፡-

 6.1. ወደ ሰማይ ነጥቆ ወስዶት በዙፋኑ ፊት የሰጠው ቃልኪዳን፡- ‹‹ዛሬ በዚህች ቀን ከአንተ ጋር እነሆ ኪዳኔን አጸናሁ፡፡ በጸሎትህ ኃይል ታምኖ በውስጣቸው የሚያመሰግን ትሠራቸው ዘንድ ያላቸው አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የደረሰ ሁሉ አንተን አስቦ ‹አቤቱ ፈጽመህ ይቅር በለኝ› የሚለኝ፣ ‹ይህን የሚያስደንቅ ሥራ በእጁ ስለገለጥክለት ስለ ባሪያህ ስለ ቅዱስ ላሊበላ ብለህ ይቅር በለኝ› እያለ የሚጸልየውን በዚያ ጊዜ እኔ ጸሎቱን እሰማዋለሁ፡፡ ከሕፃንነቱ ጀምሮ የሠራውን ኃጢአት ሁሉ አስተሠርይለታለሁ፤ ከማኅፀነ ዮርዳኖስ እንደ እንደተወለደባት ቀን የነፃ አደርገዋለሁ፡፡ የዕዳ ደብዳቤውንም በእጅህ ትቀደው ዘንድ ለአንተ እሠጥሃለሁ፤ ዕድሜውንም በምድር ላይ አረዝምለታለሁ፤ ቤቱንና ንብረቱን ሁሉ እባርክለታለሁ፤ በተንኮል የሚከራከረው ቢኖር ድል እንዳይነሣው አሠለጥነዋለሁ፤ እግሮቹ እየተመላለሰ ወደ ቤተክርስቲያን የገሠገሠ ሁሉ በኢየሩሳሌም ሰማያዊት በኤዶም ገነት ውስጥ እንዲመላለስ አደርገዋለሁ፤ መባዕ የሚያገባ ሁሉ ጥቂትም ቢሆን ብዙም ቢሆን በእጅህ ከምሠራው ከቤተ መቅደሴ የሚያመጣውን መባዕ ሁሉ ቀኝ እጄን ዘርግቼ ከእጁ ፈጽሜ እቀበለዋለሁ፡፡ ከዕጣንም ወገን በየአይነቱ ያገባ ቢኖር እንደሰው ልማድ ሥጋዬን እንደቀባበት እንደ ኒቆዲሞስ ሽቱ እቀበለዋለሁ፣ በቢታንያ እንደቀባችኝ እንደ ማርያም እንተ ዕፍረት ሽቱ መዓዛውን አሸትለታለሁ፤ ስለ ማርያም እንተ ዕፍረት እስከ ዓለም ዳርቻ ሁሉ የመንግሥቴ ወንጌል በተሰበከበት ስሟን ይጠሩ ዘንድ እንዳዘዝኩ ሁሉ ትጉሃን በሚሆኑ በሰማያውያን መላእክት ከተሞች ስሙን ይጠሩት ዘንድ አዛለሁ፡፡ ለመብራት የሚሆን ዘይት ቢያገባ በይቅርታዬ ዘይትነት ራሱን አወዛዋለሁ፣ ሰውነቱ ለዘለዓለሙ አይሻክርም፣ ከፊቱም የብርሃን መብራት አይጠፋም፡፡ ወደ ሠርግ ቤት ከሚገቡ መብራታቸው ካልጠፋባቸው ከልባሞች ደናግል ጋር በመጣሁ ጊዜ በደስታ ይቀበለኛል፡፡››
6.2. በኢየሩሳሌም ሳለ ጌታችን የስቅለቱን መከራ በራእይ ካሳየው በኋላ የሰጠው ቃልኪዳን፡- ‹‹ለሌሎቹ ጻድቃን ከዚህ ዓለም በሞት በሚለዩበት ወቅት በፍጹም ልቡናቸው እንደሚገባ ያገለገሉኝን ዋጋቸውን ሰጠኋቸው፣ ለአንተ ግን በሞት የምትለይበት ጊዜ ሳይደርስ በሕይወትህ ሳለህ ኪዳንን ሰጠሁህ፡፡ ማደሪያህ ከጳውሎስና ከጴጥሮስ ጋር ይሆናል፡፡ አቀማመጥህ በቀኜ ነው፣ ደቀ መዛሙርቴን በ12 ወንበር ተቀምጣችሁ በ12ቱ ነገደ እስራኤል ትፈርዳላችሁ እንዳልኳቸው አንተም ወንበርህ ከወንበራቸው አያንስም፤ ብርሃንህ ከብርሃናቸው፣ ክብርህ ከክብራቸው አያንስም፤ ኪዳንህም ከሰጠኋቸው ኪዳን አያንስም፤ ርስትህ ዕድል ፈንታህ ከእነርሱ ጋር ነው፡፡ የሰጠሁህን ቃልኪዳንና ገድልህን የሚያቃልል ሁሉ ዕድል ፈንታው ከአንተ ጋር አይሁን፣ ርስት ጉልቱም ከአንተ ርስት ጉልት አይገኝም፤ የጸናሁልህን ቃልኪዳን የማያምን ያ ሰው እኔን ክርስቶስን እግዚአብሔር አይደለም እሩቅ ብእሲ ነው እንጂ እንደሚለኝ ሰው ይሁን፡፡ መጽሐፍህን ሰምቶ የተቀበለ ሁሉ የመንግሥቴን ወንጌል እንደተቀበለ ይሁን፤ አንተን ያከበረ እኔን እንዳከበረ ይሁን፡፡ ደቀ መዛሙርቴን እናንተን የሰማ እኔን የሰማ ነው፣ እናንተን የካደ እኔን የካደ ነው እንዳልኳቸው አሁንም አንተን የሰማ ቃልኪዳንህንም ያመነ እኔን ጌታህን የሰማ ነው እልሃለሁ፡፡ መከራህንና ቃልኪዳንህን የካደ ሰው ቢኖር እኔ በምድር የተቀበልኩትን መከራ እንደ ካደ ሰው ነው፡፡ ወንዶችም ሆኑ ሴቶች በጸሎትህ ኃይል የታመኑ ሁሉ ማደሪያቸው ከአንተ ጋር ይሁን፤ ለቤተክርስቲያኖችህ አምኃ የሰጠ ቢኖር እንደ ደሜ ፍሳሽ እንደ ሥጋዬ ቁራሽ አድርጌ እቀበለዋለሁ፡፡››
3.ቤተ መቅደሶቹን ሠርቶ ከጨረሰ በኋላ ጌታችን የሰጠው ቃልኪዳን፡- ቅዱስ ላሊበላ ጌታችን ባሳየውና ባዘዘው መሠረት አብያተ ክርስቲያናቱን አንጾ ከጨረሰ በኋላ በቀኝና በግራው ዓሥር ዓሥር ኪሎ የሚመዝን የዓለት ድንጋይ ተሸክሞ ለ7 ዓመት ሲጾም ሲጸልይ ከኖረ በኋላ ጌታችን ተገልጦለት በፊት የገባለትን ቃልኪዳን በዚህም ጊዜ በድጋሚ አረጋግጦለታል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ‹‹…ወደ ደጅህ የመጡት ሁሉ አስራት ይሁኑልህ፣ አንተ ከገባህበትም ይግቡ፣ አንተንም ከ12ቱ ሐዋርያት ጋር በፍርድ ቀን 13ኛ አደርግሃለሁ፡፡ ያነጽካቸውን ቤተ መቅደሶች የተሳለመውን ኢየሩሳሌምን እንደተሳለመ አደርግለታለሁ፤ መታሰቢያህን ያደረገውን፣ ገድልህን የጻፈውን ያጻፈውን፣ በዚህ ቦታ ላይ መጥቶ አማልደኝ ያለውን፣ በአማላጅነትህ የተማጸነውን ሁሉ እስከ 15 ትውልድ ምሬልሃለሁ›› ብሎ የመጨረሻውን ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን! እኛንም በአማላጅነታቸው የምንታመን ሁላችንንየመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን እና የቅዱስ ላሊበላን በረከታቸውን ያድለን በጸሎታቸው ይማረን አሜን!!!


 (ምንጭ፡- ገድለ ቅዱስ ላሊበላ፡- የቅዱስ ላሊበላ ደብር በ2003 ዓ.ም ያሳተመው፣ ስንክሳር ዘወርሃ ሰኔ፣ ድርሳነ ሚካኤል ዘወርሃ ሰኔ)





Wednesday, January 30, 2019

ጥር 22-ወበዛቲ ዕለት

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 


ጥር 22-ዓለሙ ሁሉ የእግራቸውን ትቢያ ያህል እንኳን ዋጋ የሌለው የመነኮሳት ሁሉ አባት በገዳም ለሚኖሩ ቅዱሳን እንደ ኮከብ የሚያበሩላቸው ገድል ትሩፋታቸው በቃል ተነግሮ የማያልቅ እጅግ የከበሩ ርዕሰ መነኮሳት አቡነ እንጦንስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል በዓለ ሲመቱ ነው፡፡
ርዕሰ መነኮሳት አቡነ እንጦንስ፡- እንጦንስ አበ መነኮሳት በሌላኛው ስማቸው ‹‹የበረሃው ኮከብ›› እየተባሉም ይጠራሉ፡፡ ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ አቡነ እንጦንስ ገና በ7 ዓመታቸው ነው የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ተምረው አጠናቀው የጨረሱት፡፡ መልካም ትሩፋታቸውንና ታዛዥነታቸውን የልጅ አዋቂ መሆናቸውም በሁሉ ዘንድ በተሰማ ጊዜ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አባ ቲዎናስም የእንጦንስን የልጅነት ጸጋና ዕውቀት ተሩፋታቸውን ሰምተው መልእክተኞችን ልከው አስመጧቸው፡፡ ካስመጧቸውም በኋላ ዲቁና ሲሾሟቸው ‹‹ይህ ሕፃን በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናል፣ ዜናውም በዓለሙ ሁሉ ይዳረሳል›› በማለት ትንቢት ተናግረውላቸዋል፡፡ እንጦንዮስ (እንጦንስ) ግብፃዊ ወላጆቻቸው እጅግ ባለጸጎችና ደጋግ ነበሩ፡፡ ወላጆቻቸው ከሞቱ በኋላ አባ እንጦንስ የወላጆቻቸውን ሀብት ወርሰው ከአንዲት እኅታቸው ጋር መኖር ጀመሩ፡፡
አንድ ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው ወንጌል ሲነበብ ጌታችን ስለሀብታሙ ሰው የተናገረውን ምዕራፍ ሲነበብ አዳመጡ፡፡ ‹‹ልትጸድቅ ብትወድድ ሂደህ ያለህን ሁሉ ሽጥና ለድኆች ስጥ፤ መጥተህም ተከተለኝ በሰማያት መዝገብ ታከማቻለህ›› (ማቴ 19፡21) የሚለውን የጌታችንን ቃል በሰሙ ጊዜ ‹‹ይህ ስለእኔ የተነገረ ቃል ነው›› በማለት ከቤተ ክርስቲያን ወጥተው ወደ ቤታቸው በመሄድ ወላጆቻቸው ሲሞቱ ያወረሷቸውን ብዙ ንብረታቸውን በሙሉ ሸጠው መጸወቱ፡፡ የወረሱትንም 300 ሄክታር ወይም 12 ጋሻ መሬት ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች አከፋፈሉ፡፡ የቀረቻቸውን እኅታቸውንም ወስደው ሴቶች ገዳም አስገቧትና እሳቸውም ከመንደር ወጣ ብለው በመኖሪያ ቤታቸው አጠገብ በብሕትውና ሕይወት ብቻቸውን መኖር ጀመሩ፡፡
እንጦንስ አበ መነኮሳት በአንድ መቃብር ቤት ገብተው ኖሩ፡፡ ሰይጣናትም መጥተው ደብድበው ከመንገድ ላይ ጥለዋቸው ሄዱ፡፡ ከወደቁበት አንስተው ወደ ቤተ ክርስቲያን ወሰዷቸውና ጌታችን ፈወሳቸው፡፡ ተጋድሎአቸውንም እንደገና ጀመሩ፡፡ አሁንም ሰይጣናት በዱር አውሬዎች በአንበሳ፣ በተኩላ፣ በእባብና በጊንጥ እንተመሰሉ እየመጡ ይዋጓቸው ነበር፡፡ በዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ ምግባቸውን ያበስላሉ፡፡ ወደ በዓታቸውም ሰውን አያስገቡም ነበር-በውጭ ሆነው ያነጋግሯቸዋል አንጂ፡፡ እንዲህም ሆነው 20 ዓመት ተቀመጡ፡፡ ጌታችንም ተገልጦላቸው ወጥተው እንዲያስተምሩ አዘዛቸውና ወጥተው ደቀ መዛሙርትን ማፍራት ጀመሩ፡፡ የመከራ ዘመን በመጣ ሰዓት ሰማዕትነትን ለመቀበል ወደ እስክንድርያ ጎዳናዎች ወጥተው ታዩ፡፡ መኰንኑም እንዳይታዩ ብሎ መከራቸው ግን እሽ አላሉትም፡፡ ሰማዕትነት የእሳቸው ክፍል አልነበረምና ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ከተገደለ በኋላ በመልአኩ ትእዛዝ ወደ በዓታቸው ተመለሱ፡፡ ከዐረብ ነጋዴዎች ጋር ወደ ሩቅ ቦታ ሄደው በበረሃ ብቻውን መኖር ጀመሩ፡፡
አባ እንጦንስ በረሃ ለበረሃ ሲንከራተቱ አጋንንት ክፉኛ ይዋጓቸው ነበር፡፡ በረሃነቱም ጽኑ ነው፣ ከሐሩሩ ጽናት የተነሣ በቀትር ጊዜ ከደንጊያ ላይ ተልባ ቢያሰጡ ይቆላል፡፡ እርሳቸውም ከዚያ ሄደው ሲጋደሉ አጋንንት ጾር በማንሳት ግማሾቹ ‹‹ከዚህ በረሃ እንደምን ደፍረህ መጣህ?›› ሲሏቸው ሌሎቹ ደግሞ ተቀብለው ‹‹አዳም ከወጣበት ገነት እገባ ብሎ ነው…›› እያሉ ይዘብቱባቸው ነበር፡፡ አባ እንጦንስ ግን በፍጹም ትሕትና ይታገሷቸዋል፡፡ ‹‹መሆንማ ይሆን ብላችሁ ነውን? እናንተ ብዙ እኔ አንድ ብቻዬን፤ እናንተ ረቂቃን እኔ ግዙፍ፡፡ እናንተ ኀያላን እኔ ደካማ በኀይለ ክርስቶስ ብችላችሁ ነው እንጂ ያለዚያስ አልችላችሁም›› እያሉ በትሕትና ሲዋጓቸው ኖሩ፡፡ ከዕለታት ባንድ ቀን ‹‹ይኸን የአጋንንት ጾር አልቻልሁትም ልሂድ እንጂ›› ብለው ሲያስቡ አደሩ፡፡ በማለዳም ተነሥተው በትራቸውን ይዘው ከደጃፋቸው ላይ ቆሙ፡፡ እንዳይቀሩም ጾሩ ትዝ እያላቸው እንዳይሄዱም በዓታቸው እየናፈቃቸው አንድ እግራቸውን ከውስጥ፤ አንድ እግራቸውን ከአፍአ አድርገው ሲያወጡ ሲያወርዱ መልአኩ የሰሌን ቆብ ደፍቶ፤ የሰሌን መቋረፊያ ለብሶ፤ የሰሌን መታጠቂያ ታጥቆ ብትን ሰሌን ይዞ መጣ፡፡ ምን ሊያደርግ ይሆን? ሲሉም ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ ቆመ፡፡ ወዲያው ጸሎተ ወንጌልን፤ ነአኲቶን፤ ተሰሃለኒን፤ ደግሞ መጀመሪያ ለሥላሴ እጅ ነሳ፡፡ ከዚያ በኋላ አንድ አቡነ ዘበሰማያት ሰላሳ ስድስት ሰጊድ አድርሶ በመጨረሻ አንድ ጊዜ እጅ ነሥቶ ተቀመጠ፡፡ ወዲያው ያን ብትን ሰሌን አቅርቦ ይታታ ጀመር፡፡ ‹‹እንጦንስም እንግዲህማ የዚህን ፍጻሜ ሳላይ እንዴት እሄዳለሁ?›› ብለው ተቀምጠው ይመለከቱት ጀመር፡፡ ሰለስት ሲሆን ደግሞ ተነሥቶ አቡነ ዘበሰማያቱንም ሰጊዱንም ያንኑ ያህል አደረሰው፡፡ የቀሩትንም የሰዓቱንም የሠርኩንም እንደዚሁ አድርጎ አሳያቸው፡፡ ‹‹እንጦኒ ሆይ እንደዚህ ሥራ፤ ይህንን ከሠራህ ከአጋንንት ጠብ ትድናለህ›› አላቸው፡፡ እርሳቸውም የአጋንንትን ጦር መከላከያውን ሁሉ መልአኩ ባሳያቸው መሠረት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እንዲሁ የሚሠሩ ሆኑ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ስንፍናና የሰይጣን ውጊያ ወደሳቸው አልመጣም፡፡
ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም ከአባ እንጦንስ ይባረክ ዘንድ ብዙ ጊዜ ደብዳቤ ጻፈላቸው፡፡ እርሳቸውም ቸል ባሉት ጊዜ ልጆቻቸው ደግ ንጉሥ መሆኑን ስለነገሯቸውና ስለለመኗቸው አባ እንጦንስ ጽፈው በደብዳቤ ባርከውታል፡፡ የአፍርንጊያው ንጉሥም መጥተው እርሱንና ሠራዊቱን ሁሉ እንዲባርኳቸው በክርስቶስ መከራዎች አማጽኖ ደብዳቤ ጻፈላቸው፡፡ ጌታችንንም በጸሎት ሲጠይቁ ደመና መጥታ ወስዳ አደረሰቻቸውና ንጉሡንና ሕዝቡን ሁሉ ባርከዋቸዋል፡፡
አባታችን ሠላሳ ዓመት በሞላቸው ጊዜ ጌታችን በዕለተ ዓርብ የለበሰውን ልብስ አልብሷቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አባ እንጦንስ የአክሊለ ሦክ ምሳሌ የሆነውን ቆብን፤ የከለሜዳ ምሳሌ የሆነውን ቀሚስ፤ የሀብል ምሳሌ የሆነውን ቅናትን፤ እንዲሁም ሥጋ ማርያምን ከመልአክ ከተቀበሉ በኋላ ‹‹በዚህ ዓለም እኔ ብቻ ነኝን ወይስ ሌላም አለ?›› ብለው በጸሎት ወደ እግዚአብሔር አመለከቱ፡፡ ጌታችንም ‹‹አለ እንጂ፣ አንድ ጊዜ ተራምዶ ሁለተኛውን ሳይደግም የሚሠራውን ሥራ ዓለሙ ሁሉ ቢሰበሰብ የማይሠራው፣ በጸሎቱ ዝናም የሚያዘንም፣ ፀሐይን የሚያወጣ፤ እንደዚህ ያለ ወዳጅ አለኝ›› አላቸው፡፡ አባታችንም ‹‹ይኽን ሰው ለማየት ልሂድን ልቅር? ቢሉት እንዲሄዱ ፈቀደላቸው፡፡
የታዘዘ መልአክም እየመራ አባ ጳውሊ ካሉበት በዓት አደረሳቸው፡፡ እርሳቸውም ከአባ ጳውሊ ጋር ብዙ መንፈሳዊውን ነገር ተጨዋወቱ፡፡ ተጨዋውተውም ሲያበቁ አባ ጳውሊ ለአባ እንጦንስ ለብቻቸው በዓት ሰጧቸው፡፡ እንጦንዮስም ከዚያ ሆነው ጸሎታቸውን ሲያደርግ ዋሉ፡፡ ወትሮ ለአባ ጳውሊ ግማሽ ሰማያዊ ኅብስት ይወርድላቸው የነበረ ሲሆን ማታ ግን አንድ ሙሉ ኅብስት ወረደላቸው፡፡ አባ ጳውሊም በፈቃደ እግዚአብሔር ወደ እርሳቸው መምጣታቸውን ያን ጊዜ ዐወቁ፡፡ ወዲያው ያን ኅብስት ከሁለት ከፍለው እኩሌታውን ለራሳቸው አስቀርተው እኩሌታውን ለአባ እንጦንስ ሰጧቸው፡፡ ያን ተመግበው ሌሊት ሁለቱም በየሥራቸው ክብራቸው ተገልጾ ሲተያዩ አድረዋል፡፡ ጳውሊ ዓሥር ጣቶቹን እንደ ፋና ሆነው እያበሩለት አራቱን ወንጌል ሲያደርስ እንጦንዮስም እንደ ዓምደ ብርሃን ተተክለው ሲያበሩ ተያይተዋል፡፡ በዚያች ሌሊት ከዚያ ቦታ ጨለማ ጠፍቶ አድሯል፡፡
በነጋው ሠለስት እላፊ ሲሆን ጸሎታቸውን አድርሰው ሲያበቁ ተገናኝተው ሲጨዋወቱ ጳውሊ እንጦንዮስ ያረጉትን ቆብ አይተው ‹‹ይህ ከማን አገኘኸው?›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ‹‹እርሱ ባለቤቱ ሰጠኝ›› አሉ፡፡ ጳውሊም የጌታችንን ቸርነት ያደንቁ ጀመር፡፡ እንጦንዮስም ‹‹እስኪ በኔ ብቻ የሚቀር እንደሆነ ለሌላም የሚያልፍ እንደሆነ አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ሲያመለክቱ ወዲያው ተገለጸላቸውና ደስ አላቸው፡፡ ‹‹ምን አየህ?›› ቢሏቸው ‹‹ነጫጭ ርግቦች በጠፈር መልተው አንተ እየመራሃቸው ተከትለውህ ሲሄዱ አየሁ›› አሏቸው፡፡ ‹‹ይህስ ምንድን ነው?›› ቢሏቸው ‹‹እሊህማ በዚህ በቆቡ የምትወልዳቸው ንጹሐን ጻድቃን ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ ‹‹ሁለተኛ አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ካመለክቱ በኋላ አዝነውና ተከፍተው ተመለከቷቸው፡፡ ‹‹ምነው?›› ቢሏቸው ‹‹በክንፋቸው ጥቁር ተቀላቅሎባቸው አየሁ›› አሉ፡፡ ‹‹ምንድን ናቸው?›› ቢሏቸው ‹‹ጽድቅና ኀጢአት እየቀላቀሉ የሚሠሩ ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ካዘኑ በኋላ ‹‹ሦስተኛም አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ አባ ጳውሊም ለሦስተኛ ጊዜ ካመለከቱ በኋላ በድንጋጤ ቃላቸውን ከፍ አድርገው ጮኹ፡፡ አባ እንጦንስም ‹‹ምነው?›› ቢሏቸው አባ ጳውሊ እንዲህ አሉ፡- ‹‹ነገር ግን በመጨረሻ ዘመን የሚነሡቱ እንደ ቁራ ጠቁረው አየሁዋቸው›› አሉ፡፡ ‹‹ምንድን ናቸው?›› ቢሏቸው ‹‹ሀሳሲያነ ሢመት (ሹመት ፈላጊዎች)፣ መፍቀሪያነ ንዋይ (ገንዘብ የሚወዱ) እና ከመኳንንትም ጋር በጥዋት ማዕድ የሚቀመጡ በፍጻሜ ዘመን የሚነሡ ኀጥአን ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ ይህን ጊዜ አባ እንጦንስ ‹‹ያለ ንስሓ ባይጠራቸው እስኪ አመልክትልኝ›› አሉ፡፡ አባ ጳውሊም አመለከቱ ነገር ግን የዚህ ምላሽ አልመጣላቸውም፡፡
ከዚህ በኋላ አባ ጳውሊ ስለ ቆቡ አባ እንጦንስን ‹‹እንግዲህ ይህን ከራስህ ያደረግኸውን ለኔ ስጠኝ ላንተ ሌላ ሠርተህ አድርግ›› አሏቸው፡፡ አባ እንጦንስም ‹‹ይህንንስ እንዳልሰጥህ ከባለቤቱ ተቀብዬዋለሁ፡፡ ነገር ግን ሥራውን ለምጄዋለሁ ሌላ ሠርቼ ላምጣልህ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ‹‹እንግዲያስ አትዘግይ ቶሎ ሠርተህ አምጣልኝ›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ሠርተው ይዘው ሲመጡ ጳውሊ ዐርፈው ነፍሳቸውን መላእክተ ብርሃን ይዘዋት ሲያርጉ ተመለከቱ፡፡ መላእክቱም ‹‹ጳውሊ ዐርፏልና ሂደህ ቅበረው›› አሏቸው፡፡ ‹‹ይህንሳ የያዝኩትን ቆብ ልተወውን?›› ቢሏቸው፡፡ ‹‹አትተው አድርግለት›› ብለው መለሱላቸው፡፡ ይህም በምንኩስና የሠሩት ሥራ ከንቱ እንዳይደለ ለማጠየቅ ነው፡፡ አባ እንጦንስም ቢሄዱ አባ ጳውሊ መጽሐፋቸውን ታቅፈው፣ አጽፋቸውን ተጎናጽፈው፣ ከበዓታቸው ዐርፈው አገኟቸው፡፡ ከራስጌአቸው ቆመው ሲያለቅሱ ሁለት አንበሶች መጡ፡፡ ‹‹የመቃብሩን ነገር እንደምን ላድርግ?›› እያሉ ሲጨነቁ አንበሶቹ በእጃቸው እንደመጥቀስ አድርገው የመቃብራቸውን ቦታ አሳዩአቸው፡፡ እርሳቸውም ለክተው ሰጧቸው፡፡ አንበሶቹም ከቆፈሩላቸው በኋላ አባ ጳውሊን ቀብረው ‹‹እንግዲህ ከዚህ እኖራለሁ›› ብለው አሰቡ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ‹‹በዚህ መኖር አይሆንልህም ሂድ›› አላቸው፡፡ አጽፋቸውንና መጽሐፋቸውን ይዘው ሄደው እስክንድርያ ደርሰው ለሊቀ ጳጳሱ ለቅዱስ አትናቴዎስ ያዩትንና የሆነውን ሁሉ ነገሯቸው፡፡ አቡነ አትናቴዎስም ‹‹ልሄድና ከዚያ ልኑር?›› ሲሏቸው ‹‹አይሆንልህም አትሂድ እኔም አስቤ ነበር ነገር ግን የማይሆንልኝ ሆኖ መጣሁ እንጂ›› አሏቸው፡፡ ‹‹ባይሆን ለበረከት ያህል አጽፊቱን ጥለህልኝ ሂድ›› ብለው ሲለምኗቸው ትተውላቸው ሄዱ፡፡
አባ እንጦንስ ራሳቸውን ዝቅ በማድረግና በፍጹም ትሕትናቸው ይታወቃሉ፡፡ ምንም እንኳ ታላቅና በትሩፋት የበለጸጉ ቢሆኑም በጳጳሳትና በካህናት ፊት ራሳቸውን በትሕትና ዝቅ አድርገው እጅ ይነሷቸው ነበር፡፡ ዲያቆንም ቢሆን ወደ እርሳቸው በመጣ ጊዜ ከእርሱ ጠቃሚ ነጥብን ለማግኘት ይሞክራሉ፤ ላገኙትም ዕውቀት ሳያመሰግኑ አያልፉም፡፡ የእርሳቸውንም ምክር ሽተው ለሚመጡ ሁሉ እጅግ ጠቃሚ የሕይወት ምክሮችን ይሰጣሉ፡፡ ዓለምን ንቆ ገንዘብ ስለመውደድ ከመነኮሰ በኋላ ለድሆች አከፋፍሎ ለራሱም ጥቂት ንብረት ያስቀረ አንድ ወንድም ወደ አባ እንጦንስ መጣ፡፡ አባ እንጦንስም ይህን ካወቁ በኋላ እንዲህ አሉት፡- ‹‹መነኩሴ ለመሆን ከፈለግህ ወደ መንደር ሂድና ጥቂት ሥጋ ገዝተህ ራቁትህን በሰውነትህ ላይ ተሸክመህ ተመለስና ወደእኔ ና›› አሉት፡፡ ያም ወንድም ይህን ባደረገ ጊዜ ወፎችና ውሾች በሰውነቱ ያለውን ሥጋ ለመብላት ሲሉ በሰውነቱ ላይ በማንዣበብ እየሞነጨሩ አቆሰሉት፡፡ በደረሰም ጊዜ አባ እንጦንስ እንዳዘዙት ማድረጉን ጠየቁት፡፡ እርሱም የቆሰለውን ሰውነቱን ባሳያቸው ጊዜ እንጦንስ ‹‹ዓለምን ከናቁ በኋላ ገንዘብ የሚመኙትም እንደዚሁ በአጋንንት ይገደላሉ›› አሉት፡፡
አቡነ እንጦንስ ዕረፍታቸው በደረሰ ጊዜ ዕለተ ሞታቸውን ዐውቀው ደቀ መዛሙርቶቻቸውን ሲሰናበቱ እንዲህ ብለው መከሯቸው፡- ‹‹ይህ ከእናንተ ጋር የማደርገው የመጨረሻው ግንኙነት ነው፡፡ በዚህም ሕይወት ዳግመኛ እንዳንተያይ ዐውቃለሁ፡፡ አሁን እኔ የምሞትበት ጊዜ ነው፡፡ ከጥረታችሁ ግዴለሽ አትሁኑ፡፡ በብሕትውና ሕይወት ፍጹም ተስፋ አትቁረጡ፡፡ ዕለት ዕለት እንደምትሞቱ ሆናችሁ ኑሩ፡፡ አስቀድሜ እንደተናገርኩት ነፍስን ከርኩስ አሳቦች ለመጠበቅ በሥራ ትጉ፡፡ ቅዱሳንን ምሰሉ፡፡ ቅድስና የሌለውን የስንፍና ትምህርታቸውን ታውቃላችሁና ወደ መናፍቃን አትቅረቡ፣ ኑፋቄያቸው ለማንም ግልጽ ነውና፡፡››
ከዚህም በኋላ ጊዜ ዕረፍታቸው ሲደርስ ጌታችን ተገልጦላቸው ቃልኪዳን ገባላቸው፡፡ እርሳቸውም ለልጃቸው ለመቃርስ ስለ ወደፊቱ መነኮሳትና ገዳማት ትንቢትን ነገሩት፡፡ ወደፊት መነኮሳት ከበዓታቸው እየወጡ በዓለም እንደሚቅበዘበዙ ተናገሩ፡፡ ዕረፍታቸው በደረሰ ጊዜ በትራቸውን ለልጃቸው ለመቃርስ፣ ምንጣፋቸውን ለአቡነ አትናቴዎስ፣ የፍየል ሌጦ አጽፋቸውን ልጃቸው ለሊቀጳጳሱ ለሰራብዮን እንዲሰጡ አዘዙና በ120 ዓመታቸው በ356 ዓ.ም ጥር 22 በታላቅ ክብር ዐረፉ፡፡
ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን አሜን!
+ + + 


ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል፡- ኢዮር፣ ራማ እና ኤረር የተባሉ ሦስት የመላእክት ከተሞች አሉ፡፡ እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክት ከፈጠራቸው በኋላ በነገድ 100 በአለቃ 10 አድርጎ በሦስቱ ሰማያት አስፍሯቸዋል፡፡ ኢዮርን በ4፣ ራማን በ3፣ ኤረርንም በ3 ከፍሎ ነው በዓሥሩ ከተማ ያሰፈራቸው፡፡
በዚህም መሠረት ኢዮርን ላይና ታች አድርጎ በ4 ከተማ ከፍሏታል፡፡ በእርሷ ያሉትን መላእክትን በ40 ነገድ 4 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያው ነገድ ‹‹አጋእዝት›› ይባላሉ፡፡ አለቃቸው ሣጥናኤል ነበር፤ እርሱም የመላእክትን ሁሉ ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ያሳርግ ነበር፡፡ ከክብሩ ሲዋረድ ቅዱስ ሚካኤል በምትኩ ተሹሞበታል፡፡ ሁለተኛው ነገድ ‹‹ኪሩቤል›› ይባላሉ፡፡ እነርሱም መንበረ ሥላሴን ይሸከማሉ፡፡ የቀሳውስት አምሳል ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ሰብና ገጸ አንበስ ናቸው፡፡ በሦስተኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ሱራፌል ይባላሉ፡፡ የዲያቆናት አምሳል ናቸው፡፡ በትንቢተ ኢሳያስ በምዕራፍ 6 ላይ የተገለጹትና ኢሳያስን ከለምጹ እንዲፈወስ ያደረጉት ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ላህምና ገጸ ንስር ናቸው፡፡ (በነገራችን ላይ ‹‹ከሩቤል›› ወይም ‹‹ሱራፌል›› የሚባሉ የግለሰብ መጠሪያ ስሞች ስህተት ናቸው፡፡ አንደኛ እነዚህ ስሞች የብዙ መላእክት መጠሪያን የሚወክሉ ናቸው፡፡ ለአንዱ ሲሆን ‹‹ኪሩብ፣ ሱራፊ›› ይባላል፡፡ ‹ኪሩቤል› ወይም ‹ሱራፌል› ማለት ግን የብዙ ቁጥራቸው መጠሪያ ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የቅዱሳን መላእክትን ስም እንዳለ በቁሙ ወስዶ ለግል መጠሪያ ስም ማዋል ተገቢ አይደለም፡፡ ‹‹ወለተ ሚካኤ፣ ክብፈ ገብርኤል….›› እየተባሉ ይሰየማሉ እንጂ ቀጥታ ‹ሚካኤል›፣ ‹ገብርኤል› እያሉ ሰዎችን መሰየም ስህተት ነው፡፡ 4ኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ኃይላት ይባላሉ፡፡ የእሳት ሰይፍ ይዘው በሥሉስ ቅዱስ ፊት የሚቆሙ ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት የዛሉና የደከሙ ክርስቲያኖችን የሚያበረታቱ ናቸው፡፡ አለቃቸውም ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡)
ዳግመኛም እግዚአብሔር በራማ ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹አርባብ›› ይባላሉ፡፡ የሥላሴ እልፍኝ አስከልካዮች ናቸው፡፡ የእግዚአብሔርን መንበር በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ ሁለተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹መናብርት›› ይባላሉ፡፡ ለእግዚአብሔርን እጅግ ቅርብ የሆኑ ናቸው፡፡ የመብረቅ ጋሻቸውን የእሳት ጦራቸውን ይዘው የሥላሴ ጋሻ ጃግሬዎች ሆነው በተጠንቀቅ ይቆማሉ፡፡ የሰውን ችግር ለእግዚአብሔር ያቀርባሉ፡፡ መዝ 88፡6፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሦስተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹ሥልጣናት›› ይባላሉ፡፡ መላውን ፍጥረት ለመጠበቅ ሥልጣን የተሰጣቸውና የምጽአት ዕለት አዋጅ ነጋሪዎች ናቸው፡፡ ዳን 12፡1፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሱርያል ነው፡፡
ዳግመኛም እግዚአብሔር በኤረር ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹መኳንንት›› ይባላሉ፡፡ የስላሴ የእሳት ባለ ቀስት ናቸው፡፡ የሰው ልጅ ልዩ ጠባቂዎች ናቸው፤ በተለይ በአደጋ ጊዜ ሎጥን እንዳዳኑት ፈጥነው ይደርሳሉ፡፡ በዕለተ ምጽዓት የሰውን ሁሉ ዐፅም ሰብስበው ለትንሣኤ ዘጉባኤ ያበቃሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሰዳካኤል ነው፡፡ ሁለተኛዎቹ ‹‹ሊቃናት›› ይላሉ፡፡ የሥላሴ የእሳት ፈረሶች ናቸው፡፡ በእሳት ፈረስ ይመላለሳሉ፡፡ እነዚህም 24ቱ ካህናተ ሰማይ ሲሆኑ አለቃቸው ቅዱስ ሰላታኤል ነው፡፡ በኤረር ከተማ የሰፈሩት ሦስተኛዎቹ ‹‹መላእክት›› ይባላሉ፡፡ ፍጥረትን ሁሉ የሚጠብቁ ናቸው፡፡ አለቃቸው ቅዱስ አናንኤል ነው፡፡ በእነዚህ የማይጠበቅ ፍጥረት የለም፡፡ ከአዝርእት ጀምሮ ሁሉን ይጠብቃሉ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙ 7 መላእክትን አየሁ›› (ራዕ 8፡2) እንዳለ ሊቃነ መላእክት በቁጥር 7 ናቸው፡፡ እነርሱም፡- ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል፣ ቅዱስ ራጉኤል፣ ቅዱስ ዑራኤል፣ ቅዱስ ፋኑኤል እና ቅዱስ አፍኒን ናቸው፡፡
‹‹ዑራኤል›› የሚለው ስም ‹ዑር› እና ‹ኤል› ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል›› ማለት ትርጉሙ ‹‹የብርሃን ጌታ፣ የአምላክ ብርሃን›› ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዑራኤል ከ7ቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነው፡፡ በመሆኑም መጽሐፈ ሄኖክ እንደሚገልጸው መባርቅት ለጥጋብና ለበረከት እንዲበርቁ ነጎድጓድም ለሰላም እንዲሆን ያሰማራል፡፡ ምሥጢረ ሰማይንና ሰማያዊውን ዕውቀት ሁሉ ለሄኖክ የገለጸለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ የፀሐይን፣ የጨረቃን፣ የከዋክብትንና የሰማይ ሠራዊትን ብርሃንን የሚመራው ይኸው ገናና መልአክ ነው፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ 28፡13፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሆኖ በተሰቀለ ጊዜ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨው ይኸው ገናና መልአክ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ዕውቀት ተሠውሮበት ለነበረው ለኢትዮጵያዊው ሊቅ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም በእመቤታችን ትእዛዝ ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል የተባለ መልአክ ሊረዳኝ መጣ፡፡›› መጽሐፈ ዕዝራ 2፡1፡፡ አምላካችን እግዚአብሔር የሕይወትና የይቅርታ ዝናም በምድራችን ላይ ያዘንብ ዘንድ እንዲሁም የእርሻችንን አዝመራ በዝናም አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ለምግብነት እንዲበቃ ከፈጣሪ ዘንድ ምሕረትን የሚለምን መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ሊቁ አባ ጊዮርጊስም በመልአኩ አማላጂነት እጅግ ብዙ ድርሰቶችን የደረሱት መልአኩ ጽዋ ሕይወትን ካጠጣቸው በኋላ ነው፡፡ በመጀመሪያም አባ ጊዮርጊስ የተወለዱት በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት ነው፡፡ በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ የተመሠረቱ አብዛኞቹ ቅዱሳት ገዳማት በቅዱስ ዑራኤል መሪነት ነው፡፡ ድርሳኑ ላይ የማይጠቅሳቸው የሀገራችን የከበሩ ቅዱሳት ገዳማትና ቅዱሳን ነገሥታት የሉም፡፡
የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክን ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ስትሰደድ መንገድ እየመራ ወደ ግብጽ እና ወደ አገራችንን ኢትዮጵያ ያመጣቸው ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ እመቤታችንን ከተወደደ ልጇ ጋር በደመና ጭኖ መላ ኢትዮጵያን ካስጎበኛት በኋላ ቅድስት አገራችንን ለእመቤታችን የዓሥራት አገር እንድትሆን ያደረገው መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል በዓመት 3 ዓበይት በዓላት አሉት፡፡ ጥር 22 በዓለ ሲመቱ ነው፡፡ መጋቢት 27 የጌታችንን ክቡር የሆነ ወርቀ ደሙን ለዓለም የረጨበት ነው፡፡ ሐምሌ 22 ቀን ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበትና ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል የዕውቀትን ጽዋ ያጠጣበት ዕለት ነው፡፡
የሊቀ መላእክት የቅዱስ ዑራኤል ጥበቃው አይለየን! በጸሎቱ ይማረን !

ጥር 21-እረፍታ ለእግዚእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈሰ ቅዱስ ስም አሜን 
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 
ጥር 21-እረፍታ ለእግዚእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ


ከመጽሐፈ ተአምሯ፡- እመቤታችን ከዚህ ዓለም ታልፍ ዘንድ የጸለየችው ጸሎት ይህ ነው፡- ‹‹አቤቱ ቸር ጌታዬ ሆይ! ከዚህ ሑከትና ኀዘን ከመላበት ዓለም ደገኛውን መልአክህን ልከህ ወደኝ› ስትል በጸለየች ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተገለጸላት፡፡ እንዲህም እያለች ስትጸልይ ሰማይ ተከፈተ፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ወደ እመቤታችን ወርዶ ‹ጸጋን የተመላሽ ሆይ! ደስ ይበልሽ› በማለት የደስታ መልእክት ነገራት፡፡ ዳግመኛም ‹‹እነሆ ጸሎትሽ ከአንቺ ከተወለደው ከእግዚአብሔር ዘንድ ደረሰ፡፡ እንደፈቃድሽ ከዚህ በኃላፊው ዓለም ወደ ዘላለም ሕይወት ትሄጂ ዘንድ ልመናሽ ተሰምቶልሻል›› አላት፡፡ 
እመቤታችንም ይህንን ነገር ከመልአኩ በሰማች ጊዜ ወደ በዓቷ ተመለሰችና ከዚያ የሚያገለግሏትን ደናግል ሰብስባ ‹አይሁድ ሁልጊዜ የልጄን መቃብር ይጠብቃሉና ስለዚህ የእኔን ከዚያ መገኘት አንድ ቀን ይገለጽላቸውና ከዚያ መግባት ይከለክሉኛል ብዬ ፈራሁ፡፡ ስለዚህ ከዛሬ ጀምሮ ራሳችሁን ችላላችሁ በሰላም ትኖራላችሁ እኔ ወደ ቤተልሔም እሄዳለሁና› አለቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ሁሉም በአንድነት ቃላቸውን አስተባብረው ‹ከአንቺ ጋር እንሄዳለን፡፡ ስለ አንቺ እናት አባታችንን፣ እኅት ወንድሞቻችንን ያለንን ሁሉ ትተን ተከትለንሻልና እነሆ አሁንም አንቺ ከሄድሽበት እኛም አብረንሽ እንሄዳለን፣ ባለ ዘመናችን ሁሉ ከአንቺ አንለይም› አሏት፡፡ እመቤታችንም በዚያን ጊዜ ይዛቸው ወደ ቤተልሔም ሄደች፣ በዚያም ተቀመጠች፡፡ እንዲህም ያለቻቸው ስለ አይሁድ ፍራቻ ሳይሆን ከዚህ ከኃላፊው ዓለም በሞት የመለየቷ ጊዜ ስለመድረሱ ነበር፡፡ እናንት የፍቅሯን ፈለግ የተከተላችሁና በፍቅሯ ቀምበር የተጠመዳችሁ የወንጌል ልጆች ሆይ እንግዲህ እመቤታችን በቤተልሔም ተቀምጣ ሳለች መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከዚህ ዓለም በሞት የምትለይበትን ጊዜ በክብር እንደነገራት አስተውሉ፡፡ ልመናዋ ክብሯ ለዘለዓለሙ በዕውነት ይደርብን፡፡ 
እረፍታ ለእግዚእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ፡- በ50 ዓ.ም ገደማ በዕለተ እሑድ ጌታችን እልፍ አእላፍ መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ ‹‹እናቴ ሆይ! ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍሽ መጣሁ›› አላት፡፡ እመቤታችንም ‹‹ልጄ ሰማይና ምድር የማይወስኑህን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኔ ተሸክሜ፣ በድንግልና ወልጄህ እሞታለሁን?›› አለችው፡፡ ጌታችንም በሲኦል የሚሠቃዩ ነፍሳትን አሳያትና ‹‹እናቴ ሆይ! ሞትሽ ለእኒህ ቤዛ ይሆናቸዋል›› አላት፡፡ ለፍጥረታት ሁሉ እጅግ የምትራራ እመቤታችንም ‹‹እነዚህን ከማርክልኝስ ይሁን ልሙት›› አለችው፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ቅድስት ነፍስዋን ከክብርት ሥጋዋ ለይቶ በዝማሬ መላእክት አሳረጋት፡፡ ደቀመዛሙርቱንም ከያሉበት በደመና ጠቅሶ ካለችበት አድርሶ ‹‹እመቤታችሁን ቅበሩ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ይዘዋት ወደ ጌታ ሰማኔ ወሰዷት፡፡ 
አበው ‹‹እመቤታችን ሆይ! ሞትሽ ሠርግን ይመስላል›› እንዳሉት የእመቤታችን እረፍት እንባ መራጨት፣ ጠጉር መንጨት፣ ደረት መድቃት እንዳለበት የሰው ሞት አልነበረም፡፡ ይልቁንም አንደ ሠርግ ቤት ቅዱሳን መላእክት በውዳሴ፤ በማህሌት፣ በዝማሬ፣ በምስጋና ወደ ሰማይ ሸኟት እንጂ፡፡ ቅዱስ ያሬድም ‹‹እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ከፍ ከፍ አለች፤ በዚያም ከልጇ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች›› በማለት ዘምሯል፡፡ የእመቤታችን ሥጋዋ ከጌቴሴማኔ ወደ ገነት መፍለሱን አስቀድሞ አባቷ ቅዱስ ዳዊት በትንቢት ሲናገር ‹‹አቤቱ ወደ እረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት›› በማለት ተንብዮዋል፡፡ መዝ 131፡8፡፡ ይህም ‹‹ፈጣሪዬ ሆይ ምእመናንን ወደምታሳርፍበት ወደ መንግሥተ ሰማያት የመቅደስህን ታቦት ድንግል ማርያምን ይዘህ ተነሥ›› ሲል ነው፡፡ ይህም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም 64 ዓመት በዚህ ዓለም ከኖረች በኋላ ነብሷ ከሥጋዋ ተለይቶ እንደ ልጅዋ ትንሣኤ መነሣቷን የሚያመለክት ነው፡፡ ‹‹ታቦት›› ያላትም ማደሪያው ስለሆነች ነው፡፡
ጠቢቡ ሰሎሞን በምሳሌ ሲናገር «ወደጄ ሆይ ተነሺ፣ ውበቴ ሆይ ነይ፡፡ እነሆ ክረምት አለፈ፣ ዝናቡም አልፎ ሄደ፣ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፣ የዜማም ጊዜ ደረሰ፣ የቁርዬውም ቃል በምድራችን ተሰማ፡፡ በለሱ ጎመራ ወይኖችም አበቡ መዐዛቸውንም ሰጡ ወዳጄ ሆይ ተነሺ፤ ውበቴ ሆይ ነይ» አለ፡፡ መኃ 2፡10-14፡፡ ይህ ኃይለ ቃል ሲተረጎም በውስጡ ብዙ ምሥጢራዊ ነገሮችን ያያዘ ነው፡፡ «በክረምትና በዝናብ» የተመሰሉ የእመቤታችን መከራዎች ናቸው፡፡ የመከራሽ ጊዜ አልፏል ሲላት «አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ» ማለቱ ከልጅሽ እግር ሥር ቁጭ ብለው ተምረው ወንጌልን የተቀበሉ ሐዋርያት አንቺን በእናትነት የተረከቡ የሐዋርያት ድምፅ ወይም ስብከት በምድር ሁሉ መሰማቱን ያጠይቃል፡፡
ጠቢቡ ሰሎሞን «የዜማ ጊዜ ደረሰ» ያለው የመከሩን ወቅት ነው፡፡ መከር የፍሬ ጊዜ እንደመኖኑ ሐዋርያት የዘሩት ዘር ማለትም ስብከታቸው ፍሬ አፈራና ክርስቲያኖች በዙ፤ «በለሱ ጎመራ» በጎ ምግባር የሌላቸው ሰዎች በሐዋርያት ስብከት ተምረው ምግባር መሥራት ጀመሩ፤ «ወይኖች አብበዋል መዐዛቸውንም ሰጥተዋል» በመላው ዓለም ያሉ ምዕመናን በሃይማኖት ማበብ፣ መዐዛ ምግባራቸውን ማቅረብ መስጠት ጀመሩ በማለት ሊቃውንት አባቶች ምሥጢሩን ያብራሩታል፡፡ በዚህ ትርጓሜ ‹‹ወደጄ ሆይ! ተነሽ›› እያለ የሚናገረው ተወዳጁ ልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ድንግል ማርያምን በመለኮታዊ ስልጣኑ ከሙታን ለይቶ ማስነሣቱን ሲያስረዳን ነው፡፡ 
ስለዚህ ድንቅ ምስጢር ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት›› (መዝ 131፡8) ብሎ የተናገረው ትንቢት በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና የጸናች የእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ዕረፍትና ትንሳኤ እንዲሁም ፍልሰት (ዕርገት) ከማሳየቱም በተጨማሪ የአምላክ እናት በልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት በክብር መኖሯንም በግልጽ ያስረዳል ያስገነዝባል፡፡ ‹‹በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች›› (መዝ 44፡9) የሚለውን የቅዱስ ዳዊት ትንቢታዊ ቃል ሊቃውንት አባቶች በተለይም የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መተርጉማን ‹‹ንግሥተ ሰማይ ወምድር ድንግል ማርያም በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና›› ተሸልማና አጊጣ በሰማያዊው ዓለም በልጇ መንግሥት በክብር መኖሯን የሚያመለክት መሆኑን አስረግጠው አስረድተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ሰማያዊው አባታቸውን እግዚአብሔርን ‹‹አቡነ ዘበሰማያት፤ በሰማያት የምትኖር አባታችን›› እያሉ ዘወትር ሲያመሰግኑ፤ በአንጻሩ ደግሞ መንፈሳዊት እናታቸውን ድንግል ማርያምን ‹‹በሰላመ ቅዱስ ገብርኤል መልአክ ኦ እግዝእትየ ማርያም ሰላም ለኪ፤ እመቤቴ ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል ሰላምታ ሰላም እልሻለሁ›› እያሉ ዘወትር ያከብሯታል ያመሰግኗታልም፡፡ ሉቃ 1፡28፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ ዘወትር በምንጸልየው የእሑድ የእመቤታችን ውዳሴ ላይ ‹‹ምልዕተ ጸጋ፣ ምልዕተ ክብር፣ ምልዕተ ውዳሴ የሆንሽ ድንግል ሆይ ከቅዱሳን ሁሉ ይልቅ ትለምኝልኝ ዘንድ ለአንቺ ይገባል፡፡ አንቺ ከሊቃነ ጳጳሳት ትበልጫለሽ፤ ከቅዱሳን ነቢያት፣ ከቅዱሳን ሐዋርያት ከሰብዓ አርድእትም ትበልጫለሽ፡፡ ዳግመኛም ከሱራፌልና ከኪሩቤል ይልቅ የሚበልጥ የመወደድ የመፈራት ግርማ አለሽ፡፡ በእውነት የባሕርያችን መመኪያ አንቺ ነሽ፡፡ ለሰውነታችንም ሕይወትን፣ ድኅነትን የምትለምኚና የምታማልጅን አንቺ ነሽ›› በማለት የእመቤታችን ልዕልናዋን የጸጋዋን ፍጹምነትና የክብሯን ታላቅነት በአጽንኦት ገልጾ መስክሯል፡፡
እመቤታችን በጥር ሃያ አንድ ቀን በታላቅ ክብር ካረፈች በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት በፈቃደ እግዚአብሔር ከያሉበት መጥተው በኢየሩሳሌም ተሰብስበው የፈጣሪያችን እናት ድንግል ማርያምን በጸሎትና በማዕጠንት አክብረው ገንዘው ጥልቅ በሆነ ኃዘን ሊቀብሯት ወደ ጌቴሰማኒ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉምና «ቀድሞ ልጇ ሞቶ ተቀብሮ ሳለ ተነሣ እያሉ ሕዝቡን አስኮበለሉ አሁን ደግሞ እናቱን ሞታ ተነሣች እያሉ እንዳያውኩ ሥጋዋን እናቃጥል» በሚል የክፋት ምክር ተነሳሱ፡፡ በተለይም ደግሞ በእመቤታችን ላይ በክፋትና በተንኮል ከተነሳሱት ከእኒህ አይሁድ መካከል ታውፋንያ የተባለው አይሁዳዊ
አማናዊት ታቦተ እግዚአብሔር የሆነችው የድንግል ማርያም ቅዱስ ሥጋ ያረፈበትን አልጋ ለመያዝ እጁን በድፍረት ዘረጋ፡፡ በዚህን ጊዜ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን (2ኛ ሳሙ 6፡6፤ 1ኛ ዜና 13፡7-10) ላይ የአሚናዳብ ልጅ ዖዛ እጁን በታቦተ ጽዮን ላይ በድፍረት በመዘርጋቱ ምክንያት ተቆጥቶ እንደቀጣው ታውፋንያንም ሰማያዊው መልአክ ሰይፍ እጆቹን ቀጣው ቆረጠው፡፡ «እግዚአብሔር በቀባው ላይ እጁን የሚዘረጋ ንጹሕ አይሆንም (1ኛ ሳሙ 26፡9) እንደተባለ እጆቹም አልጋው ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ፡፡ 
ታውፋንያም ስለተቆረጡት እጆቹ ወደ እመቤታችን አምኖ ወደ እርሷ ቢጮህ ቢማጸናት፤ በቅዱስ ጴጥሮስ አማካይኝነት እጆቹን እንደ ቀድሞ ሆነው ድነውለታል፡፡ በጌታችን ትእዛዝ መልአኩ የእመቤታችንን ቅዱስ ሥጋ ከወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ጋር በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር በክብር አኑሮታል፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት ዮሐንስ ከተመለሰ በኋላ ‹‹እመቤታችን እንደምን አለች?›› አሉት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም «ከገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች» አላቸው፡፡ እነርሱም ዮሐንስ ዐይቶ እኛ ሳናይ ብለው በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፡፡ ጥር አርፋ በነሐሴ ወር ሁለት ሱባኤ ይዘው ሲጨርሱ በነሐሴ 14 መልአኩ ቅዱስ ሥጋዋን ከገነት አምጥቶ ሰጥቷቸው በጸሎትና በምሕላ ቀብረዋታል፡፡ በዚህ ጊዜ ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ ቶማስ አልነበረም፡፡ በሦስተኛው ቀን እንደ ልጇ ተነሥታ ስታርግ፣ ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ ያገኛታል፡፡ በዚህ ጊዜ ትንሣኤዋን ሌሎች ሐዋርያት አይተው፣ ለእርሱ የቀረበት መስሎት አዝኖ ‹‹በፊት የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ አሁን ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ ብሎ ከደመናው ለመውደቅ ተመኘ፡፡ በዚህ ጊዜ እመቤታችን ቶማስን አጽናናችው፡፡ ከእርሱ በቀር ትንሣኤዋን ሌላ እንዳላየ ነገራው ለምስክር እንዲሆነው ሰበኗን/መግነዝ ሰጥታው ዐረገች፡፡ 
ጌታችን ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር ቆይቶ ሙስና መቃብር ሳያገኘው መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል በሥልጣኑ እሑድ በመንፈቀ ሌሊት እንደተነሣ ሁሉ ክብርት እናቱ እመቤታችም በተቀበረች በሦስተኛው ቀን ማኅደረ መለኮት ናትና ሙስና መቃብር ሳያገኛት መግነዝ ፍቱልኝ፣ መቃብር ክፈቱልኝ ሳትል የልጇ ሥልጣን ኃይል ሆኗት መነሣቷን ትንሣኤዋ ‹‹እንደ ልጅዋ ትንሣኤ›› ነው ተብሎ ሲከበርላት ይኖራል፡፡ 
ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያት ወዳሉበት ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ እመቤታችንን እኮ ቀበርናት ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ምስጢሩን ደብቆ ‹‹ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር›› አላቸው፡፡ ሐዋርያትም ‹‹አንተ ተጠራጣሪ ነህ›› ብለው መቃብሩን ሊያሳዩት ሲከፍቱ አጧት፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹እመቤታችን ተነሥታ አርጋለች›› ብሎ ሁኔታውን ተረከላቸው፡፡ ‹‹ለምስክር ይሁንህ›› ብላ የሰጠቸውንም ሰበኗን አሳያቸው፡፡ ሐዋርያትም ይህን አይተው ትንሣኤዋን አመኑ። ሰበኗን ቆራርጠው ለበረከት ተከፋፍለው ወደየሃገረ ስብከታቸው ተመልሰዋል፡፡ ዛሬም በመጾር መስቀልና በካህናት እጅ መስቀላቸው ላይ የሚያስሯት ‹‹መሀረብ›› የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡ በዓመቱም ሐዋርያት ‹‹ቶማስ ትንሣኤሽን አይቶ እንዴት እኛ ይቅርብን!›› ብለው ከነሐሴ አንድ ጀምረው ሱባኤ ገቡ፡፡ በነሐሴ 16 ቀንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቅዱሳን ሐዋርያትን ወደ ሰማይ አሳርጎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቅዳሴ ቀድሶ አቁርቧቸዋል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም የመቤታችንን ትንሣኤና ዕርገቷን በዓይናቸው አይተውና በሚገባ ተረድተው ዓለምን ዙረው አስተምረዋል፡፡ 
+ + + 
ከመጽሐፈ ስንክሳር፡- እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ከመሞቷ በፊት በጌታችን በመድሃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መቃብሩ ቦታ ትጸልይ ነበር፡፡ መንፈስ ቅዱስም ለእመቤታችን ከዚህ ዓለም እንደምትለይ ነገራት፡፡ ጌታችንም በደብረ ዘይት ላሉ ደናግላን ነግሯቸዋልና ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በፍጥነት መጡ፡፡ እርሷም መንፈስ ቅዱስ የነገራትን ለእነርሱ ነገረቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ እመቤታችን እንዲህ ብላ ጸለየች፡- ‹‹ልጄ ወዳጄ፣ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ልመናየን ተቀብለህ ደቀ መዝሙርህን ዮሐንስን በዚህች ሰዓት አምጣው፤ እንዲሁም ሕያዋን የሆኑትን ሐዋርያትን ሁሉንም ነፍሶቻቸውን የለየሃቸውንም ሁሉ ወደ እኔ አምጣቸው፤ አንተ የሕያዋን አምላክ ነህና ለአንተም ምስጋና ይሁን አሜን›› አለች፡፡ 
በዚያን ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ትዕዛዝ ቅዱስ ዮሐንስን ደመና ተሸክማ ወደ እመቤታችን አደረሰችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በፊቷ ሰገደላትና እንዲህ አላት፡- ‹‹ሰላምታ ይገባሻል፣ ጌታችንን ፈጣሪያችንን መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን የወለድሽው ጸጋን የተመላሽ ሆይ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ ከዚህ ዓለም ተለይተሽ በክብር በምስጋና ወደ ዘለዓለም ሕይወት ትሄጃለሽና፡፡ ይህም ስሙ ክቡር ምስጉን የሆነ ጌታችንና ፈጣሪያችን ድንቅ ድንቅ ተአምራቶችን በአንቺ ላይ ከገለጠ በኋላ ነው›› አላት፡፡ እመቤታችንም ይህን በሰማች ጊዜ እጅግ ደስ አላት እግዚአብሔርንምእንዲህ ብላ አመሰገነችው፡- ‹‹ፈጣሪዬ ጌታዬ ላንተ ምስጋና ይሁን፣ የለመንኩህን ሰጥተኸኛልና፡፡ አሁንም ነብሴን ተቀብለው ወደ ሰማይ ወደ አንተ ሊይሳርጓት ከሚመጡ ቅዱሳን መላእክቶችህ ጋር በመምጣትህ የምለምንህን ሁሉ ስጠኝ›› አለችው፡፡ በዚያም ጊዜ ከሰማይ እንዲህ የሚል ቃል መጣ፡- ‹‹እነሆ አሁን መላእክት ይደርሳሉ፡፡ ሐዋርያትም ሁሉ ከምድር ዳርቻ በደመና ተጭነው ለሰማይና ለምድር ጌታ ለኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ወደሆነች ወደ ቅድስት ድንግል ይደርሳሉ፡፡ ወዲያውም ሁሉም ሐዋርያት የሞቱት ከመቃብራቸው ተነሥተው በሕይወት ያሉትም ሁሉም ወደ እመቤታችን ደርሰው ሰገዱላት፡፡ ‹‹አምላካችን ከአንቺ የተወለደ ጸጋን የተመላሽ ሆይ! ደስ ይበልሽ፣ እርሱ ከዚህ ዓለም ለይቶ ቃል ኪዳን እንደሰጠሽ በክብር በምስጋና ከእርሱ ጋር ያሳርግሻልና›› አሏት፡፡ 
በዚያንም ጊዜ እመቤታችን በዐልጋዋ ላይ ተቀመጠችና ሐዋርያትን እንዲህ አለቻቸው፡- ፈጣሪዬ ፈጣሪያችሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እንደሚመጣ እናንተንም እንዳየኋችሁ እንደማየው አሁን ዐወቅሁ፡፡ ከዚህ ከሥጋዬ ወጥቼ ወደ ዘለዓለም ሕይወት እሄዳለሁ፡፡ ነገር ግን ትነግሩኝ ዘንድ እሻለሁ፣ እኔ ከዚህ ዓለም እንደምለይ ከወዴት ዐወቃችሁ?›› ብላ የጠቀቻቸው፡፡ በመጀመሪያ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚያም ሁሉም ሐዋርያት ‹‹ወደ አንቺ እንመጣ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ አዘዘን፣ በደመና ላይም በተጫን ጊዜ እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥነን ደረስን›› አሏት፡፡ 
እመቤታችንም ይህን ነገር ከሐዋርያት በሰማች ጊዜ ድምጿን ከፍ አድርጋ እንዲህ አለች፡- ‹‹ጌታዬና ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ክቡር ምስጉን የሆነ ስምህን ፈጽሜ አመሰግናለሁ፣ የእኔን የአገልጋይህን መከራ ተመልክተህ ድንቅ ኃይልን አድርገህልኛልና ከእንግዲህ ወዲያ ትውልድ ሁሉ ያከብሩኛል ያመሰግኑኛል›› አለች፡፡ ጸሎቷንም ስትጨርስ ሐዋርያትን ‹‹ዕጣን አምጥታችሁ በማጠን የጌታዬን የኢየሱስ ክርስቶስን ስሙን ጥሩት›› አለቻቸው፡፡ እነሱም እንዳዘዘቻቸው አደረጉ፡፡ በዚያም ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን እልፍ አእላፍ ቅዱሳን መላእክቱ አጅበው እያመሰገኑት መጣና እመቤታችንን አረጋጋት፡፡ ያዘጋጀላትንም ተድላ ደስታ ነገራት፡፡ በዚያም ጊዜ ድንቆቸ የሆኑ ተአምራት ተደረጉ፡፡ ዓይነ ሥውራን ማየት ቻሉ፣ ደንቆሮች መስማት ቻሉ፣ ዲዳዎች ተናገሩ፣ ለምጻሞች ነጹ፣ ሐንካሶች መሄድ ቻሉ፣ ደዌ ያለበትም ሁሉ ዳነ፡፡ የብርሃን እናቱ ወላዲተ አምላክ እመቤታችን ወደ አለችበት ቤት በቀረቡ ጊዜ ከደዌአቸው ሁሉ ይፈወሳሉና፡፡ 
ከዚህም በኋላ እመቤታችን ተወዳጅ ልጇን ‹‹በአየር ውስጥ ተበትነው ከሚኖሩ ከሚያስነግጡ ግሩማን መላእክት የተነሣ ከእሳት ባሕርም የተነሣ እፈራለሁ›› ባለችው ጊዜ እርሱም ‹‹እናቴ ሆይ ከእነርሱ ለማንም በአንቺ ላይ ሥልጣን የለውም›› አላት፡፡ ከሥጋዋም የምትለይበት ጊዜ ሲደርስ ሐዋርያትንና ደናግል ትባርካቸው ዘንድ እያለቀሱ ለመኗት፡፡ እመቤታችንም እጇን በላያቸው ዘርግታ ባረከቻቸው፡፡ በዚህን ጊዜ ጌታችን ቅድስት ንጽሕት ነፍሷን ከሥጋዋ ለይቶ በመለኮታዊ እጆቹ ይዞ በብርሃን ልብስ አጎናጽፎ ወደ ከፍተኛ መኖሪያ ከእርሱ ጋር አሳረጋት። ሥጋዋን ግን እንደሚገባ ገንዘው፤ ወደ ጌቴ ሰማኒ ተሸክመው እንዲወስዷ ሐዋርያትን አዘዛቸው፡፡ ነፍሷ ከሥጋዋ ከመውጣቷ በፊት በሰው አንደበት ይህ ነው ተብሎ የማይነገር ብርሃን እያየች ነበር፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችንም ‹‹እንግዲህ ሥጋሽን ተድላ ደስታ ወዳለበት ገነት አፈልሳለሁ፡፡ ዳግመኛም ሥጋሽን ከነፍሽ ጋር አዋሕጄ አስነሥቼ መላእክት በፊትሽ ሆነው በሚያመሰግኑበት አምሳያ በሌለው ተድላ ደስታ ባለበት መኖሪያ አኖርሻለሁ›› አላት፡፡ 
እመቤታችንም እንዲህ አለች፡- ‹‹አቤቱ በረቀቀ ጥበብህ ይህን ሁሉ የሠራህ አመሰግንሃለሁ፤ ሁለተኛም ልመናየን ትሰማ ዘንድ እለምንሃለሁ፤ በስሜ ወደ አንተ የሚለምነውን ሁሉ፤ ልመናውን ተቀበለው በመከራም ውስጥ ሁኖ ስሜን ጠርቶ ወደ አንተ የሚለምነውን ከመከራም ሁሉ አድነው፤ በሰማይም በምድርም በሥራው ላይ ሁሉ አንተ ከሃሊ ነህና መታሰቢያየን በውስጧ የሚያደርጉባትን ቦታ ሁሉ ባርክ፣ በእኔ ስም የሚያቀርቡትን የሁሉንም መሥዋዕታቸውን ተቀበል›› አለችው፡፡ ጌታችንም እንዲህ ብሎ መለሰላት፡- ‹‹የለመንሽኝን ሁሉ አደርግልሻለሁ፤ ደስ ይበልሽ፣ ከእኔ ከአባቴ ከመንፈስ ቅዱስ ዘንድ ጸጋ ክብር ባለሟልነት ተሰጥቶሻልና ስምሽንም ጠርቶ የሚለምን ሁሉ በዚህ ዓለምም በወዲያኛው ዓለምም ከቶ አይጠፋም›› አላት፡፡ እመቤታችንም በታላቅ ክብር ካረፈች በኋላ ጌታችን እንዳዘዘ ወደ ጌቴ ሰማኒ ሊወስዷት ሐዋርይት ገንዘው ተሸከሟት፡፡ አይሁድም በሰሙ ጊዜ ሥጋዋን ሊይቃጥሉ ወጡ፡፡ ከእርሳቸውም አንዱ ከምድር ይጥላት ዘንድ የእመቤታችንን አልጋዋን ያዘ፡፡ ያን ጊዜም ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘ መልአክ እጆቹን በእሳት ሰይፍ ቀጣውና እጆቹ በአልጋው ላይ ጠንጠለጠሉ፡፡ ያን ጊዜ በጌታችን አምኖ ወደ እመቤታችን እያለቀሰ እንዲህ ብሎ ለመነ፡- ‹‹የእውነተኛ አምላክ የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እናት ሆይ! አንቺ በእውነት ድንግል ይሆንሽ በእኔ ላይ ይቅርታ ታደርጊ ዘንድ አለምንሻለሁ፡፡›› በሐዋርይትም ልመና እጆቹ ተመልሰው እንደቀድሞው ደኅነኞች ሆኑ፡፡ 
ሐዋርያትም እመቤታችንን በቀብሯት ጊዜ ከዚያ ሶስት ቀን ኖሩ፣ ዕረፍቷም የሆነው እሑድ ቀን ጥር ወር በ21 ቀን ነበረ፡፡ ጌታችንም ብርሃናውያን መላእክትን ላከ፣ እነርሱም ሥጋዋን ከመቃብር ወስደው በገነት ውስጥ በዕፀ ሕይወት ሥር አኖሯት፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ግን ያን ጊዜ አልነበረም በደመና ላይ ተጭኖ እርሱ ሲመጣ መላእክት ሲያሳርጓት እመቤታችንን አገኟት፡፡ ቅዱሳን መላእክትም ‹‹ለአምላክ እናት ለእመቤታችን ድንግል ማርይም ና እጅ ንሣ›› አሉት፡፡ እርሱም ሰገደላትና ተሳለማት ከእርሷም ተባረከ፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሐዋርያት ደረሰ፡፡ እነርሱም እመቤታችንን ማርያምን እንዳረፈችና እንደ ቀበሯት ነገሩት፡፡ ቶማስም ‹‹ሥጋዋን እስከማይ አላምንም›› አላቸው፡፡ ሥጋውንም ያሳዩት ዘንድ ወደ መቃብሯት ባደረሱት ጊዜ በመቃብሩ ውስጥ ሥጋዋን አላገኙም፤ እነርሱም ደንግጠው እያደነቁ ሳለ ያን ጊዜ ቶማስ ከመላእክት ጋር ወደ ሰማይ ስታርግ እመቤታችን እንዳገኛት ነገራቸው፡፡ ሐዋርያትም ይህን በሰሙ ጊዜ የእመቤታችንን ዕርገቷን ስላላዩ እጅግ አዘኑ፡፡ ሥጋዋን በምድር ውስጥ ይተው ዘንድ እንዳልወደደ መንፈስ ቅዱስ አስገነዘባቸው፡፡ ከዚህም በኋላ አንድ ጊዜ ደግሞ እርሷን ያሳያቸው ዘንድ እንዳለው ጌታችን ቃል ኪዳን በማድረግ ተስፋ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም በተስፋ እስከ ነሐሴ 16 በተስፋ ኖሩ፡፡
አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችን ፍቅሯን ጣዕሟን ታሳድርብን!
+ + + 
ዳግመኛም በዚህች ዕለት ጥር 21 
+ እመቤታችን ተገልጣለት ‹‹ዕረፍትህ በዕረፍቴ ቀን ነውና ተዘጋጅ›› ብላ የነገረችው የኑሲሱ አቡነ ጎርጎሪዮስ ዕረፍቱ ነው፡፡ 
+ አርሲ ፈንታሌ ተራራ ላይ ሠሪቲ ለምትባል ጠንቋይ እየተላላኩ ሕዝቡን የሚያስቱና የሚያሰቃዩ አራት መቶ ሰባ ሺህ ሦስት መቶ አጋንንትን በጸሎታቸው እሳት ከሰማይ አውርደው ያቃጠሏቸው የመሐግሉ አቡነ ቀውስጦስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+ የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ ታላቅ ወንድም የሆኑት ዋሸራን ገዳምን የመሠረቱት በሱባኤ ስለ ዋሸራ ሕዝብ ታላቅ ምሥጢር የተነገራቸው አቡነ ተስፋ ኢየሱስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+ በሐይቅ ሲያጥኑ የማዕጠንታቸው ሽታ እስከ ጣና ቂርቆስ ድረስ ይሸት ስለነበር ቅዱሳን ሲሸታቸው አባ ኤልያስ ዛሬ ቅዳሴ ገባ ይሏቸው የነበሩትና በሞት ማረፋቸውን የሚያጥንባት ጽንሐቸው አፍ አውጥታ የተናገረችላቸው የመርጦው አቡነ ኤልያስም ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ የሮሜው አገር ንጉሥ ልጅ የሆነችው ቅድስት ኢላርያ ዕረፍቷ ነው፡፡ 
+ የደብረ ጽላልሽዋ ቅድስት ማርያም ክብራም ዕረፍቷ ነው፡፡ 
+ ነቢዩ ኤርምያስ መታሰቢያ በዓሉ ነው፡፡ 
+ በሰማዕትነት ያረፈ በዋሻ የሚኖር ቅዱስ ኒቆላዎስ መታሰቢያ በዓሉ መሆኑን ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል፡፡ 
+ በመናፍቁ ንጉሥ በመርቅያን ዘመን መኮንኑ ጳውሎስና ቀሲስ ሲላስ ምስክር ሆነው በዚህች ዕለት ዐርፈዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን የዕረፍቷ በዓል ዕለት በጌቴሴማኒ ከምእመናን ጋር ሆነው ተሰብስበው ሳሉ ከሃዲው መኮንን መጥቶ በዚያ ካሉት አንድም ሰው ሳያስቀር የገደላቸው መሆኑን ስንክሳሩ በአጭሩ ይጠቅሳቸዋል፡፡ 
አቡነ ተስፋ ኢየሱስ ዘጎጃም፡- የትውልድ ሀገራቸው ጎጃም ሲሆን የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ ዘግሽ ዓባይ ታላቅ ወንድም ናቸው፡፡ እንደ ወንድማቸው የተወለዱት በመልአክ ብስራት ነው፡፡ አቡነ ተስፋ ኢየሱስን መልአክ እየመራ ወስዶ ጣና ሐይቅ ገዳም አደረሳቸውና በዚያ የቤተ ክርስቲያን ትምህርትና ሥርዓቷን ሁሉ በሚገባ ተማሩ፡፡ የዋሸራን ገዳም በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው ከመሠረቱት 300 ቅዱሳን መነኮሳት ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡ በ300ው መነኮሳትም ተመርጠው የገዳሟ ባራኪ ሆነው ተሹመው አገልግለዋል፡፡ ሱባኤ ገብተው ስለ ዋሸራ ገዳምና ስለ አካባቢው ሕዝብ ምሥጢር የተገለጠላቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ገዳሟ ፈለፈ ሊቃውንት እንደምትሆን ተገልጦላቸዋል፡፡ ደግመው ሱባኤ ቢገቡ ገዳሟ በስተኋላ እንደምትቀዘቅዝ ተገለጠላቸው፡፡ ለ3ኛም ጊዜ ሱባኤ ቢገቡ ገዳሟ እስከ ዕለተ ምዕዓት ጸንታ እንደምትኖር ተገልጦላቸው በዚህም ደስ ተሰኝተዋል፡፡ ዋሸራ ገዳም በመጀመሪያ በባሐር የተከበበች ብትሆንም አቡነ ተስፋ ኢየሱስ ባሕሩን ቢባርኩት ተስተካክሎ እንደ ጸበል ሆኖላቸዋል፡፡ እመቤታችንም ዕለት ዕለት እየተገለጠችላቸው ትባርካቸው ነበር፡፡ ጻድቁ በተጋድሎ ብዙ ካገለገሉና ከጌታችን ታላቅ ቃል ኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ጥር 21 ቀን ዐርፈው በዚያው ተቀብረዋል፡፡ 
ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን፡፡ 
+ + + 
አቡነ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ፡- ይኸውም የቅዱስ ባስልዮስ ወንድም ነው፡፡ ሀገሩ ቂሳርያ ሲሆን የተሾመው ኑሲስ በተባለች ደሴት ላይ ነው፡፡ መናፍቁ ሰባልዮስ ‹‹አንድ ገጽ›› በማለቱ ሌሎቹ መናፍቃንም መቅዶንዮስና አቡሊናርዮስ ‹‹መንፈስ ቅዱስ ህጹፅ›› እና ‹ወልድ ሥጋ እንጂ ነፍስ አልነሳም› በማለታቸው በ381 ዓ.ም 150ው ሊቃውንት በቍስጥንጥንያ ተሰብስበው መናፍቃኑን ተከራክረው እረተው ሃይማኖትን ሲያጸኑ ከጢሞቲዎስ ጋር አንድ ላይ የጉባኤው አፈ ጉባዔ የነበረው ሊቁ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ ነበር፡፡ እርሱም በጉባኤው ላይ እነ መቅዶንዮስንና አቡሊናርዮስን ተከራክሮ በመርታት መልስ አሳጥቷቸዋል፡፡ ሃይማኖትንም አጽንቷል፡፡ 
ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ቅዳሴ ሲቀድስ ጌታችን በርግብ አምሳል ሲወርድ ያየው ስለነበር ዘወትር እያለቀሰ ይቀድሳል፡፡ ከተጋድሎውም ጽናት የተነሣ ታማሚ ሆኖ ነበር፡፡ በኤጲስ ቆጶስነት ተሹሞ 33 ዓመት ኖሯል፡፡ ከተጋድሎውም ብዛት ድካም አጋጥሞት ነበርና አንድ ቀን ወንድሙ ባስልዮስ ሊጠይቀው መጣ፡፡ ቅዱስ ጎርጎርዮስም እንደልማዱ ሊቀድስ ወደ መሠዊያው በወጣ ጊዜ እመቤታችን ተገለጠችለትና ‹‹ዕረፍትህ በዕረፍቴ ቀን ነውና ዛሬ ወደእኔ ትመጣለህ›› አለችው፡፡ ጎርጎርዮስም የቁርባኑን ቅዳሴ ሲጨርስ ሕዝቡን በቀናች ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ ለመምከር ተነሣ ነገር ግን ከድካምና ሕመም ብዛት ሰውነቱ መቆም ስላልቻለ ወንደሙን ባስልዮስን ‹‹ዛሬ አንተ አስተምራቸው›› አለው፡፡ ወዲያውም እንደሚያንቀላፋ ሆነና ዐረፍ አለ፡፡ በቀሰቀሱትም ጊዜ በሞት ዐርፎ አገኙት፡፡ ይኸውን ጥር 21 ቀን ነው፡፡ በስሙ የተጠራ አንድ ቅዳሴና ገድለ ዜና አለው፡፡ በትንቢት ተናጋሪነቱ፣ በደራሲነቱና በመምህርነቱ መጽሐፍ ‹‹ጎርጎሪዮስ ዐቃቤ ሥራይ ቁስለ መድኃኒት ዘነፍስ›› ይለዋል፡፡ ከሃዲው ንጉሥ ዑልያኖስ ወንድማማቾቹን ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን በጸሎታቸው ሰዓት ደርሶባቸው እነርሱን ገድሎ መሥዋዕታቸውን ሊበላባቸው ሲመጣባቸው የቅዱስ መርቆሬዎስን ሥዕል በጸሎት ቢማጸኑ ሥዕሉ በገዘፈ ሥጋ ሆኖ በተአምራት ዑልያኖስን በጦር ወግቶ ገድሎላቸዋል፡፡
የቅዱስ ጎርጎሪዎስ ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን፡፡ 
+ + + 
አቡነ ኤልያስ ዘመርጦ፡- ትውልድ ሀገራቸው ጎጃም መርጡ ለማርያም ነው፡፡ አባታቸው መሠረተ ጽዮን መርጡ ለማርያምን በሹመት ብዙ ዘመን አገልግለዋል፡፡ አቡነ ኤልያስ 7 ዓመት ሲሆናቸው ለታላቁ ጻድቅ መቋሚያቸው እንደ ሰው አፍ አውጥታ ለምትናገረው ለአቡነ ተክል አልፋ ሰጧቸው፡፡ አቡነ ተክል አልፋም ብሉያቱን፣ ሐዲሳቱን፣ ቀኖናውንና ዶግማውን ሁሉ በሥርዓት ካስተማሯቸው በኋላ አመንኩሰዋቸዋል፡፡ ጻድቁ ወደ ሐይቅ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ሄደው 14 ዓመት በገዳሙ አገልግለዋል፡፡ 
አቡነ ኤልያስ በሚያጥኑበት ጊዜ የዕጣኑ ሽታ እስከ ጣና ቂርቆስ ድረስ ይሸት ነበርና ቅዱሳን ሲሸታቸው ‹‹ዛሬ አባ ኤልያስ ቅዳሴ ገባ›› ይላሉ፡፡ ጻድቁ ባረፉ ጊዜ በሞት መለየታቸውን ለመነኮሳቱ የተናገረችው ያጥኑባት የነበረችው ጽንሐ ናት፡፡ እንደ ሰው አፍ አውጥታ ‹‹አባታችን ዐረፉ›› ብላ ተናግራለች፡፡ መነኮሳቱም ወስደው በተድባበ ማርያም ቀብረዋቸዋል፡፡ በስማቸው የተቀረጹ ታቦታት በተደባበ ማርያም፣ በቸር ተከል ማርያምና በየህላ ቅዱስ ሚካኤል እንደሚገኝ ሊቀ ብርሃናት መርቆሬዎስ አረጋ ጽፈዋል፡፡
የአቡነ ኤልያስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን፡፡
+ + + 
ቅድስት ማርያም ክብራ ዘጽላልሽ፡- ትውልዷ ሸዋ ደብረ ጽላልሽ ሲሆን በወቅቱ የትልቅ ባለስልጣን የመስፍን ልጅ ነበረች፡፡ ወደ ደብረ በግዕ ገዳም ገብታ መነኮሳቱን በብዙ ድካም ስታገለግል ከኖረች በኋላ በአቡነ ሕፃን ሞዐ እጅ መንኩሳለች፡፡ 
አቡነ ሕፃን ሞዐ ማለት የደብረ በግዕህ ገዳምን የመሠረቱት ታላቅ አባት ሲሆኑ እንደበሬ በመታረስ ሰማዕትነት የተቀበሉ ናቸው፡፡ ጻድቁን ከአንድ በሬ ጋር ጠምደው ቀኑን ሙሉ ሲያርሷቸው በድካም ሆነው በኋይል የተነፈሱበት ቦታ ላይ ምድሪቱ ዛሬም ድረስ እንደእርሳቸው ስትተነፍስ የእስትንፋሷ ድምጹና ሙቀቱ ይሰማል፡፡ ለአስም ሕመም መድኃኒት ነው፡፡ ቦታውም ከደብረ ብርሃን በእግር የሁለት ሰዓት ተኩል መንገድ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን የጻድቁ ቤተ ክርስቲያኑ ከወይንዬ ተክለ ሃይማኖት ገዳም አጠገብ ይገኛል፡፡ 
ቅድስት ማርያም ክብራ በጻድቁ ሕፃን ሞዐ እጅ ከመነኮሰች በኋላ ወደ አቡነ ዜና ማርቆስ ገዳም ገብታ በታላቅ ተጋድሎ ስትኖር ሰይጣን ብዙ ጊዜ በሰው አምሳል እየተገለጠ በፈተና ሊጥላት ይሞክር ነበር፡፡ የእግዚአብሔርም መልአክ እየተገለጠ ያበረታት ነበር፡፡ እርሷም በበትረ መስቀሏ ሰይጣንን እያሳደደች ታባርረው ነበር፡፡ ረድኤት በረከቷ ይደርብን በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + 
ቅድስት ኢላርያ፡- ይኽችም ቅድስት የሮሜው አገር ንጉሥ የዘይኑን ልጅ ናት፡፡ እርሱም እግዚአብሔርን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ነው፡፡ ልጁ ቅድስት ኢላርያንም ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እያስተማረ አሳደጋት፡፡ ከሁለት ሴቶቹ ለጆቹ በቀር ወንድ ልጅ የለውም ነበር፡፡ 
ቅድስት ኢላርያም ዕድሜዋ ከፍ ሲል ዓለምን ፍጹም ንቃለችና የምንኩስናን ልብስ የመላእክትንም አስኬማ ትለብስ ዘንድ ወደደች፡፡ ከቤተ መንግሥትም ተደብቃ ወጥታ የወንድ ልብስ በመልበስ ወደ ግብጽ አገር ሄደች፡፡ ወደ አስቄጥስ ገዳምም ገብታ ስሙ አባ ባውሚን የሚባል ፍጹም ሽማግሌ ጻድቅ ሰውን አግኝታ የምንኩስና ሀሳቧን ነገረችው፡፡ እርሷም ሴት እንደሆነች ስትነግረው ምሥጢሯን ጠብቆ ለብቻዋ ከዋሻ ውስጥ አስገባት፡፡ እየጎበኛትም ልትሠራው የሚገባትን ሁሉ ያስተምራት ነበር፡፡ እንዲህም ሆና በዚያ ዋሻ ውስጥ 12 ዓመት ኖረች፡፡ ቅድስት ኢላርያ ፂም ስለሌላት ለአረጋውያን መነኮሳት ጃንደረባ ትመስላቸው ነበር፡፡ በወንድ ስም አጠራርም አባ ኢላርዮን ብለው ይጠሯት ነበር፡፡ 
ከአባቷ ዘንድ ያለችው ታናሽ እኅቷ ርኩስ መንፈስ አደረባትና ብዙ አሠቃያት፡፡ ያድኗትም ዘንድ አባቷ ብዙ በመድከም ገንዘቡን አወጣ ነገር ግን ልትድን አልቻለችም፡፡ መኳንንቶቹም ወደ ግብጽ አስጥስ ገዳም እንዲልካት ለንጉሡ ነገሩት-በዚያ ያሉ መነኮሳት ክብራቸውና ጸጋቸው በሮም አገሮች ሁሉ ታውቋልና፡፡ ንጉሡም የታመመችውን ልጁን ከብዙ ሠራዊት ጋር ወደ ግብጽ ላካት፡፡ ለመነኮሳቱም ‹‹… ሁለት ሴቶች ልጆችን ወለድኩ ነገር ግን አንደኛዋ ጥላኝ ጠፋች፣ ሁለተኛዋንም ርኩስ መንፈስ ይዞ መጨወቻ አደረገብኝ፡፡ ቅዱሳን አባቶቼ ሆይ ልጄን በጸሎታቸሁ ትፈውሱልኝ ዘንድ ቅድስናችሁን እለምናለሁ›› የምትል ደብዳቤ ጽፎ ላከላቸው፡፡ መነኮሳቱም የንጉሡን ደብዳቤ ካነበቡ በኋላ በልጅቱ ላይ ጸለዩ፡፡ ነገር ግን ያደረባት ርኩስ መንፈስ ሊለቃት አልቻለም፡፡ ከዚህም በኋላ አረጋውያኑ መነኮሳት ጃንደረባ የሚሏትን ኢላርያን ጠርተው ‹‹እግዚአብሔር እስካዳናት ድረስ የንጉሡን ልጅ ወስደህ በላይዋ ላይ ጸልይ›› ብለው ሰጧት፡፡ እርሷም ‹‹ይህ ለእናንተ እንጂ ለእኔ አይቻለኝም›› ብትላቸውም ግድ አሏት፡፡ 
ከዚህም በኋላ ቅድስት ኢላርያ የታመመችውን ልጅ ወደ በዓቷ ወስዳ ጸሎት አደረገችላት፡፡ ሰይጣኑም ወዲያው ጥሏት ሸሸ፡፡ በጥቂት ቀንም ውስጥ ፈጽማ ዳነች፡፡ ቅድስት ኢላርያም እኅቷ እንደሆነች ታውቃለችና አቅፋ ትስማት ነበር ስለ ፍቅሯና ናፍቆቷም ወደ ውጭ እየወጣች ታለቅስ ነበር ነገር ግን ታማ የነበረችው እኅቷ አላወቀቻትም፡፡ ቅድስት ኢላርያም በጸሎቷ ከፈወሰቻ በኋላ ወደ አረጋውያኑ መነኮሳት ወስዳ ‹‹እነሆ በጸሎታች እግዚአብሔር ፈውሷታልና ወደ ንጉሡ አባቷ መልሷት›› ብላ ሰጠቻቸው፡፡ እነርሱም እጅግ ደስ ብሏቸው ወደ አባቷ መለሷት፡፡ ሮሜ አገር በደረሰችም ጊዜ ልጃቸው ስለዳነችላቸው ንጉሡና መኳንንቱ የአገሩም ሰዎች ሁሉ ተደስተው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ከዚህም በኋላ አባቷ በገዳም ስለነበራት ቆይታ ልጁን ጠየቃት፡፡ እርሷም ‹‹ያ በጸሎቱ ያዳነኝ አባ ኢላርዮን የሚባል መነኩሴ አብዝቶ ይወደኛል፤ አቅፎም ይስመኛል›› አለችው፡፡ ንጉሡም ይህንን ሲሰማ ልቡ ታወከና ‹‹መነኩሴ እንዴት ሴትን ለመሳም ይገባዋል/›› አለ፡፡ በዚህም ጊዜ ‹‹በእኔ ላይ ይጸልይ ዘንድ አገሬንም ይባርክ ዘንድ ልጄን ያዳናትን አባ ኢላርዮንን ወደኔ ላኩልኝ›› ብሎ ደብዳቤ ጽፎ ወደ አስቄጥስ ገዳም ላከ፡፡ 
አረጋውያኑም ቅድስት ኢላርያ ጠርተው ወደ ንጉሡ አገር ሄዳ እንድትባርከው አዘዟት፡፡ እርሷም ይተዋት ዘንድ እያለቀሰች ብትለምናቸውም እነርሱ ግን ‹‹ይህ ንጉሥ ክርስቲያኖችን የሚወድ ጻድቅ ነው፣ ቅዱሳት መጻሕፍትም እንደሚያዙን ትእዛዙን መተላለፍ የለብንም›› ብለው አስገድደው ላኳት፡፡ 
ወደ ንጉሡም በደረሰች ጊዜ ሁሉም በክብር ተቀብለው ተሳለሟት፡፡ ንጉሡና ንግሥቲቱም ለብቻቸው ሆነው ወደ ውስጠኛ ክፍል አስገቧትና ንጉሡ እንዲህ ብሎ ጠየቃት፡- ‹‹ልጄን ትስማት እንደነበር በሰማሁ ጊዜ በሀሳቤ ታውኬያለሁ፤ መነኩሴ ሴትን መሳም አይገባውምና ይህን ነገር ትገልጥልኝ ዘንድ እወዳለሁ›› አላት፡፡ የከበረች ቅድስት ኢላርያም በነገርኳችሁ ጊዜ ወደ አስጥስ ገዳም መሄድን ላትከለክሉኝ የከበረ ወንጌልን አምጥታችሁ ማሉልኝ›› አለቻቸው፡፡ እነርሱም ማሉላት፡፡ በዚህም ጊዜ እርሷ ማለት ልጃቸው ኢላርያ መሆኗን ነገረቻቸው፡፡ እንዴት ከቤተ መንግሥት እንደወጣችም አስረዳቻቸውና በአካሏ ላይ ያለውን ምልክት አሳየቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ በቤተ መንግሥቱ ታላቅ ጩኸት ሆነ፡፡ አቅፈውም እየሳሟት አለቀሱ፡፡ ‹‹ከእኛ ዘንድ እንድትሄጂ ከቶ አንተውሽም›› አሏት፡፡ እርሷም ‹‹በከበረ ወንጌል የማላቸሁትን መሐላ አስቡ›› አለቻቸው፡፡ እሺ ብለው ግን እስከ 40 ቀን አብራቸው እንድትቆይ ለመኗት 40 ቀን አብራቸው ቆየች፡፡
ቅድስት ኢላርያም ወደ አስቄጥስ ገዳም ከተመለሰች በኋላ ንጉሡ ዘይኑን ለገዳሙ መነኮሳት ለፍላጎታቸው ይሆን ዘንድ የግብጽን ምድር ግብር እንዲሰጧቸው አዘዘ፡፡ በዚያም ወራት በአባ መቃርስ ገዳም 400 የመነኮሳት ቤቶች ተሠሩ፡፡ በአባ ዮሐንስ ገዳም 700 በአባ ሙሴ ገዳም 300 ቤቶቸ ተሠሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ቅድስት ኢላርያ 5 ዓመት ኖራ በሰላም ዐረፈች፡፡ ከዕረፍቷም አስቀድሞ እርሷ ሴት እንደሆነች ያወቀ የለም፡፡ 
የቅድስት ኢላርያ ረድኤት በረከቷ ይደርብን በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + 
አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል፡- ቅዱሳን አባቶቻችን እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖትና እነ አቡነ ዜና ማርቆስ ሌሎቹም እነ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ ሕፃን ሞዐ፣ አቡነ አኖሪዮስ(ትልቁ)፣ አቡነ ገላውዲዮስ፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋርና አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል በሥጋም ዘመዳሞች ናቸው፡፡ ይኸውም የመሐግሉ አቡነ ቀውስጦስ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የቅርብ ዘመድ ናቸው፡፡ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት እናት እግዚእ ኀረያና የአቡነ ቀውስጦስ እናት እብነ ጽዮን ታላቅና ታናሸ ናችው፡፡ በአባትም በኩል ወረደ ምሕረት ዘካርያስን ወለደ፡፡ ዘካርያስም የእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አባት የሆኑ 6 ወንድማማች ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም እንድርያስ፣ አርከሌድስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብ፣ ቀሲስ ዮሐንስና ቀሲስ ዮናስ ናቸው፡፡ እንድርያስም ሳሙኤል ዘወገግን ወለደ፤ አርከሌድስም ሕፃን ሞዐን ወለደ፤ ዘርዐ አብርሃምም ታላቁን አኖርዮስን ወለደ፤ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብም ተክለ ሃይማኖትን ወለደ፤ ቀሲስ ዮሐንስም ዜና ማርቆስን ወለደ፣ ቀሲስ ዮናስ ደግሞ የፈጠጋሩን ማትያስንና ገላውዲዮስን ወለዳቸው፡፡ ገላውዲዮስም የመሐግሉ ቀውስጦስን ወለደ፡፡
አቡነ ቀውስጦስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከሾሙአቸው ከ12ቱ ንብረ ዕድ ወስጥ አንዱ ሲሆኑ ደብረ ሊባኖስንም የሚያጥኑበትም ወር በመጋቢት ወር ነበር። ሕዝቡ አጥብቆ የሚወዳቸውና የሚያከበራቸው አባት ናቸው፡፡
ግብፃዊው አቡነ ያዕቆብ ከግብፅ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የደብረ ሊባኖሱን እጨጌ አቡነ ፊልጶስን አስጠርተው፤ ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት “ኢትዮጵያ በአንድ ጳጳስ መወሰን የለባትም፡፡ ስለዚህ ዐሥራ ሁለት አበው መርጠን ክርስትና ይስፋፋ” ብለው ባቀረቡት ሐሳብ መሠረት፤ አቡነ ፊልጶስ ዘደብረ ሊባኖስ /ኤጲስ ቆጶስ/፣ አቡነ አኖሬዎስ ዘሞረት፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋር፣ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ አኖሬዎስ ዘወረብ፣ አቡነ ታዴዎስ ዘጽላልሽ፣ አቡነ ገብረ ክርስቶስ ዘግድም፣ አቡነ መርቆሬዎስ ዘመርሐ ቤቴ፣ አቡነ አድኃኒ ዘዳሞት፣ አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል፣ አቡነ ኢዮስያስ ዘወጅ፣ አቡነ ዮሴፍ ዘእናርያን መርጠው ሀገረ ስብከት ተሰጥቷቸው ለሐዋርያዊ ተልእኮ ተሠማሩ፡፡ ዐሥራ ሁለቱን ንቡራነ ዕድ ለስብከተ ወንጌል በመላዋ አገሪቱ ሲሠማሩ፡፡
ጻድቁ አቡነ ቀውስጦስ አርሲ ፈንታሌ ተራራ ላይ ሠሪቲ ለምትባል ጠንቋይ እየተላላኩ ሕዝቡን የሚያስቱና የሚያሰቃዩ 470300 (አራት መቶ ሰባ ሺህ ሦስት መቶ) አጋንንትን በጸሎታቸው እሳት ከሰማይ አውርደው ተራውንን ደምስሰው አጋንንቱን ያቃጠሉ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ የታናሽ ወንድማቸው የዐፄ ይኩኖ አምላክ ልጅ ዐፄ አምደ ጽዮን በክፉዎች ምክር የአባቱን እቁባት በማግባቱ አቡነ ቀውስጦስ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ ሄደው ንጉሡን ስለገሠፁት በግዞት ወስዶ ጎናቸው በጦር ወግቶ ገድሏቸዋል፡፡ ጻድቁ ልደታቸውም ሆነ ዕረፍታቸው ከእመቤታችን ልደትና ዕረፍት ጋር የተባበረላቸው ናቸው፡፡ ግንቦት አንድ ቀን ተወልደው ጥር 21 ቀን ዐርፈዋል፡፡ 
የአቡነ ቀውስጦስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን፡፡
LIKE OUR PAGE https://www.facebook.com/tewadhdohaimanotachin

Wednesday, January 23, 2019

ጥር 15 - ወበዛቲ ዕለት

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈሰ ቅዱስ ስም አሜን
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 
ጥር 15-በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ የከበረች ወንጌልን ሰብኮ ጣዖት አምላኪዎችን በተአምራቱ ያሳመነውና ብዙ አሰቃቂ መከራዎችን የተቀበለው ሕፃኑ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ማኅበርተኞቹ የሆኑ ዓሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎችም አብረው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ 
+ በግራኝ ዘመን ከአንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር በእሳት ተቃጥሎ በሰማዕትነት ያረፈው አቡነ ቄርሎስ ዕረፍቱ ነው፡፡
+ የሶርያ ክርስቲያኖች በዚህች ዕለት በዓሉን በድምቀት የሚያከብሩለት የኑሲሱ አቡነ ጎርጎሪዮስ መታሰቢያ በዓሉ ነው፡፡ 
+ ነቢዩ ቅዱስ አብድዩ ዕረፍቱ ነው፡፡
አቡነ ቄርሎስ ኢትዮጵያዊ፡- አባታቸው ሳይንቱ እናታቸው ወለቃት ሲባሉ የመጀመሪያ ስማቸው መብዓ ሥላሴ ነው፡፡ በባሕታዊነታቸው መላ ገዳማቱ ሁሉ ያደንቋቸው የነበሩ ሲሆን እንደ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ 60 አንበሶችና 60 ነብሮች የተሰጣቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ጻድቁ በክፉው ግራኝ ዘመን ከአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጋር አብረው ተቃጥለው ነው በሰማዕትነት ያረፉት፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!


+++
ነቢዩ ቅዱስ አብድዩ፡- የስሙ ትርጓሜ ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋይ›› ማለት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ 1ኛ ነገ 18፡3 ላይ ‹‹አብደዩ እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር›› ተብሎ የተነገረለት እውነትም ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋይ›› የሆነ የነቢዩ ኤልያስ ደቀመዝሙር የነበረ ታላቅ ነቢይ ነው፡፡ ይህም ቅዱስ ነቢይ ከጠረፍ በረሃ አቅራቢያ ካለች ሱሳም በምትባል አገር ካሉ ሰዎች ወገን ነው፡፡ አባቱ ሐናንያ ይባላል፡፡ ለነቢዩ ኤልያስ ደቀ መዝሙሩ ሆኖ በንጉሡ በአክዓብምና በንግሥቲቱ በኤልዛቤል ምክንያት በእርሱ ላይ የመጣውን መከራ ሁሉ ታግሷል፡፡ ታላቁ ነቢይ ኤልያስ ከእነ ኤልዛቤል ሸሽቶ ወደ ተራራ ላይ ወጥቶ በዋሻ ተሸሽጎ ምግቡን አሞራ እያመጣለት በኖረበት ጊዜ እንኳን ነቢዩ አብድዩ ግን ብቻውን የእግዚአብሔርን ነቢያት ይንከባከብ ነበር፡፡ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥ የነበረ ቢሆንም ንግሥት ኤልዛቤል የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ አብድዩ መቶውን ነቢያት ወስዶ ሃምሳ ሃምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው የነበረ ታላቅ ባለውለታ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ታሪኩ እንዲህ ተብሎ ነው የተጻፈው፡-
‹‹ከብዙ ቀንም በኋላ በሦስተኛው ዓመት ‹‹ሂድ ለአክዓብ ተገለጥ፥ በምድር ላይም ዝናብ እሰጣለሁ›› የሚል የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኤልያስ መጣ፡፡ ኤልያስም ለአክዓብ ይገለጥ ዘንድ ሄደ፤ በሰማርያም ራብ ጸንቶ ነበር፡፡ አክዓብም የቤቱን አዛዥ አብድዩን ጠራ፤ አብድዩ እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤልም የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ እርሱ መቶውን ነቢያት ወስዶ አምሳ አምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው ነበር፡፡ አክዓብም አብድዩን ‹‹በአገሩ መካከል ወደ ውኃው ምንጭ ሁሉና ወደ ወንዝ ሁሉ ሂድ፤ እንስሶችም ሁሉ እንዳይጠፉ ፈረሶችንና በቅሎችን የምናድንበት ሣር ምናልባት እናገኛለን›› አለው፡፡ ሁለቱም የሚመለሱበትን አገር ተካፈሉ፤ አክዓብም ለብቻው በአንድ መንገድ አብድዩም ለብቻው በሌላ መንገድ ሄዱ፡፡
አብድዩም በመንገድ ሲሄድ እነሆ ኤልያስ ተገናኘው፤ አብድዩም አወቀው፣ በግምባሩም ተደፍቶ ‹‹ጌታዬ ሆይ! ኤልያስ አንተ ነህን? አለ፡፡ ኤልያስም ‹‹እኔ ነኝ ሄደህ ለጌታህ ‹ኤልያስ ተገኝቶአል› በል›› አለው፡፡ አብድዩም ‹‹እኔን ባሪያህን እንዲገድል በአክዓብ እጅ አሳልፈህ ትሰጠኝ ዘንድ ምን ኃጢአት አድርጌአለሁ? አምላክህ ሕያው እግዚአብሔርን! ጌታዬ ይፈልግህ ዘንድ ያልላከበት ሕዝብ ወይም መንግሥት የለም፤ ሁሉም ‹‹በዚህ የለም›› ባሉ ጊዜ አንተን እንዳላገኙ መንግሥቱንና ሕዝቡን አምሎአቸው ነበር፡፡ አሁንም እነሆ ‹ሂድ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር› ትለኛለህ፡፡ እኔም ከአንተ ጥቂት ራቅ ስል የእግዚአብሔር መንፈስ አንሥቶ ወደማላውቀው ስፍራ ይወስድሃል፤ እኔም ገብቼ ለአክዓብ ስናገር ባያገኝህ ይገድለኛል፤ እኔም ባሪያህ ከትንሽነቴ ጀምሬ እግዚአብሔርን እፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤል የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ መቶውን የእግዚአብሔር ነቢያት ወስጄ አምሳ አምሳውንም በዋሻ ውስጥ ሸሽጌ እንጀራና ውኃ የመገብኋቸው ነበር፡፡ ይህ ያደርግሁት ነገር በውኑ ለጌታዬ አልታወቀህምን? አሁንም ‹ሄደህ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር ትላለህ› እርሱም ይገድለኛል›› አለው፡፡
ኤልያስም ‹‹በፊቱ የቆምሁት የሠራዊት ጌታ ሕያው እግዚአብሔርን! እኔ ዛሬ ለእርሱ እገለጣለሁ›› አለ፡፡ አብድዩም አክዓብን ሊገናኘው ሄደ፣ ነገረውም፤ አክዓብም ኤልያስን ሊገናኘው መጣ፡፡ አክዓብም ኤልያስን ባየው ጊዜ ‹‹እስራኤልን የምትገለባብጥ አንተ ነህን?›› አለው፡፡ ኤልያስም ‹‹እስራኤልን የምትገለባብጡ፣ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ትታችሁ በኣሊምን የተከተላችሁ፣ አንተና የአባትህ ቤት ናችሁ እንጂ እኔ አይደለሁም›› አለው፡፡ 1ኛ ነገ 18፡1-20፡፡
ቅዱስ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥነቱን ትቶ የኤልያስ ቀደ መዝሙሩ ሆኖ በነቢይነት እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኖረ፡፡ በንጉሥ ኢዮሳፍጥ ዘመንም ትንቢትን ተናገረ፡፡ እግዚአብሔርም ስለ ትንሣኤና ስለ ፍርድ ቀን በቃሉ ነገረው፡፡ ሁለተኛም ከእስራኤል ልጆች የሚሆነውን ከአሕዛብም ለቀሩት አጸናቸው፣ አብዝቶ መከራቸው፣ ገሠጻቸውም፡፡ የትንቢቱም ወራት ሲፈጸም በዚህች ዕለት በሰላም በፍቅር አንድነት ዐርፏል፡፡ የትንቢቱም ወራት ሃያ ዓመት ነው፡፡ ይኸውም ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በ900 ዓመት ነው፡፡
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የሶርያ ክርስቲያኖች የኑሲሱን የአቡነ ጎርጎሪዮስን የዕረፍቱን በዓል በደማቅ ሁኔታ ያከበራሉ፡፡ በእኛ አቆጣጠር ግን ዕረፍቱ ጥር 21 ቀን ነው፡፡ (የጥር ሃያ አንዱን ይመለከቷል፡፡)
+ + +
ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ፡- ሦስት ዓመት እንኳን ሳይሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ታላቅ ሰማዕትነትን የተቀበለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አባቱ ቆዝሞስ (ስምዖን) እናቱ ኢየሉጣ ይባላሉ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ በኅዳር 15 ቀን የተወለደ ሲሆን ሀገሩ በታችኛው እስያ ልዩ ስሙ ሀንጌቤን ይባላል፡፡ ዘመኑ ዘመነ ሰማዕታት ነበርና መምለኬ ጣዖት የሆነው ንጉሥ እስክንድሮስ ቅድስት ኢየሉጣን ‹‹ለጣዖቴ ስገጂ›› ብሎ አስገደዳት፡፡ እርሷም ‹‹ሕፃኑ ልጄ መጥቶ ይመስክር›› ብላ ስትናገር ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጠራና ተጠየቀ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስም ‹‹ለጣዖት አንሰግድም፣ ዘላለማዊ የሆነ የማይሻር አምላክ ስላለ ለእርሱ ነው የምንሰግደው›› ብሎ የአምላኩን ክብር በሕፃን አንደበቱ መሰከረ፡፡ ሕፃኑም ይህንን በመሰከረ ጊዜ ዕድሜው ገና ሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ነበር፡፡
ነቢዩ ቅዱስ ዳዊትም ‹‹ከልጆችና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ›› ሲል እንደተናገረ (መዝ 10፡2፣ 118፡130) መድኃኔዓለም ክርስቶስም በቅዱስ ወንጌሉ ላይ ‹‹አባት ሆይ፣ የሰማይና የምድር ጌታ ይህን ከጥበበኞችና ከአስተዋዮች ሰውረህ ለሕፃናት ስለ ገለጥህላቸው አመሰግንሃለሁ›› ያለውን ቃል በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ሕይወት ተግባራዊ ሆኖ አይተነዋል፡፡ ማቴ 11፡27፡፡ በነቢዩም ትንቢት መሠረት በበዓለ ሆሣዕና ዕለት በእናታቸው እቅፍና ጀርባ ላይ የነበሩ እምቦቀቅላ ጨቅላ ሕፃናት ‹‹ሆሣዕና፤ በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው›› በማለት ጌታችንን አመስግነውታል፡፡
እንደዚሁ ሁሉ ቅዱስ ቂርቆስም በከሃዲው ንጉሥ ፊት የጌታችንን ክብር በመሰከረ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ 40 ጋን ውኃ የሚይዝ በርሜል አስጥዶ 40 ቀን ሙሉ እሳት አስነድዶ ቅንጭብ፣ ዘይት፣ ዝፍጥና ሌላም በእጅጉ የሚጎዱ ነገሮችን በውስጡ ጨምሮ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ወደዚያ እቶኑ እሳት እንዲከቷቸው አዘዘ፡፡ ንጉሡ እስክንድሮስ ጭፍሮቹን "ሰም፣ ጨው፣ ባሩድ፣ሙጫ፣ እርሳስ፣ ብረትን፣ ቅንጭብ፣ ቁልቋል ጨምሩበት" ብሎ አዘዛቸው፡፡ ጭፍሮችም ያዘዛቸውን ከፈጸሙ በኀላ መጥተው "ያዘዝከንን ሁሉ ጨምረንበት ነዶ ፈልቷል" አሉት፡፡ "ድምፁም እንደ ነጎድጓድ ይሰማል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ያንፀባርቃል፡፡ የፍላቱም ኃይል 14 ክንድ ያህል እየዘለለ ይወጣል፡፡ በውስጡ የሚጣሉትን ሰዎች እዘዝ" አሉት፡፡ ያንጊዜም ህፃን ቂርቆስንና እናቱን ኢየሉጣን ይዘው ከእስር ቤት አወጧቸው፡፡ በክርስቶስ ስም ስላመኑ በእስር ቤት አግብተው አስረዋቸው ነበርና ፍላቱ ወደ ላይ በሚዘል በብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ሲወስዷቸው በዚያን ጊዜም እልፍ ከአንድ ሺህ አራት መቶ ሰዎች እንዲወጡና በፈላው የብረት ጋን ውስጥ የቅዱሳንን አሟሟት እንዲያዩ ሹሙ አዘዘ፡፡ ቅድስት ኢየሉጣም የፍላቱን ግርማ ባየች ጊዜ ተሸበረች፡፡ ተጠብቆላት ያለውንም ዋጋ ትታ ልትክድ ፈለገች፡፡ ቅዱስ ቂርቆስም ይህን ባወቀ ጊዜ "እናቴ ሆይ ከብረት ጋን ግርማ የተነሳ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ" እያለ ከብሉይና ከሐዲስ እየጠቀሰ እንድትጸና አስተማራት፡፡
"ነገር ግን እናቴ ሆይ አናንያንና አዘርያን፣ ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከዕቶን እሳት እንዳወጣቸው እወቂ፤ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ውስጥ ሊያድነን ይችላል፡፡ እናት ሆይ ከሚያልፈው ከዚህ ዓለም ጭንቅ ልታመልጭ በሚያልፈው በዘለዓለም እሳት ልትቀጭ ትሻለች፡፡ እናት ሆይ ይህን አትሺ፤ ይቅርብሽ አሁን እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ ሶስናን ከሀጢያተኞች እጅ ያዳናት እኛንም ከብረት ጋን ያድነናል፡፡ ዳንኤልን ከአንበሶች አፍ ያዳነ እርሱ ያድነናል፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችን ልንፈፅም ፈቅዶም እንደሆነ የኢዮብን ነፃነት (ትእግስት) ልናገኝ ይገባናል፡፡ እርሱ ልጆቹንና ሚስቱን ያገኘው ገንዘብ ሁሉ አጥቶ በመጨረሻው ሰውነቱን አጥቶ ነበርና ምንም ምንም የቀረበለት አልነበረምና እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ ከማለት በቀር ያለው ነገር የለም እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔርም ወሰደ አለ፡፡ የእግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለም ይመስገን አለ፡፡ እኛም ይህንን መከራ ልንታገስና የተጠበቀልንን ልንከተል ይገባናል..." እያለ አብዝቶ መከራት፡፡ ነገርግን በዚህም ምክር እናቱን መመለስና ለሰማዕትነት ማዘጋቸት አልቻለም፡፡ ከዚህ በኋላ ቂርቆስ ዓይኖቹን ወደሰማይ አቅንቶ መጸለይ ጀመረ፡፡ "እግዚአብሔር ሆይ ይህች ባርያህ ከምትክድ ከህይወት መፅሐፍ እኔን ፋቀኝ አለ፡፡ አቤቱ ይህነን ነገር ልታደርግ አይገባህም፤ አቤቱ እርሻውን ልታቃጥል ፍሬውንም ልትባርክ ትወዳለህን፡፡ አቤቱ እንጨቱን ቁረጡና አንድዱት ቅጠሉን ጠብቁ ብለህ ልታዝ አይገባህም፡፡ እንጨቱንም ቅጠሉንም ጠብቁ ብለህ እዘዝ እንጂ ይህ አይገባህም ያመነብህ ሁሉ ይህን ያየ ዘንድ፡፡ ማዳን የሚችል አምላክ ኑሮአቸው ቢሆን ከዚህ ከእሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ እንዳይጠራጠር፡፡ ዲያብሎስ ከባለስልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ ቅዱሳኑም ድል ነሳኋቸው ብሎ እንዳይመካ፣ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ እንዳይል አቤቱ የኃይል መንፈስ ለእናቴ ስጣት አበርታት..." ብሎ ጸለየ፡፡ በዚያን ጊዜ ዲያብሎስ ከእርሷ ሸሽቶ ሄደ፡፡ ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ እንዲህ አለች፡- በመንግስተ ሰማያት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ጌታህ ኃይል ስጠኝ፡፡ የሚጠብቀንን ገድላችንን እንፈፅምና ድል እንነሣ" አለችው፡፡ የብረት ጋኑን ሲነድ ሳየው በምንጭ ላይ በዝቶ እንደሚወርድ ጠል ሁኖ አየዋለሁና፡፡ ቅዱሳንም ይህንን ሲነጋገሩ አንስተው ከብረት ጋኑ ውስጥ ጨመሯቸው፡፡ በውስጡም አንገትን የሚቆለምም ልብን የሚያጣምም ሆድን የሚሰነጥቅ ሥርንም የሚበጥስ መሣሪያ ነበረበት፡፡ ወዲያውም የራማው ልዑል ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ ከሰማይ ወረደና የብረት ጋኑን እሳት ፈጽሞ አበረደው፡፡ ከቅዱሳንም አንዱን እንኳን ሳይነካው የብረት ጋን ማቃጠሉና መፍላቱ ፀጥ አለ፡፡ እንደ ውኃም ሆነ፡፡
ንጉሡም እሳቱ እንዳልጎዳቸው ሲያውቅ ከዚያ አውጥቶ በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አፍና አፍንጫ መርዝ ከተተበት፣ ነገር ግን መርዙ ምንም አልጎዳውም እንዳውም ምግብ ሆነው፡፡ ዳግመኛም ጨውና በርበሬ በዐይኑ አነደደበት፡፡ አሁንም ምንም አልነካውም፡፡ ከዚህም በኀላ ሹም እስክድሮስም አስራ አራት የተሳሉና የጋሉ ብረቶች ያመጡ ዘንድ ዳግመኛ አዘዘ፡፡ ሰባቱን በእናቱ አካል ሰባቱን በሱ አካል ውስጥ ይተክሉ ዘንድ ከነዚሁም ሁለቱን በጆሮዎቹ ሁለቱን በዓይኖቹ ሁለቱን በአፍንጫዎቹ አንዱን በልቡ ይተክሉ ዘንድ አዘዘ፡፡በሕፃኑም ላይ ሹሙ እንዳዘዘው አደረጉበት፡፡ አሁንም ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና ፈወሳቸው፡፡
ዳግመኛም የሕጻኑን እራስ ከነቆዳው ገፈው በእሳት ውስጥ ይጨምሩ አንድ ሹም አዘዘ፡፡ እንዲሁም አደረጉበት፡፡ ዳግመኛም ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ መጥቶ ይህንን መከራ ከሕፃኑ አራቀለት፡፡ ዳግመኛም ሹሙ በመቃን ውስጥ ጨመረው በገመድ እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ከዚህም መከራ መልአኩ አዳነው፡፡ ሐምሌ 19 ቀን በዓሉን በታላቅ ድምቀት የምናከብረው ይህንን ሁሉ የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤልን ተራዳኢነት በማሰብ ነው፡፡
ንጉሡም በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በብዙ ጭንቅና ሥቃይ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ለ3 ዓመታት አሠቃያቸው፡፡ እነርሱም መከራን እየተቀበሉ በከሀዲው ንጉሥ ፊት የአምላካቸውን ስም እየጠሩ መሰከሩ፡፡ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና ክብሩን ይመሰክሩለት ዘንድ የቢታንያን ድንጋዮችና የበለዓምን አህያ አንደበት ከፍቶ ያናገረ አምላክ ሦስት ዓመት እንኳን ባለሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወር ሕፃን ልጅ ላይ አድሮ በወቅቱ የነበሩ ዓላውያን ነገሥታት ክብሩን እንዲያውቁ አደረገ፡፡
ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ሄሮድስ ላስፈጃቸው 144,000 የቤቴልሔም ሕፃናት አለቃቸው ነው፡፡ ይህስ እንደምን ነው ቢሉ ሄሮድስ ያስፈጃቸው እነኚያ እልፍ የቤቴልሔም ሕፃናት የተገደሉት ጌታችንን ለማግኘት በተደረገው ፍለጋ ምክንያት ስለሆነ ቅዱስ ቂርቆስን በመሞት ይተካከሉታል እርሱ ግን የአምላኩን ስምና ክብር በማስተማርና በመመስከር ሰማዕትነትን ስለተቀበለ በዚህ ይበልጣቸዋልና ለእነኚያ እልፍ የቤቴልሔም ሕፃናት አለቃ አድርጎ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሾሞታል፡፡ ቅዱስ ገድሉም እንደሚናገረው ‹‹መንገድ ጠራጊ ከተባለ ከዮሐንስ መጥምቅ በቀር ሴቶች ከወለዱዋቸው እንደ አንተ ያለ አልተገኘም›› በማለት ጌታችን በማይታበል ቅዱስ ቃሉ ታላቅ የሆነ ቃልኪዳኑን በመሐላ አጽንቶለታል፡፡ በመጨረሻም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጋድሎውን ፈጽሞ ጥር 15 ቀን በ3 ዓመት ከ1 ወር ከ3 ቀኑ አንገቱን በሰይፍ ተቆርጦ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡ ሲሰየፍም ከአንገቱም ደም፣ ውኃና ወተት የወጣ ሲሆን ሦስት አክሊላትም ወርደውለታል፡፡ ጌታችንም የመከራውን ጽናት የትዕግስቱን ብዛት አይቶ ከመከራ ሊያሳርፈው ፈቀደና ተገልጾለት ‹‹ሰላም ለከ ኦ ፍቁርየ ቂርቆስ›› አለው፡፡ ‹‹ሰላም ላንተ ይሁን፤ የመከራህን ጽናት፣ የትዕግስትህን ብዛት አይቼ ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍህ መጣሁ›› ብሎ ብዙ ቃልኪዳን ሰጠው፡፡ ‹‹…ስምህ በተጠራበት፣ ቤተመቅደስህ በታነጸበት፣ ስዕልህ ባለበት ቦታ ሁሉ የሕፃናት እልቂት፣ የከብት በሽታ፣ የእህል እጦት ርሀብ፣ ቸነፈር አይደርስም›› የሚል አስደናቂ ቃልኪዳንም ገብቶለታል፡፡ ሕፃኑም በምድር ላይ አልተቀበረም ይልቁንም ጌታችን በኤልያስ ሰረገላ ሥጋውን አሳርጎለታል፡፡ እናቱ ቅድስት ኢየሉጣም በጥር 16 ቀን ሰማዕትቷን በክብር ፈጽማለች፡፡ የቅዱስ ቂርቆስ ማኅበርተኞች የሆኑ ዓሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎች የጌታችንን ክብር እየመሰከሩ በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡
የቅዱስ ቂርቆስና ማኅበርተኞች የሆኑ የቅዱሳን ሰማዕታት ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!
ዳግመኛም ጥር 14 ቀን እነዚኽ ታላላቅ ቅዱሳን በዓመታዊ በዓላቸው ታስበው ውለዋል፡-
+ የዚህን ዓለም ሹመት ለመሾም ወደ ንጉሡ እየሄደ ሳለ ማዕበል የተፋው አንድ በድን ቢያገኝ በዚያው የዓለምን ኃላፊነትና የእርሱንም መሞት አስቦ የመነኮሰውና የሴትንም ፊት እንዳያይ ቃል ገብቶ በታላቅ ተጋድሎ የኖረው አቡነ አርከሌድስ ዕረፍቱ ነው፡፡ 
+ በ12 ዓመቷ ከከሃድያንን ነገሥታት ጋር ስለ እምነቷ ተጋድላ በሰማዕትነት ያረፈችው ቅድስት ምህራኤል ዕረፍቷ ነው፡፡ + መቋሚያቸው በሰው አንደበት የምትናገረውና የወይራ ዛፍ እንደተደገፉ ሳይንቀሳቀሱ 40 ዓመት ሙሉ የጸለዩት ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ አካለ ክርስቶስ ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ ዐፅማቸው ደብረ ዳሞ ያረፈው የወሎው አቡነ ዘድንግል ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ ዐፅማቸው ዋልድባ ዳልሻ የሚገኘው የትግራይ ተወላጁ አቡነ ምሥራቃዊ ልደታቸው ነው፡፡ 
+ ቅዱስ መክሲሞስ በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡ 
+ ቅድስት እምራይስ በሰማዕትነት ዐረፈች፡፡ 
+ ከተሰዓቱ ቅዱሳን ውስጥ አንዱና ዋነኛው የሆኑት ጻድቁ አቡነ አረጋዊ ልደታቸው ነው፡፡
ሰማዕቷ ቅድስት ምህራኤል፡- ይህችውም የከበረችና የተመሰገነች ቅድስት ምህራኤል ጠምዋህ ከሚባል አገር የተገኘች ታላቅ ሰማዕት ናት፡፡ ወላጆቿ ካህኑ አባቷ ዮሐንስና እናቷ ኢላርያ እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ደገኞች ናቸውና እርሷንም በሃይማኖት በምግባር ኮትኩተው አሳደጓት፡፡ መጀመሪያውንም ልጅ ስላልነበራቸው በስዕለት ከብዙ ዘመን በኋላ ነው ያገኟት፡፡ ስዕለታቸውም ደርሶላቸው ቅድስት ምህራኤልን ከወለዷት በኋላ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ አሳደጓት፡፡
ቅድስት ምህራኤልም 12 ዓመት በሆናት ጊዜ በላይዋ ባደረ በመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን መሥራት ጀመረች፡፡ ከሃዲው ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ በነገሠና አምልኮተ ጣዖትን በአዋጅ ባወጀ ጊዜ ቅድስት ምህራኤል ስለ ጌታችን አምላክነት መስክራ ሰማዕት መሆንን ተመኘች፡፡ ከዚህም በኋላ በቁርጥ ሀሳብ ተነሥታ ወደ ባሕር ዳርቻ በመሄድ በመርከብ ተሳፍራ ሄዳ ስሙ ፍልፍልያኖስ የሚባለው የዲዮቅልጥያኖስ መኮንን ዘንድ ደረሰች፡፡ በመርከብም ስትጓዝ ሌሎች ስለ ቀናች እምነታቸው ሰማዕትነትን ለመቀበል የተዘጋጁ ሰማዕታትን አግኝታ ከእነርሱ ጋር ነበረች፡፡ በመኮንኑም ፊት ቆማ እውነተኛውና ሊመለክ የሚገባው አምላክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ መሆኑን መሰከረች፡፡ መኮንኑም ስለ ታናሽነቷ ራርቶላት ከሌሎቹ ለይቶ ሊተዋት ወደደ፡፡ ነገር ግን ቅድስት ምህራኤል መኮንኑ እንደተዋት ዐውቃ የተመኘችውን ሰማዕትነት ሊያስቀርባት መሆኑን ባየች ጊዜ ዳግመኛ መኮንኑንና የረከሱ አማልክቶቹን በድፍረት ረገመችበት፡፡
ከዚህም በኋላ መኮንኑ በጣም ተቆጥቶ ጽኑ በሆኑ የተለያዩ ሥቃዮች አሠቃያት፡፡ ከቀናች ሃይማኖቷም ሸንግሎ ይመልሳት ዘንድ እንዳልተቻለው ሲያውቅ መርዛማ እባቦች፣ ጊንጦችና እፉኝቶች ወዳሉበት ጉድጓት ጣላት፡፡ ከቅድስት ምህራኤልም ጋራ ሌሎች ብዙ ሰማዕታት አብረው ተጣሉ፡፡ በዚህም ጊዜ የታዘዘ የእግዚአብሔር መልአክ ለቅድስት ምህራኤል ተገለጸላትና ከጌታችን ዘንድ የተሰጣትን ቃልኪዳን አስረከባት፡፡ ከዚህም በኋላ ነፍሷን ለእግዚአብሔር አሳልፋ ሰጥታ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች፡፡ ምእመናንም የከበረ ሥጋዋን መርዛማ እባቦችና ጊንጦች ካሉበት ቦታ አውጥተው በክብር ቀበሯት፡፡ በኋላም ወላጆቿ ልጃቸው ቅድስት ምህራኤል ስለ እምነቷ መስክራ በክብር ሰማዕት መሆኗን በሰሙ ጊዜ ከብዙ የሀገራቸው ሕዝብ ጋር መጥተው የከበረ ሥጋዋን አፍልሰው ወደ አገራቸው ወሰዱት፡፡ ያመረች ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው ሥጋውን በውስጧ ባኖሩ ጊዜ ከሰማዕቷ ቅዱስ ሥጋ ብዙ አስገራሚ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡
+ + +
አቡነ አርከሌድስ ግብፃዊ፡- በትውልዱ ከሮሜ ሀገር ከታላላቅ ወገኖች ነው፡፡ አባቱ ዮሐንስ እናቱ ሰንደሊቃ ሲባሉ ሁለቱም የእግዚአብሔርን ሕግ የሚጠብቁ እውነተኞች ነበሩ፡፡ ቅዱስ አርከሌድስም ዕድሜው 12 ዓመት በሆነው ጊዜ አባቱ ዮሐንስ ሞተ፡፡ በኋላም እናቱ ግን ሚስት ልታጋባው አሰበች እርሱ ግን ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ አባቱ በሕይወት ሳለ ንጉሡ የሾመው ነበርና እናቱ አሁንም ወደ ንጉሡ ሄዶ የአባቱን ሹመት ይቀበል ዘንድ አርከሌድስን መከረችው፡፡ ለንጉሡ የሚሰጥ እጅ መንሻንና አገልጋዮችን አድርጋ ብዙ ገንዘብ አስይዛ ላከችው፡፡ እርሱም በመርከብም ተጭኖ ሲሄድ ታላቅ ንፋስ ተነሣና ማዕበሉ አየለባቸው፡፡ መርከቡም ተሰበረ፡፡
ቅዱስ አርከሌድም አንዲት የመርከብ ስባሪ ሠሌዳ ላይ ተንጠልጥሎ ወደ የብስ ደረሰ፡፡ ከባህሩ ሲወጣ ማዕበል የተፋው አንድ በድን አገኘና ተቀምጦ ስለ በድኑ አለቀሰ፡፡ የዓለምን ኃላፊነትና እርሱም ከሞተ በኋላ አፈርነቱን አሰበ፣ ነፍሱንም ገሠጻት፡፡ ወደ ቀና መንገድ ይመራውም ዘንድ ወደ ጌታችን ለመነ፡፡ ረጅም መንገድ ተጓዘና ሶርያ ውስጥ በቅዱስ ሮማኖስ ስም ወደተሠራች አንድ ተራራማ ገዳም ደረሰ፡፡ ከገንዘቡም ከእርሱ ጋር የቀረውን ሁለት መቶ የወርቅ ዲናር ለአበ ምኔቱ ሰጠው፡፡ እንዲያመነኩሰውም ጠየቀው፡፡ መጀመሪያውኑ አርኬሌድስ ከመምጣቱ በፊት ለአበምኔቱ መንፈስ ቅዱስ የመምጣቱን ነገር አስረድቶት ነበርና እርሱ በደረሰ ጊዜ ደስ አለው፡፡ መነኮሳቱም ሁሉ ከጸለዩለት በኋላ አመነኮሰው፡፡
ከዚህም በኋላ የከበረ አርከሌድስ ጽኑ ተጋድሎ መጋደል ጀመረ፡፡ ሲጸልይ ይውላል ሲጸልይ ያድራል፤ ሁልጊዜ በየሰባቱ ቀን የሚጾም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም ሀብተ ፈውስን ሰጥቶት ብዙ ሕመምተኞችን ፈወሳቸው፡፡ ከዚህም በኋላ የሴቶችን ፊት ከቶ እንዳያይ ከጌታችን ጋር ቃል ገባ፡፡ ። እናቱም ለ12 ዓመት ያህል የልጇን ወሬ ምንም ስላልሰማች በእርሱ የሆነውን አላወቀችም ነበርና የሞተም ስለመሰላት እጅግ አዘነች፡፡ የእንግዶችና የመጻተኞች መቀበያ የሚሆን ቤት ሠርታ የመንገደኞች ማደርያ አደረገችው፡፡ በአንዲት ዕለት ያሳደረቻቸው እንግዶች የቅዱስ አርከሌድስን ዜና ሲናገሩ ሰማቻቸው፡፡ እንግዶቹም ስለ ቅድስናው፣ ስለ ተጋድሎው የሚያሳያቸውን ምልክቶችና ተአምራቶቹን፣ የመልኩንም ደም ግባት ሲነጋገሩ ሰምታ ልጇ እንደሆነ ዐወቀች፡፡
መንገደኞቹንም ስለ ሥራው ጠየቀቻቸውና ሥራውን ሁሉ ነገሯት፡፡ ልጇ በሕይወት እንዳለና ሕያው እንደሆነ ተረዳች፡፡ በዚያን ጊዜ ተነሥታ ወደ ከበረ ሮማኖስ ገዳም ሄደች፡፡ ወደ ልጇዋ ወደ ቅዱስ አርከሌድስ ‹‹እነሆ ፊትህን አይ ዘንድ ወድጄ እኔ እናትህ መጥቻለሁ›› ብላ መልእክት ላከች፡፡ ልጇ ቅዱስ አርከሌድም ‹‹ከቶ የሴቶችን ፊት እንዳላይ ከክብር ባለቤት ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃል ገብቻለሁና ቃልኪዳኔን ማፍረስ አይቻለኝም›› ብሎ መልሶ ወደእርሷ ላከ፡፡ እናቱም ‹‹ፊትህን ካላሳየኸኝ እኔ ወደ ዱር እሄዳለሁ፣ አራዊትም ይበሉኛል›› ብላ ላከችበት፡፡ ቅዱስ አርከሌድስም እናቱ ካላየችው እንደማትተወው እርሱም ለእግዚአብሔር የገባውን ቃልኪዳን ማፍረስ እንደማይቻለው ባወቀ ጊዜ ነፍሱን እንዲወስዳት ወደ ጌታችን ለመነ፡፡ ከዚህም በኋላ የበሩን ጠባቂ ‹‹እናቴን ወደእኔ ትገባ ዘንድ ፍቀድላት›› አለው፡፡ እናቱም ወደ ውስጥ በገባች ጊዜ ልጇን ቅዱስ አርከሌድስን ሙቶ አገኘችውና በታላቅ ድምፅ በመጮህ አለቀሰች፡፡ የእርሷንም ነፍስ ይወስድ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነች፡፡ ጌታችንም ልመናዋን ተቀብሎ ነፍሷን ወሰደ፡፡
እናትና ልጅም በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ካረፉ በኋላ የሁለቱን ሥጋቸውን ለይተው ሊቀብሯቸው ሲሉ የቅዱስ አርከሌደስ በድን በሰው አንደበት መናገር ጀመረ፡፡ ‹‹የእናቴን ሥጋ ከሥጋዬ አትለዩ በሕይወቷ ሳለች ታየኝ ዘንድ ልቧን ደስ አላሰኘሁምና›› የሚል ቃል ከአርከሌድስ በድን ወጣ፡፡ ይህንንም ቃል በሰሙ ጊዜ እጅግ አድንቀው እግዚአብሔርን ካመሰገኑት በኋላ ሁለቱንም በአንድ መቃብር ውስጥ ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም በቅዱስ አርከሌድና በእናቱ ሥጋ ላይ ታላቅ ፈውስን ገለጠና አስገራሚ ተአምራት መታየት ጀመሩ፡፡ በሞት ካረፈ በኋላ በድኑ አፍ አውጥታ የተናገረች ይህ ታላቅ ጻድቅ በስሙ የተሰየመው ትልቅ ገዳም ትግራይ ተንቤን ሀገረ ሰላም ይገኛል፡፡
+ + +
ቅድስት እምራይስ፡- ይኽችውም ቅድስት ከከበሩ ደገኛ ክርስቲያኖች የተወለደች ናት፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እየተማረች አደገች፡፡ በአንዲትም ዕለት ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ ወርዳ ሳለ ተይዘው ስለ ክርስቶስ ታስረው የሚሠቃዩ ሰማዕታትን አየች፡፡ እነርሱም ጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት ናቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ቅድስት እምራይስ ወደ መኮንኑ ጭፍራ ዘንድ ቀርባ ‹‹እኔም በእነዚህ ቅዱሳን አምላክ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝና ስሜን ከስማቸው ጋር ጽፈህ ወደ ሰማዕትነት አደባባይ አድርሰኝ›› አለቸው፡፡ እርሱም ስሟን ከሰማዕታቱ ስም ጋራ ጽፎ አብሮ አሰራትና በከሃዲው መኮንን ቁልቁልያስ ፊት አቆማት፡፡ መኮንኑም ለጣዖታቱ እንድትሰግድ በብዙ የስንገላ ቃላት አባበላት ነገር ግን ቅድስት እምራይስ የጌታችንን አምላክነት እየመሰከረች የመኮንኑን ጣዖታት ረገመችበት፡፡ መኮንኑም እጅግ ተቆጥቶ አንገቷን በሰይፍ አስረጠውና ሰማዕትነቷን በድል ፈጽማ የክብር አክሊልን ተቀዳጀች፡፡
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የከበረ ሕፃን የቅዱስ ቂርቆስ ማኅበርተኞች የሆኑ አራት ሺህ ሠላሳ አራት ሰዎች በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ ዜና ገድላቸው ከአባታቸው ከሕፃኑ ከቅዱስ ቂርቆስ ዕረፍት ጋር ጥር 15 ተጽፏል፡፡
የእጅግ የከበረ የቅዱስ ዱማቴዎስ ወንድም ቅዱስ መክሲሞስም ዕረፍቱ በዚሁ ዕለት ነው ነገር ግን ገድሉን በዚሁ ወር በ17 ከወንድሙ ታሪክ ጋር እንጽፈዋለን፡፡
የቅዱሳን ሰማዕታት ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!