Wednesday, January 30, 2019

ጥር 22-ወበዛቲ ዕለት

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 


ጥር 22-ዓለሙ ሁሉ የእግራቸውን ትቢያ ያህል እንኳን ዋጋ የሌለው የመነኮሳት ሁሉ አባት በገዳም ለሚኖሩ ቅዱሳን እንደ ኮከብ የሚያበሩላቸው ገድል ትሩፋታቸው በቃል ተነግሮ የማያልቅ እጅግ የከበሩ ርዕሰ መነኮሳት አቡነ እንጦንስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል በዓለ ሲመቱ ነው፡፡
ርዕሰ መነኮሳት አቡነ እንጦንስ፡- እንጦንስ አበ መነኮሳት በሌላኛው ስማቸው ‹‹የበረሃው ኮከብ›› እየተባሉም ይጠራሉ፡፡ ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ አቡነ እንጦንስ ገና በ7 ዓመታቸው ነው የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ተምረው አጠናቀው የጨረሱት፡፡ መልካም ትሩፋታቸውንና ታዛዥነታቸውን የልጅ አዋቂ መሆናቸውም በሁሉ ዘንድ በተሰማ ጊዜ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አባ ቲዎናስም የእንጦንስን የልጅነት ጸጋና ዕውቀት ተሩፋታቸውን ሰምተው መልእክተኞችን ልከው አስመጧቸው፡፡ ካስመጧቸውም በኋላ ዲቁና ሲሾሟቸው ‹‹ይህ ሕፃን በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናል፣ ዜናውም በዓለሙ ሁሉ ይዳረሳል›› በማለት ትንቢት ተናግረውላቸዋል፡፡ እንጦንዮስ (እንጦንስ) ግብፃዊ ወላጆቻቸው እጅግ ባለጸጎችና ደጋግ ነበሩ፡፡ ወላጆቻቸው ከሞቱ በኋላ አባ እንጦንስ የወላጆቻቸውን ሀብት ወርሰው ከአንዲት እኅታቸው ጋር መኖር ጀመሩ፡፡
አንድ ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው ወንጌል ሲነበብ ጌታችን ስለሀብታሙ ሰው የተናገረውን ምዕራፍ ሲነበብ አዳመጡ፡፡ ‹‹ልትጸድቅ ብትወድድ ሂደህ ያለህን ሁሉ ሽጥና ለድኆች ስጥ፤ መጥተህም ተከተለኝ በሰማያት መዝገብ ታከማቻለህ›› (ማቴ 19፡21) የሚለውን የጌታችንን ቃል በሰሙ ጊዜ ‹‹ይህ ስለእኔ የተነገረ ቃል ነው›› በማለት ከቤተ ክርስቲያን ወጥተው ወደ ቤታቸው በመሄድ ወላጆቻቸው ሲሞቱ ያወረሷቸውን ብዙ ንብረታቸውን በሙሉ ሸጠው መጸወቱ፡፡ የወረሱትንም 300 ሄክታር ወይም 12 ጋሻ መሬት ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች አከፋፈሉ፡፡ የቀረቻቸውን እኅታቸውንም ወስደው ሴቶች ገዳም አስገቧትና እሳቸውም ከመንደር ወጣ ብለው በመኖሪያ ቤታቸው አጠገብ በብሕትውና ሕይወት ብቻቸውን መኖር ጀመሩ፡፡
እንጦንስ አበ መነኮሳት በአንድ መቃብር ቤት ገብተው ኖሩ፡፡ ሰይጣናትም መጥተው ደብድበው ከመንገድ ላይ ጥለዋቸው ሄዱ፡፡ ከወደቁበት አንስተው ወደ ቤተ ክርስቲያን ወሰዷቸውና ጌታችን ፈወሳቸው፡፡ ተጋድሎአቸውንም እንደገና ጀመሩ፡፡ አሁንም ሰይጣናት በዱር አውሬዎች በአንበሳ፣ በተኩላ፣ በእባብና በጊንጥ እንተመሰሉ እየመጡ ይዋጓቸው ነበር፡፡ በዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ ምግባቸውን ያበስላሉ፡፡ ወደ በዓታቸውም ሰውን አያስገቡም ነበር-በውጭ ሆነው ያነጋግሯቸዋል አንጂ፡፡ እንዲህም ሆነው 20 ዓመት ተቀመጡ፡፡ ጌታችንም ተገልጦላቸው ወጥተው እንዲያስተምሩ አዘዛቸውና ወጥተው ደቀ መዛሙርትን ማፍራት ጀመሩ፡፡ የመከራ ዘመን በመጣ ሰዓት ሰማዕትነትን ለመቀበል ወደ እስክንድርያ ጎዳናዎች ወጥተው ታዩ፡፡ መኰንኑም እንዳይታዩ ብሎ መከራቸው ግን እሽ አላሉትም፡፡ ሰማዕትነት የእሳቸው ክፍል አልነበረምና ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ከተገደለ በኋላ በመልአኩ ትእዛዝ ወደ በዓታቸው ተመለሱ፡፡ ከዐረብ ነጋዴዎች ጋር ወደ ሩቅ ቦታ ሄደው በበረሃ ብቻውን መኖር ጀመሩ፡፡
አባ እንጦንስ በረሃ ለበረሃ ሲንከራተቱ አጋንንት ክፉኛ ይዋጓቸው ነበር፡፡ በረሃነቱም ጽኑ ነው፣ ከሐሩሩ ጽናት የተነሣ በቀትር ጊዜ ከደንጊያ ላይ ተልባ ቢያሰጡ ይቆላል፡፡ እርሳቸውም ከዚያ ሄደው ሲጋደሉ አጋንንት ጾር በማንሳት ግማሾቹ ‹‹ከዚህ በረሃ እንደምን ደፍረህ መጣህ?›› ሲሏቸው ሌሎቹ ደግሞ ተቀብለው ‹‹አዳም ከወጣበት ገነት እገባ ብሎ ነው…›› እያሉ ይዘብቱባቸው ነበር፡፡ አባ እንጦንስ ግን በፍጹም ትሕትና ይታገሷቸዋል፡፡ ‹‹መሆንማ ይሆን ብላችሁ ነውን? እናንተ ብዙ እኔ አንድ ብቻዬን፤ እናንተ ረቂቃን እኔ ግዙፍ፡፡ እናንተ ኀያላን እኔ ደካማ በኀይለ ክርስቶስ ብችላችሁ ነው እንጂ ያለዚያስ አልችላችሁም›› እያሉ በትሕትና ሲዋጓቸው ኖሩ፡፡ ከዕለታት ባንድ ቀን ‹‹ይኸን የአጋንንት ጾር አልቻልሁትም ልሂድ እንጂ›› ብለው ሲያስቡ አደሩ፡፡ በማለዳም ተነሥተው በትራቸውን ይዘው ከደጃፋቸው ላይ ቆሙ፡፡ እንዳይቀሩም ጾሩ ትዝ እያላቸው እንዳይሄዱም በዓታቸው እየናፈቃቸው አንድ እግራቸውን ከውስጥ፤ አንድ እግራቸውን ከአፍአ አድርገው ሲያወጡ ሲያወርዱ መልአኩ የሰሌን ቆብ ደፍቶ፤ የሰሌን መቋረፊያ ለብሶ፤ የሰሌን መታጠቂያ ታጥቆ ብትን ሰሌን ይዞ መጣ፡፡ ምን ሊያደርግ ይሆን? ሲሉም ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ ቆመ፡፡ ወዲያው ጸሎተ ወንጌልን፤ ነአኲቶን፤ ተሰሃለኒን፤ ደግሞ መጀመሪያ ለሥላሴ እጅ ነሳ፡፡ ከዚያ በኋላ አንድ አቡነ ዘበሰማያት ሰላሳ ስድስት ሰጊድ አድርሶ በመጨረሻ አንድ ጊዜ እጅ ነሥቶ ተቀመጠ፡፡ ወዲያው ያን ብትን ሰሌን አቅርቦ ይታታ ጀመር፡፡ ‹‹እንጦንስም እንግዲህማ የዚህን ፍጻሜ ሳላይ እንዴት እሄዳለሁ?›› ብለው ተቀምጠው ይመለከቱት ጀመር፡፡ ሰለስት ሲሆን ደግሞ ተነሥቶ አቡነ ዘበሰማያቱንም ሰጊዱንም ያንኑ ያህል አደረሰው፡፡ የቀሩትንም የሰዓቱንም የሠርኩንም እንደዚሁ አድርጎ አሳያቸው፡፡ ‹‹እንጦኒ ሆይ እንደዚህ ሥራ፤ ይህንን ከሠራህ ከአጋንንት ጠብ ትድናለህ›› አላቸው፡፡ እርሳቸውም የአጋንንትን ጦር መከላከያውን ሁሉ መልአኩ ባሳያቸው መሠረት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እንዲሁ የሚሠሩ ሆኑ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ስንፍናና የሰይጣን ውጊያ ወደሳቸው አልመጣም፡፡
ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም ከአባ እንጦንስ ይባረክ ዘንድ ብዙ ጊዜ ደብዳቤ ጻፈላቸው፡፡ እርሳቸውም ቸል ባሉት ጊዜ ልጆቻቸው ደግ ንጉሥ መሆኑን ስለነገሯቸውና ስለለመኗቸው አባ እንጦንስ ጽፈው በደብዳቤ ባርከውታል፡፡ የአፍርንጊያው ንጉሥም መጥተው እርሱንና ሠራዊቱን ሁሉ እንዲባርኳቸው በክርስቶስ መከራዎች አማጽኖ ደብዳቤ ጻፈላቸው፡፡ ጌታችንንም በጸሎት ሲጠይቁ ደመና መጥታ ወስዳ አደረሰቻቸውና ንጉሡንና ሕዝቡን ሁሉ ባርከዋቸዋል፡፡
አባታችን ሠላሳ ዓመት በሞላቸው ጊዜ ጌታችን በዕለተ ዓርብ የለበሰውን ልብስ አልብሷቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አባ እንጦንስ የአክሊለ ሦክ ምሳሌ የሆነውን ቆብን፤ የከለሜዳ ምሳሌ የሆነውን ቀሚስ፤ የሀብል ምሳሌ የሆነውን ቅናትን፤ እንዲሁም ሥጋ ማርያምን ከመልአክ ከተቀበሉ በኋላ ‹‹በዚህ ዓለም እኔ ብቻ ነኝን ወይስ ሌላም አለ?›› ብለው በጸሎት ወደ እግዚአብሔር አመለከቱ፡፡ ጌታችንም ‹‹አለ እንጂ፣ አንድ ጊዜ ተራምዶ ሁለተኛውን ሳይደግም የሚሠራውን ሥራ ዓለሙ ሁሉ ቢሰበሰብ የማይሠራው፣ በጸሎቱ ዝናም የሚያዘንም፣ ፀሐይን የሚያወጣ፤ እንደዚህ ያለ ወዳጅ አለኝ›› አላቸው፡፡ አባታችንም ‹‹ይኽን ሰው ለማየት ልሂድን ልቅር? ቢሉት እንዲሄዱ ፈቀደላቸው፡፡
የታዘዘ መልአክም እየመራ አባ ጳውሊ ካሉበት በዓት አደረሳቸው፡፡ እርሳቸውም ከአባ ጳውሊ ጋር ብዙ መንፈሳዊውን ነገር ተጨዋወቱ፡፡ ተጨዋውተውም ሲያበቁ አባ ጳውሊ ለአባ እንጦንስ ለብቻቸው በዓት ሰጧቸው፡፡ እንጦንዮስም ከዚያ ሆነው ጸሎታቸውን ሲያደርግ ዋሉ፡፡ ወትሮ ለአባ ጳውሊ ግማሽ ሰማያዊ ኅብስት ይወርድላቸው የነበረ ሲሆን ማታ ግን አንድ ሙሉ ኅብስት ወረደላቸው፡፡ አባ ጳውሊም በፈቃደ እግዚአብሔር ወደ እርሳቸው መምጣታቸውን ያን ጊዜ ዐወቁ፡፡ ወዲያው ያን ኅብስት ከሁለት ከፍለው እኩሌታውን ለራሳቸው አስቀርተው እኩሌታውን ለአባ እንጦንስ ሰጧቸው፡፡ ያን ተመግበው ሌሊት ሁለቱም በየሥራቸው ክብራቸው ተገልጾ ሲተያዩ አድረዋል፡፡ ጳውሊ ዓሥር ጣቶቹን እንደ ፋና ሆነው እያበሩለት አራቱን ወንጌል ሲያደርስ እንጦንዮስም እንደ ዓምደ ብርሃን ተተክለው ሲያበሩ ተያይተዋል፡፡ በዚያች ሌሊት ከዚያ ቦታ ጨለማ ጠፍቶ አድሯል፡፡
በነጋው ሠለስት እላፊ ሲሆን ጸሎታቸውን አድርሰው ሲያበቁ ተገናኝተው ሲጨዋወቱ ጳውሊ እንጦንዮስ ያረጉትን ቆብ አይተው ‹‹ይህ ከማን አገኘኸው?›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ‹‹እርሱ ባለቤቱ ሰጠኝ›› አሉ፡፡ ጳውሊም የጌታችንን ቸርነት ያደንቁ ጀመር፡፡ እንጦንዮስም ‹‹እስኪ በኔ ብቻ የሚቀር እንደሆነ ለሌላም የሚያልፍ እንደሆነ አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ሲያመለክቱ ወዲያው ተገለጸላቸውና ደስ አላቸው፡፡ ‹‹ምን አየህ?›› ቢሏቸው ‹‹ነጫጭ ርግቦች በጠፈር መልተው አንተ እየመራሃቸው ተከትለውህ ሲሄዱ አየሁ›› አሏቸው፡፡ ‹‹ይህስ ምንድን ነው?›› ቢሏቸው ‹‹እሊህማ በዚህ በቆቡ የምትወልዳቸው ንጹሐን ጻድቃን ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ ‹‹ሁለተኛ አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ካመለክቱ በኋላ አዝነውና ተከፍተው ተመለከቷቸው፡፡ ‹‹ምነው?›› ቢሏቸው ‹‹በክንፋቸው ጥቁር ተቀላቅሎባቸው አየሁ›› አሉ፡፡ ‹‹ምንድን ናቸው?›› ቢሏቸው ‹‹ጽድቅና ኀጢአት እየቀላቀሉ የሚሠሩ ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ካዘኑ በኋላ ‹‹ሦስተኛም አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ አባ ጳውሊም ለሦስተኛ ጊዜ ካመለከቱ በኋላ በድንጋጤ ቃላቸውን ከፍ አድርገው ጮኹ፡፡ አባ እንጦንስም ‹‹ምነው?›› ቢሏቸው አባ ጳውሊ እንዲህ አሉ፡- ‹‹ነገር ግን በመጨረሻ ዘመን የሚነሡቱ እንደ ቁራ ጠቁረው አየሁዋቸው›› አሉ፡፡ ‹‹ምንድን ናቸው?›› ቢሏቸው ‹‹ሀሳሲያነ ሢመት (ሹመት ፈላጊዎች)፣ መፍቀሪያነ ንዋይ (ገንዘብ የሚወዱ) እና ከመኳንንትም ጋር በጥዋት ማዕድ የሚቀመጡ በፍጻሜ ዘመን የሚነሡ ኀጥአን ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ ይህን ጊዜ አባ እንጦንስ ‹‹ያለ ንስሓ ባይጠራቸው እስኪ አመልክትልኝ›› አሉ፡፡ አባ ጳውሊም አመለከቱ ነገር ግን የዚህ ምላሽ አልመጣላቸውም፡፡
ከዚህ በኋላ አባ ጳውሊ ስለ ቆቡ አባ እንጦንስን ‹‹እንግዲህ ይህን ከራስህ ያደረግኸውን ለኔ ስጠኝ ላንተ ሌላ ሠርተህ አድርግ›› አሏቸው፡፡ አባ እንጦንስም ‹‹ይህንንስ እንዳልሰጥህ ከባለቤቱ ተቀብዬዋለሁ፡፡ ነገር ግን ሥራውን ለምጄዋለሁ ሌላ ሠርቼ ላምጣልህ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ‹‹እንግዲያስ አትዘግይ ቶሎ ሠርተህ አምጣልኝ›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ሠርተው ይዘው ሲመጡ ጳውሊ ዐርፈው ነፍሳቸውን መላእክተ ብርሃን ይዘዋት ሲያርጉ ተመለከቱ፡፡ መላእክቱም ‹‹ጳውሊ ዐርፏልና ሂደህ ቅበረው›› አሏቸው፡፡ ‹‹ይህንሳ የያዝኩትን ቆብ ልተወውን?›› ቢሏቸው፡፡ ‹‹አትተው አድርግለት›› ብለው መለሱላቸው፡፡ ይህም በምንኩስና የሠሩት ሥራ ከንቱ እንዳይደለ ለማጠየቅ ነው፡፡ አባ እንጦንስም ቢሄዱ አባ ጳውሊ መጽሐፋቸውን ታቅፈው፣ አጽፋቸውን ተጎናጽፈው፣ ከበዓታቸው ዐርፈው አገኟቸው፡፡ ከራስጌአቸው ቆመው ሲያለቅሱ ሁለት አንበሶች መጡ፡፡ ‹‹የመቃብሩን ነገር እንደምን ላድርግ?›› እያሉ ሲጨነቁ አንበሶቹ በእጃቸው እንደመጥቀስ አድርገው የመቃብራቸውን ቦታ አሳዩአቸው፡፡ እርሳቸውም ለክተው ሰጧቸው፡፡ አንበሶቹም ከቆፈሩላቸው በኋላ አባ ጳውሊን ቀብረው ‹‹እንግዲህ ከዚህ እኖራለሁ›› ብለው አሰቡ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ‹‹በዚህ መኖር አይሆንልህም ሂድ›› አላቸው፡፡ አጽፋቸውንና መጽሐፋቸውን ይዘው ሄደው እስክንድርያ ደርሰው ለሊቀ ጳጳሱ ለቅዱስ አትናቴዎስ ያዩትንና የሆነውን ሁሉ ነገሯቸው፡፡ አቡነ አትናቴዎስም ‹‹ልሄድና ከዚያ ልኑር?›› ሲሏቸው ‹‹አይሆንልህም አትሂድ እኔም አስቤ ነበር ነገር ግን የማይሆንልኝ ሆኖ መጣሁ እንጂ›› አሏቸው፡፡ ‹‹ባይሆን ለበረከት ያህል አጽፊቱን ጥለህልኝ ሂድ›› ብለው ሲለምኗቸው ትተውላቸው ሄዱ፡፡
አባ እንጦንስ ራሳቸውን ዝቅ በማድረግና በፍጹም ትሕትናቸው ይታወቃሉ፡፡ ምንም እንኳ ታላቅና በትሩፋት የበለጸጉ ቢሆኑም በጳጳሳትና በካህናት ፊት ራሳቸውን በትሕትና ዝቅ አድርገው እጅ ይነሷቸው ነበር፡፡ ዲያቆንም ቢሆን ወደ እርሳቸው በመጣ ጊዜ ከእርሱ ጠቃሚ ነጥብን ለማግኘት ይሞክራሉ፤ ላገኙትም ዕውቀት ሳያመሰግኑ አያልፉም፡፡ የእርሳቸውንም ምክር ሽተው ለሚመጡ ሁሉ እጅግ ጠቃሚ የሕይወት ምክሮችን ይሰጣሉ፡፡ ዓለምን ንቆ ገንዘብ ስለመውደድ ከመነኮሰ በኋላ ለድሆች አከፋፍሎ ለራሱም ጥቂት ንብረት ያስቀረ አንድ ወንድም ወደ አባ እንጦንስ መጣ፡፡ አባ እንጦንስም ይህን ካወቁ በኋላ እንዲህ አሉት፡- ‹‹መነኩሴ ለመሆን ከፈለግህ ወደ መንደር ሂድና ጥቂት ሥጋ ገዝተህ ራቁትህን በሰውነትህ ላይ ተሸክመህ ተመለስና ወደእኔ ና›› አሉት፡፡ ያም ወንድም ይህን ባደረገ ጊዜ ወፎችና ውሾች በሰውነቱ ያለውን ሥጋ ለመብላት ሲሉ በሰውነቱ ላይ በማንዣበብ እየሞነጨሩ አቆሰሉት፡፡ በደረሰም ጊዜ አባ እንጦንስ እንዳዘዙት ማድረጉን ጠየቁት፡፡ እርሱም የቆሰለውን ሰውነቱን ባሳያቸው ጊዜ እንጦንስ ‹‹ዓለምን ከናቁ በኋላ ገንዘብ የሚመኙትም እንደዚሁ በአጋንንት ይገደላሉ›› አሉት፡፡
አቡነ እንጦንስ ዕረፍታቸው በደረሰ ጊዜ ዕለተ ሞታቸውን ዐውቀው ደቀ መዛሙርቶቻቸውን ሲሰናበቱ እንዲህ ብለው መከሯቸው፡- ‹‹ይህ ከእናንተ ጋር የማደርገው የመጨረሻው ግንኙነት ነው፡፡ በዚህም ሕይወት ዳግመኛ እንዳንተያይ ዐውቃለሁ፡፡ አሁን እኔ የምሞትበት ጊዜ ነው፡፡ ከጥረታችሁ ግዴለሽ አትሁኑ፡፡ በብሕትውና ሕይወት ፍጹም ተስፋ አትቁረጡ፡፡ ዕለት ዕለት እንደምትሞቱ ሆናችሁ ኑሩ፡፡ አስቀድሜ እንደተናገርኩት ነፍስን ከርኩስ አሳቦች ለመጠበቅ በሥራ ትጉ፡፡ ቅዱሳንን ምሰሉ፡፡ ቅድስና የሌለውን የስንፍና ትምህርታቸውን ታውቃላችሁና ወደ መናፍቃን አትቅረቡ፣ ኑፋቄያቸው ለማንም ግልጽ ነውና፡፡››
ከዚህም በኋላ ጊዜ ዕረፍታቸው ሲደርስ ጌታችን ተገልጦላቸው ቃልኪዳን ገባላቸው፡፡ እርሳቸውም ለልጃቸው ለመቃርስ ስለ ወደፊቱ መነኮሳትና ገዳማት ትንቢትን ነገሩት፡፡ ወደፊት መነኮሳት ከበዓታቸው እየወጡ በዓለም እንደሚቅበዘበዙ ተናገሩ፡፡ ዕረፍታቸው በደረሰ ጊዜ በትራቸውን ለልጃቸው ለመቃርስ፣ ምንጣፋቸውን ለአቡነ አትናቴዎስ፣ የፍየል ሌጦ አጽፋቸውን ልጃቸው ለሊቀጳጳሱ ለሰራብዮን እንዲሰጡ አዘዙና በ120 ዓመታቸው በ356 ዓ.ም ጥር 22 በታላቅ ክብር ዐረፉ፡፡
ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን አሜን!
+ + + 


ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል፡- ኢዮር፣ ራማ እና ኤረር የተባሉ ሦስት የመላእክት ከተሞች አሉ፡፡ እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክት ከፈጠራቸው በኋላ በነገድ 100 በአለቃ 10 አድርጎ በሦስቱ ሰማያት አስፍሯቸዋል፡፡ ኢዮርን በ4፣ ራማን በ3፣ ኤረርንም በ3 ከፍሎ ነው በዓሥሩ ከተማ ያሰፈራቸው፡፡
በዚህም መሠረት ኢዮርን ላይና ታች አድርጎ በ4 ከተማ ከፍሏታል፡፡ በእርሷ ያሉትን መላእክትን በ40 ነገድ 4 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያው ነገድ ‹‹አጋእዝት›› ይባላሉ፡፡ አለቃቸው ሣጥናኤል ነበር፤ እርሱም የመላእክትን ሁሉ ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ያሳርግ ነበር፡፡ ከክብሩ ሲዋረድ ቅዱስ ሚካኤል በምትኩ ተሹሞበታል፡፡ ሁለተኛው ነገድ ‹‹ኪሩቤል›› ይባላሉ፡፡ እነርሱም መንበረ ሥላሴን ይሸከማሉ፡፡ የቀሳውስት አምሳል ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ሰብና ገጸ አንበስ ናቸው፡፡ በሦስተኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ሱራፌል ይባላሉ፡፡ የዲያቆናት አምሳል ናቸው፡፡ በትንቢተ ኢሳያስ በምዕራፍ 6 ላይ የተገለጹትና ኢሳያስን ከለምጹ እንዲፈወስ ያደረጉት ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ላህምና ገጸ ንስር ናቸው፡፡ (በነገራችን ላይ ‹‹ከሩቤል›› ወይም ‹‹ሱራፌል›› የሚባሉ የግለሰብ መጠሪያ ስሞች ስህተት ናቸው፡፡ አንደኛ እነዚህ ስሞች የብዙ መላእክት መጠሪያን የሚወክሉ ናቸው፡፡ ለአንዱ ሲሆን ‹‹ኪሩብ፣ ሱራፊ›› ይባላል፡፡ ‹ኪሩቤል› ወይም ‹ሱራፌል› ማለት ግን የብዙ ቁጥራቸው መጠሪያ ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የቅዱሳን መላእክትን ስም እንዳለ በቁሙ ወስዶ ለግል መጠሪያ ስም ማዋል ተገቢ አይደለም፡፡ ‹‹ወለተ ሚካኤ፣ ክብፈ ገብርኤል….›› እየተባሉ ይሰየማሉ እንጂ ቀጥታ ‹ሚካኤል›፣ ‹ገብርኤል› እያሉ ሰዎችን መሰየም ስህተት ነው፡፡ 4ኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ኃይላት ይባላሉ፡፡ የእሳት ሰይፍ ይዘው በሥሉስ ቅዱስ ፊት የሚቆሙ ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት የዛሉና የደከሙ ክርስቲያኖችን የሚያበረታቱ ናቸው፡፡ አለቃቸውም ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡)
ዳግመኛም እግዚአብሔር በራማ ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹አርባብ›› ይባላሉ፡፡ የሥላሴ እልፍኝ አስከልካዮች ናቸው፡፡ የእግዚአብሔርን መንበር በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ ሁለተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹መናብርት›› ይባላሉ፡፡ ለእግዚአብሔርን እጅግ ቅርብ የሆኑ ናቸው፡፡ የመብረቅ ጋሻቸውን የእሳት ጦራቸውን ይዘው የሥላሴ ጋሻ ጃግሬዎች ሆነው በተጠንቀቅ ይቆማሉ፡፡ የሰውን ችግር ለእግዚአብሔር ያቀርባሉ፡፡ መዝ 88፡6፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሦስተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹ሥልጣናት›› ይባላሉ፡፡ መላውን ፍጥረት ለመጠበቅ ሥልጣን የተሰጣቸውና የምጽአት ዕለት አዋጅ ነጋሪዎች ናቸው፡፡ ዳን 12፡1፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሱርያል ነው፡፡
ዳግመኛም እግዚአብሔር በኤረር ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹መኳንንት›› ይባላሉ፡፡ የስላሴ የእሳት ባለ ቀስት ናቸው፡፡ የሰው ልጅ ልዩ ጠባቂዎች ናቸው፤ በተለይ በአደጋ ጊዜ ሎጥን እንዳዳኑት ፈጥነው ይደርሳሉ፡፡ በዕለተ ምጽዓት የሰውን ሁሉ ዐፅም ሰብስበው ለትንሣኤ ዘጉባኤ ያበቃሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሰዳካኤል ነው፡፡ ሁለተኛዎቹ ‹‹ሊቃናት›› ይላሉ፡፡ የሥላሴ የእሳት ፈረሶች ናቸው፡፡ በእሳት ፈረስ ይመላለሳሉ፡፡ እነዚህም 24ቱ ካህናተ ሰማይ ሲሆኑ አለቃቸው ቅዱስ ሰላታኤል ነው፡፡ በኤረር ከተማ የሰፈሩት ሦስተኛዎቹ ‹‹መላእክት›› ይባላሉ፡፡ ፍጥረትን ሁሉ የሚጠብቁ ናቸው፡፡ አለቃቸው ቅዱስ አናንኤል ነው፡፡ በእነዚህ የማይጠበቅ ፍጥረት የለም፡፡ ከአዝርእት ጀምሮ ሁሉን ይጠብቃሉ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙ 7 መላእክትን አየሁ›› (ራዕ 8፡2) እንዳለ ሊቃነ መላእክት በቁጥር 7 ናቸው፡፡ እነርሱም፡- ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል፣ ቅዱስ ራጉኤል፣ ቅዱስ ዑራኤል፣ ቅዱስ ፋኑኤል እና ቅዱስ አፍኒን ናቸው፡፡
‹‹ዑራኤል›› የሚለው ስም ‹ዑር› እና ‹ኤል› ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል›› ማለት ትርጉሙ ‹‹የብርሃን ጌታ፣ የአምላክ ብርሃን›› ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዑራኤል ከ7ቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነው፡፡ በመሆኑም መጽሐፈ ሄኖክ እንደሚገልጸው መባርቅት ለጥጋብና ለበረከት እንዲበርቁ ነጎድጓድም ለሰላም እንዲሆን ያሰማራል፡፡ ምሥጢረ ሰማይንና ሰማያዊውን ዕውቀት ሁሉ ለሄኖክ የገለጸለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ የፀሐይን፣ የጨረቃን፣ የከዋክብትንና የሰማይ ሠራዊትን ብርሃንን የሚመራው ይኸው ገናና መልአክ ነው፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ 28፡13፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሆኖ በተሰቀለ ጊዜ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨው ይኸው ገናና መልአክ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ዕውቀት ተሠውሮበት ለነበረው ለኢትዮጵያዊው ሊቅ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም በእመቤታችን ትእዛዝ ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል የተባለ መልአክ ሊረዳኝ መጣ፡፡›› መጽሐፈ ዕዝራ 2፡1፡፡ አምላካችን እግዚአብሔር የሕይወትና የይቅርታ ዝናም በምድራችን ላይ ያዘንብ ዘንድ እንዲሁም የእርሻችንን አዝመራ በዝናም አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ለምግብነት እንዲበቃ ከፈጣሪ ዘንድ ምሕረትን የሚለምን መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ሊቁ አባ ጊዮርጊስም በመልአኩ አማላጂነት እጅግ ብዙ ድርሰቶችን የደረሱት መልአኩ ጽዋ ሕይወትን ካጠጣቸው በኋላ ነው፡፡ በመጀመሪያም አባ ጊዮርጊስ የተወለዱት በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት ነው፡፡ በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ የተመሠረቱ አብዛኞቹ ቅዱሳት ገዳማት በቅዱስ ዑራኤል መሪነት ነው፡፡ ድርሳኑ ላይ የማይጠቅሳቸው የሀገራችን የከበሩ ቅዱሳት ገዳማትና ቅዱሳን ነገሥታት የሉም፡፡
የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክን ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ስትሰደድ መንገድ እየመራ ወደ ግብጽ እና ወደ አገራችንን ኢትዮጵያ ያመጣቸው ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ እመቤታችንን ከተወደደ ልጇ ጋር በደመና ጭኖ መላ ኢትዮጵያን ካስጎበኛት በኋላ ቅድስት አገራችንን ለእመቤታችን የዓሥራት አገር እንድትሆን ያደረገው መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል በዓመት 3 ዓበይት በዓላት አሉት፡፡ ጥር 22 በዓለ ሲመቱ ነው፡፡ መጋቢት 27 የጌታችንን ክቡር የሆነ ወርቀ ደሙን ለዓለም የረጨበት ነው፡፡ ሐምሌ 22 ቀን ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበትና ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል የዕውቀትን ጽዋ ያጠጣበት ዕለት ነው፡፡
የሊቀ መላእክት የቅዱስ ዑራኤል ጥበቃው አይለየን! በጸሎቱ ይማረን !

ጥር 21-እረፍታ ለእግዚእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈሰ ቅዱስ ስም አሜን 
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 
ጥር 21-እረፍታ ለእግዚእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ


ከመጽሐፈ ተአምሯ፡- እመቤታችን ከዚህ ዓለም ታልፍ ዘንድ የጸለየችው ጸሎት ይህ ነው፡- ‹‹አቤቱ ቸር ጌታዬ ሆይ! ከዚህ ሑከትና ኀዘን ከመላበት ዓለም ደገኛውን መልአክህን ልከህ ወደኝ› ስትል በጸለየች ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተገለጸላት፡፡ እንዲህም እያለች ስትጸልይ ሰማይ ተከፈተ፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ወደ እመቤታችን ወርዶ ‹ጸጋን የተመላሽ ሆይ! ደስ ይበልሽ› በማለት የደስታ መልእክት ነገራት፡፡ ዳግመኛም ‹‹እነሆ ጸሎትሽ ከአንቺ ከተወለደው ከእግዚአብሔር ዘንድ ደረሰ፡፡ እንደፈቃድሽ ከዚህ በኃላፊው ዓለም ወደ ዘላለም ሕይወት ትሄጂ ዘንድ ልመናሽ ተሰምቶልሻል›› አላት፡፡ 
እመቤታችንም ይህንን ነገር ከመልአኩ በሰማች ጊዜ ወደ በዓቷ ተመለሰችና ከዚያ የሚያገለግሏትን ደናግል ሰብስባ ‹አይሁድ ሁልጊዜ የልጄን መቃብር ይጠብቃሉና ስለዚህ የእኔን ከዚያ መገኘት አንድ ቀን ይገለጽላቸውና ከዚያ መግባት ይከለክሉኛል ብዬ ፈራሁ፡፡ ስለዚህ ከዛሬ ጀምሮ ራሳችሁን ችላላችሁ በሰላም ትኖራላችሁ እኔ ወደ ቤተልሔም እሄዳለሁና› አለቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ሁሉም በአንድነት ቃላቸውን አስተባብረው ‹ከአንቺ ጋር እንሄዳለን፡፡ ስለ አንቺ እናት አባታችንን፣ እኅት ወንድሞቻችንን ያለንን ሁሉ ትተን ተከትለንሻልና እነሆ አሁንም አንቺ ከሄድሽበት እኛም አብረንሽ እንሄዳለን፣ ባለ ዘመናችን ሁሉ ከአንቺ አንለይም› አሏት፡፡ እመቤታችንም በዚያን ጊዜ ይዛቸው ወደ ቤተልሔም ሄደች፣ በዚያም ተቀመጠች፡፡ እንዲህም ያለቻቸው ስለ አይሁድ ፍራቻ ሳይሆን ከዚህ ከኃላፊው ዓለም በሞት የመለየቷ ጊዜ ስለመድረሱ ነበር፡፡ እናንት የፍቅሯን ፈለግ የተከተላችሁና በፍቅሯ ቀምበር የተጠመዳችሁ የወንጌል ልጆች ሆይ እንግዲህ እመቤታችን በቤተልሔም ተቀምጣ ሳለች መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከዚህ ዓለም በሞት የምትለይበትን ጊዜ በክብር እንደነገራት አስተውሉ፡፡ ልመናዋ ክብሯ ለዘለዓለሙ በዕውነት ይደርብን፡፡ 
እረፍታ ለእግዚእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ፡- በ50 ዓ.ም ገደማ በዕለተ እሑድ ጌታችን እልፍ አእላፍ መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ ‹‹እናቴ ሆይ! ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍሽ መጣሁ›› አላት፡፡ እመቤታችንም ‹‹ልጄ ሰማይና ምድር የማይወስኑህን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኔ ተሸክሜ፣ በድንግልና ወልጄህ እሞታለሁን?›› አለችው፡፡ ጌታችንም በሲኦል የሚሠቃዩ ነፍሳትን አሳያትና ‹‹እናቴ ሆይ! ሞትሽ ለእኒህ ቤዛ ይሆናቸዋል›› አላት፡፡ ለፍጥረታት ሁሉ እጅግ የምትራራ እመቤታችንም ‹‹እነዚህን ከማርክልኝስ ይሁን ልሙት›› አለችው፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ቅድስት ነፍስዋን ከክብርት ሥጋዋ ለይቶ በዝማሬ መላእክት አሳረጋት፡፡ ደቀመዛሙርቱንም ከያሉበት በደመና ጠቅሶ ካለችበት አድርሶ ‹‹እመቤታችሁን ቅበሩ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ይዘዋት ወደ ጌታ ሰማኔ ወሰዷት፡፡ 
አበው ‹‹እመቤታችን ሆይ! ሞትሽ ሠርግን ይመስላል›› እንዳሉት የእመቤታችን እረፍት እንባ መራጨት፣ ጠጉር መንጨት፣ ደረት መድቃት እንዳለበት የሰው ሞት አልነበረም፡፡ ይልቁንም አንደ ሠርግ ቤት ቅዱሳን መላእክት በውዳሴ፤ በማህሌት፣ በዝማሬ፣ በምስጋና ወደ ሰማይ ሸኟት እንጂ፡፡ ቅዱስ ያሬድም ‹‹እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ከፍ ከፍ አለች፤ በዚያም ከልጇ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች›› በማለት ዘምሯል፡፡ የእመቤታችን ሥጋዋ ከጌቴሴማኔ ወደ ገነት መፍለሱን አስቀድሞ አባቷ ቅዱስ ዳዊት በትንቢት ሲናገር ‹‹አቤቱ ወደ እረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት›› በማለት ተንብዮዋል፡፡ መዝ 131፡8፡፡ ይህም ‹‹ፈጣሪዬ ሆይ ምእመናንን ወደምታሳርፍበት ወደ መንግሥተ ሰማያት የመቅደስህን ታቦት ድንግል ማርያምን ይዘህ ተነሥ›› ሲል ነው፡፡ ይህም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም 64 ዓመት በዚህ ዓለም ከኖረች በኋላ ነብሷ ከሥጋዋ ተለይቶ እንደ ልጅዋ ትንሣኤ መነሣቷን የሚያመለክት ነው፡፡ ‹‹ታቦት›› ያላትም ማደሪያው ስለሆነች ነው፡፡
ጠቢቡ ሰሎሞን በምሳሌ ሲናገር «ወደጄ ሆይ ተነሺ፣ ውበቴ ሆይ ነይ፡፡ እነሆ ክረምት አለፈ፣ ዝናቡም አልፎ ሄደ፣ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፣ የዜማም ጊዜ ደረሰ፣ የቁርዬውም ቃል በምድራችን ተሰማ፡፡ በለሱ ጎመራ ወይኖችም አበቡ መዐዛቸውንም ሰጡ ወዳጄ ሆይ ተነሺ፤ ውበቴ ሆይ ነይ» አለ፡፡ መኃ 2፡10-14፡፡ ይህ ኃይለ ቃል ሲተረጎም በውስጡ ብዙ ምሥጢራዊ ነገሮችን ያያዘ ነው፡፡ «በክረምትና በዝናብ» የተመሰሉ የእመቤታችን መከራዎች ናቸው፡፡ የመከራሽ ጊዜ አልፏል ሲላት «አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ» ማለቱ ከልጅሽ እግር ሥር ቁጭ ብለው ተምረው ወንጌልን የተቀበሉ ሐዋርያት አንቺን በእናትነት የተረከቡ የሐዋርያት ድምፅ ወይም ስብከት በምድር ሁሉ መሰማቱን ያጠይቃል፡፡
ጠቢቡ ሰሎሞን «የዜማ ጊዜ ደረሰ» ያለው የመከሩን ወቅት ነው፡፡ መከር የፍሬ ጊዜ እንደመኖኑ ሐዋርያት የዘሩት ዘር ማለትም ስብከታቸው ፍሬ አፈራና ክርስቲያኖች በዙ፤ «በለሱ ጎመራ» በጎ ምግባር የሌላቸው ሰዎች በሐዋርያት ስብከት ተምረው ምግባር መሥራት ጀመሩ፤ «ወይኖች አብበዋል መዐዛቸውንም ሰጥተዋል» በመላው ዓለም ያሉ ምዕመናን በሃይማኖት ማበብ፣ መዐዛ ምግባራቸውን ማቅረብ መስጠት ጀመሩ በማለት ሊቃውንት አባቶች ምሥጢሩን ያብራሩታል፡፡ በዚህ ትርጓሜ ‹‹ወደጄ ሆይ! ተነሽ›› እያለ የሚናገረው ተወዳጁ ልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ድንግል ማርያምን በመለኮታዊ ስልጣኑ ከሙታን ለይቶ ማስነሣቱን ሲያስረዳን ነው፡፡ 
ስለዚህ ድንቅ ምስጢር ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት›› (መዝ 131፡8) ብሎ የተናገረው ትንቢት በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና የጸናች የእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ዕረፍትና ትንሳኤ እንዲሁም ፍልሰት (ዕርገት) ከማሳየቱም በተጨማሪ የአምላክ እናት በልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት በክብር መኖሯንም በግልጽ ያስረዳል ያስገነዝባል፡፡ ‹‹በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች›› (መዝ 44፡9) የሚለውን የቅዱስ ዳዊት ትንቢታዊ ቃል ሊቃውንት አባቶች በተለይም የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መተርጉማን ‹‹ንግሥተ ሰማይ ወምድር ድንግል ማርያም በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና›› ተሸልማና አጊጣ በሰማያዊው ዓለም በልጇ መንግሥት በክብር መኖሯን የሚያመለክት መሆኑን አስረግጠው አስረድተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ሰማያዊው አባታቸውን እግዚአብሔርን ‹‹አቡነ ዘበሰማያት፤ በሰማያት የምትኖር አባታችን›› እያሉ ዘወትር ሲያመሰግኑ፤ በአንጻሩ ደግሞ መንፈሳዊት እናታቸውን ድንግል ማርያምን ‹‹በሰላመ ቅዱስ ገብርኤል መልአክ ኦ እግዝእትየ ማርያም ሰላም ለኪ፤ እመቤቴ ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል ሰላምታ ሰላም እልሻለሁ›› እያሉ ዘወትር ያከብሯታል ያመሰግኗታልም፡፡ ሉቃ 1፡28፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ ዘወትር በምንጸልየው የእሑድ የእመቤታችን ውዳሴ ላይ ‹‹ምልዕተ ጸጋ፣ ምልዕተ ክብር፣ ምልዕተ ውዳሴ የሆንሽ ድንግል ሆይ ከቅዱሳን ሁሉ ይልቅ ትለምኝልኝ ዘንድ ለአንቺ ይገባል፡፡ አንቺ ከሊቃነ ጳጳሳት ትበልጫለሽ፤ ከቅዱሳን ነቢያት፣ ከቅዱሳን ሐዋርያት ከሰብዓ አርድእትም ትበልጫለሽ፡፡ ዳግመኛም ከሱራፌልና ከኪሩቤል ይልቅ የሚበልጥ የመወደድ የመፈራት ግርማ አለሽ፡፡ በእውነት የባሕርያችን መመኪያ አንቺ ነሽ፡፡ ለሰውነታችንም ሕይወትን፣ ድኅነትን የምትለምኚና የምታማልጅን አንቺ ነሽ›› በማለት የእመቤታችን ልዕልናዋን የጸጋዋን ፍጹምነትና የክብሯን ታላቅነት በአጽንኦት ገልጾ መስክሯል፡፡
እመቤታችን በጥር ሃያ አንድ ቀን በታላቅ ክብር ካረፈች በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት በፈቃደ እግዚአብሔር ከያሉበት መጥተው በኢየሩሳሌም ተሰብስበው የፈጣሪያችን እናት ድንግል ማርያምን በጸሎትና በማዕጠንት አክብረው ገንዘው ጥልቅ በሆነ ኃዘን ሊቀብሯት ወደ ጌቴሰማኒ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉምና «ቀድሞ ልጇ ሞቶ ተቀብሮ ሳለ ተነሣ እያሉ ሕዝቡን አስኮበለሉ አሁን ደግሞ እናቱን ሞታ ተነሣች እያሉ እንዳያውኩ ሥጋዋን እናቃጥል» በሚል የክፋት ምክር ተነሳሱ፡፡ በተለይም ደግሞ በእመቤታችን ላይ በክፋትና በተንኮል ከተነሳሱት ከእኒህ አይሁድ መካከል ታውፋንያ የተባለው አይሁዳዊ
አማናዊት ታቦተ እግዚአብሔር የሆነችው የድንግል ማርያም ቅዱስ ሥጋ ያረፈበትን አልጋ ለመያዝ እጁን በድፍረት ዘረጋ፡፡ በዚህን ጊዜ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን (2ኛ ሳሙ 6፡6፤ 1ኛ ዜና 13፡7-10) ላይ የአሚናዳብ ልጅ ዖዛ እጁን በታቦተ ጽዮን ላይ በድፍረት በመዘርጋቱ ምክንያት ተቆጥቶ እንደቀጣው ታውፋንያንም ሰማያዊው መልአክ ሰይፍ እጆቹን ቀጣው ቆረጠው፡፡ «እግዚአብሔር በቀባው ላይ እጁን የሚዘረጋ ንጹሕ አይሆንም (1ኛ ሳሙ 26፡9) እንደተባለ እጆቹም አልጋው ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ፡፡ 
ታውፋንያም ስለተቆረጡት እጆቹ ወደ እመቤታችን አምኖ ወደ እርሷ ቢጮህ ቢማጸናት፤ በቅዱስ ጴጥሮስ አማካይኝነት እጆቹን እንደ ቀድሞ ሆነው ድነውለታል፡፡ በጌታችን ትእዛዝ መልአኩ የእመቤታችንን ቅዱስ ሥጋ ከወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ጋር በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር በክብር አኑሮታል፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት ዮሐንስ ከተመለሰ በኋላ ‹‹እመቤታችን እንደምን አለች?›› አሉት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም «ከገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች» አላቸው፡፡ እነርሱም ዮሐንስ ዐይቶ እኛ ሳናይ ብለው በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፡፡ ጥር አርፋ በነሐሴ ወር ሁለት ሱባኤ ይዘው ሲጨርሱ በነሐሴ 14 መልአኩ ቅዱስ ሥጋዋን ከገነት አምጥቶ ሰጥቷቸው በጸሎትና በምሕላ ቀብረዋታል፡፡ በዚህ ጊዜ ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ ቶማስ አልነበረም፡፡ በሦስተኛው ቀን እንደ ልጇ ተነሥታ ስታርግ፣ ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ ያገኛታል፡፡ በዚህ ጊዜ ትንሣኤዋን ሌሎች ሐዋርያት አይተው፣ ለእርሱ የቀረበት መስሎት አዝኖ ‹‹በፊት የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ አሁን ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ ብሎ ከደመናው ለመውደቅ ተመኘ፡፡ በዚህ ጊዜ እመቤታችን ቶማስን አጽናናችው፡፡ ከእርሱ በቀር ትንሣኤዋን ሌላ እንዳላየ ነገራው ለምስክር እንዲሆነው ሰበኗን/መግነዝ ሰጥታው ዐረገች፡፡ 
ጌታችን ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር ቆይቶ ሙስና መቃብር ሳያገኘው መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል በሥልጣኑ እሑድ በመንፈቀ ሌሊት እንደተነሣ ሁሉ ክብርት እናቱ እመቤታችም በተቀበረች በሦስተኛው ቀን ማኅደረ መለኮት ናትና ሙስና መቃብር ሳያገኛት መግነዝ ፍቱልኝ፣ መቃብር ክፈቱልኝ ሳትል የልጇ ሥልጣን ኃይል ሆኗት መነሣቷን ትንሣኤዋ ‹‹እንደ ልጅዋ ትንሣኤ›› ነው ተብሎ ሲከበርላት ይኖራል፡፡ 
ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያት ወዳሉበት ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ እመቤታችንን እኮ ቀበርናት ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ምስጢሩን ደብቆ ‹‹ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር›› አላቸው፡፡ ሐዋርያትም ‹‹አንተ ተጠራጣሪ ነህ›› ብለው መቃብሩን ሊያሳዩት ሲከፍቱ አጧት፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹እመቤታችን ተነሥታ አርጋለች›› ብሎ ሁኔታውን ተረከላቸው፡፡ ‹‹ለምስክር ይሁንህ›› ብላ የሰጠቸውንም ሰበኗን አሳያቸው፡፡ ሐዋርያትም ይህን አይተው ትንሣኤዋን አመኑ። ሰበኗን ቆራርጠው ለበረከት ተከፋፍለው ወደየሃገረ ስብከታቸው ተመልሰዋል፡፡ ዛሬም በመጾር መስቀልና በካህናት እጅ መስቀላቸው ላይ የሚያስሯት ‹‹መሀረብ›› የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡ በዓመቱም ሐዋርያት ‹‹ቶማስ ትንሣኤሽን አይቶ እንዴት እኛ ይቅርብን!›› ብለው ከነሐሴ አንድ ጀምረው ሱባኤ ገቡ፡፡ በነሐሴ 16 ቀንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቅዱሳን ሐዋርያትን ወደ ሰማይ አሳርጎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቅዳሴ ቀድሶ አቁርቧቸዋል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም የመቤታችንን ትንሣኤና ዕርገቷን በዓይናቸው አይተውና በሚገባ ተረድተው ዓለምን ዙረው አስተምረዋል፡፡ 
+ + + 
ከመጽሐፈ ስንክሳር፡- እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ከመሞቷ በፊት በጌታችን በመድሃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መቃብሩ ቦታ ትጸልይ ነበር፡፡ መንፈስ ቅዱስም ለእመቤታችን ከዚህ ዓለም እንደምትለይ ነገራት፡፡ ጌታችንም በደብረ ዘይት ላሉ ደናግላን ነግሯቸዋልና ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በፍጥነት መጡ፡፡ እርሷም መንፈስ ቅዱስ የነገራትን ለእነርሱ ነገረቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ እመቤታችን እንዲህ ብላ ጸለየች፡- ‹‹ልጄ ወዳጄ፣ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ልመናየን ተቀብለህ ደቀ መዝሙርህን ዮሐንስን በዚህች ሰዓት አምጣው፤ እንዲሁም ሕያዋን የሆኑትን ሐዋርያትን ሁሉንም ነፍሶቻቸውን የለየሃቸውንም ሁሉ ወደ እኔ አምጣቸው፤ አንተ የሕያዋን አምላክ ነህና ለአንተም ምስጋና ይሁን አሜን›› አለች፡፡ 
በዚያን ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ትዕዛዝ ቅዱስ ዮሐንስን ደመና ተሸክማ ወደ እመቤታችን አደረሰችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በፊቷ ሰገደላትና እንዲህ አላት፡- ‹‹ሰላምታ ይገባሻል፣ ጌታችንን ፈጣሪያችንን መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን የወለድሽው ጸጋን የተመላሽ ሆይ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ ከዚህ ዓለም ተለይተሽ በክብር በምስጋና ወደ ዘለዓለም ሕይወት ትሄጃለሽና፡፡ ይህም ስሙ ክቡር ምስጉን የሆነ ጌታችንና ፈጣሪያችን ድንቅ ድንቅ ተአምራቶችን በአንቺ ላይ ከገለጠ በኋላ ነው›› አላት፡፡ እመቤታችንም ይህን በሰማች ጊዜ እጅግ ደስ አላት እግዚአብሔርንምእንዲህ ብላ አመሰገነችው፡- ‹‹ፈጣሪዬ ጌታዬ ላንተ ምስጋና ይሁን፣ የለመንኩህን ሰጥተኸኛልና፡፡ አሁንም ነብሴን ተቀብለው ወደ ሰማይ ወደ አንተ ሊይሳርጓት ከሚመጡ ቅዱሳን መላእክቶችህ ጋር በመምጣትህ የምለምንህን ሁሉ ስጠኝ›› አለችው፡፡ በዚያም ጊዜ ከሰማይ እንዲህ የሚል ቃል መጣ፡- ‹‹እነሆ አሁን መላእክት ይደርሳሉ፡፡ ሐዋርያትም ሁሉ ከምድር ዳርቻ በደመና ተጭነው ለሰማይና ለምድር ጌታ ለኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ወደሆነች ወደ ቅድስት ድንግል ይደርሳሉ፡፡ ወዲያውም ሁሉም ሐዋርያት የሞቱት ከመቃብራቸው ተነሥተው በሕይወት ያሉትም ሁሉም ወደ እመቤታችን ደርሰው ሰገዱላት፡፡ ‹‹አምላካችን ከአንቺ የተወለደ ጸጋን የተመላሽ ሆይ! ደስ ይበልሽ፣ እርሱ ከዚህ ዓለም ለይቶ ቃል ኪዳን እንደሰጠሽ በክብር በምስጋና ከእርሱ ጋር ያሳርግሻልና›› አሏት፡፡ 
በዚያንም ጊዜ እመቤታችን በዐልጋዋ ላይ ተቀመጠችና ሐዋርያትን እንዲህ አለቻቸው፡- ፈጣሪዬ ፈጣሪያችሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እንደሚመጣ እናንተንም እንዳየኋችሁ እንደማየው አሁን ዐወቅሁ፡፡ ከዚህ ከሥጋዬ ወጥቼ ወደ ዘለዓለም ሕይወት እሄዳለሁ፡፡ ነገር ግን ትነግሩኝ ዘንድ እሻለሁ፣ እኔ ከዚህ ዓለም እንደምለይ ከወዴት ዐወቃችሁ?›› ብላ የጠቀቻቸው፡፡ በመጀመሪያ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚያም ሁሉም ሐዋርያት ‹‹ወደ አንቺ እንመጣ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ አዘዘን፣ በደመና ላይም በተጫን ጊዜ እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥነን ደረስን›› አሏት፡፡ 
እመቤታችንም ይህን ነገር ከሐዋርያት በሰማች ጊዜ ድምጿን ከፍ አድርጋ እንዲህ አለች፡- ‹‹ጌታዬና ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ክቡር ምስጉን የሆነ ስምህን ፈጽሜ አመሰግናለሁ፣ የእኔን የአገልጋይህን መከራ ተመልክተህ ድንቅ ኃይልን አድርገህልኛልና ከእንግዲህ ወዲያ ትውልድ ሁሉ ያከብሩኛል ያመሰግኑኛል›› አለች፡፡ ጸሎቷንም ስትጨርስ ሐዋርያትን ‹‹ዕጣን አምጥታችሁ በማጠን የጌታዬን የኢየሱስ ክርስቶስን ስሙን ጥሩት›› አለቻቸው፡፡ እነሱም እንዳዘዘቻቸው አደረጉ፡፡ በዚያም ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን እልፍ አእላፍ ቅዱሳን መላእክቱ አጅበው እያመሰገኑት መጣና እመቤታችንን አረጋጋት፡፡ ያዘጋጀላትንም ተድላ ደስታ ነገራት፡፡ በዚያም ጊዜ ድንቆቸ የሆኑ ተአምራት ተደረጉ፡፡ ዓይነ ሥውራን ማየት ቻሉ፣ ደንቆሮች መስማት ቻሉ፣ ዲዳዎች ተናገሩ፣ ለምጻሞች ነጹ፣ ሐንካሶች መሄድ ቻሉ፣ ደዌ ያለበትም ሁሉ ዳነ፡፡ የብርሃን እናቱ ወላዲተ አምላክ እመቤታችን ወደ አለችበት ቤት በቀረቡ ጊዜ ከደዌአቸው ሁሉ ይፈወሳሉና፡፡ 
ከዚህም በኋላ እመቤታችን ተወዳጅ ልጇን ‹‹በአየር ውስጥ ተበትነው ከሚኖሩ ከሚያስነግጡ ግሩማን መላእክት የተነሣ ከእሳት ባሕርም የተነሣ እፈራለሁ›› ባለችው ጊዜ እርሱም ‹‹እናቴ ሆይ ከእነርሱ ለማንም በአንቺ ላይ ሥልጣን የለውም›› አላት፡፡ ከሥጋዋም የምትለይበት ጊዜ ሲደርስ ሐዋርያትንና ደናግል ትባርካቸው ዘንድ እያለቀሱ ለመኗት፡፡ እመቤታችንም እጇን በላያቸው ዘርግታ ባረከቻቸው፡፡ በዚህን ጊዜ ጌታችን ቅድስት ንጽሕት ነፍሷን ከሥጋዋ ለይቶ በመለኮታዊ እጆቹ ይዞ በብርሃን ልብስ አጎናጽፎ ወደ ከፍተኛ መኖሪያ ከእርሱ ጋር አሳረጋት። ሥጋዋን ግን እንደሚገባ ገንዘው፤ ወደ ጌቴ ሰማኒ ተሸክመው እንዲወስዷ ሐዋርያትን አዘዛቸው፡፡ ነፍሷ ከሥጋዋ ከመውጣቷ በፊት በሰው አንደበት ይህ ነው ተብሎ የማይነገር ብርሃን እያየች ነበር፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችንም ‹‹እንግዲህ ሥጋሽን ተድላ ደስታ ወዳለበት ገነት አፈልሳለሁ፡፡ ዳግመኛም ሥጋሽን ከነፍሽ ጋር አዋሕጄ አስነሥቼ መላእክት በፊትሽ ሆነው በሚያመሰግኑበት አምሳያ በሌለው ተድላ ደስታ ባለበት መኖሪያ አኖርሻለሁ›› አላት፡፡ 
እመቤታችንም እንዲህ አለች፡- ‹‹አቤቱ በረቀቀ ጥበብህ ይህን ሁሉ የሠራህ አመሰግንሃለሁ፤ ሁለተኛም ልመናየን ትሰማ ዘንድ እለምንሃለሁ፤ በስሜ ወደ አንተ የሚለምነውን ሁሉ፤ ልመናውን ተቀበለው በመከራም ውስጥ ሁኖ ስሜን ጠርቶ ወደ አንተ የሚለምነውን ከመከራም ሁሉ አድነው፤ በሰማይም በምድርም በሥራው ላይ ሁሉ አንተ ከሃሊ ነህና መታሰቢያየን በውስጧ የሚያደርጉባትን ቦታ ሁሉ ባርክ፣ በእኔ ስም የሚያቀርቡትን የሁሉንም መሥዋዕታቸውን ተቀበል›› አለችው፡፡ ጌታችንም እንዲህ ብሎ መለሰላት፡- ‹‹የለመንሽኝን ሁሉ አደርግልሻለሁ፤ ደስ ይበልሽ፣ ከእኔ ከአባቴ ከመንፈስ ቅዱስ ዘንድ ጸጋ ክብር ባለሟልነት ተሰጥቶሻልና ስምሽንም ጠርቶ የሚለምን ሁሉ በዚህ ዓለምም በወዲያኛው ዓለምም ከቶ አይጠፋም›› አላት፡፡ እመቤታችንም በታላቅ ክብር ካረፈች በኋላ ጌታችን እንዳዘዘ ወደ ጌቴ ሰማኒ ሊወስዷት ሐዋርይት ገንዘው ተሸከሟት፡፡ አይሁድም በሰሙ ጊዜ ሥጋዋን ሊይቃጥሉ ወጡ፡፡ ከእርሳቸውም አንዱ ከምድር ይጥላት ዘንድ የእመቤታችንን አልጋዋን ያዘ፡፡ ያን ጊዜም ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘ መልአክ እጆቹን በእሳት ሰይፍ ቀጣውና እጆቹ በአልጋው ላይ ጠንጠለጠሉ፡፡ ያን ጊዜ በጌታችን አምኖ ወደ እመቤታችን እያለቀሰ እንዲህ ብሎ ለመነ፡- ‹‹የእውነተኛ አምላክ የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እናት ሆይ! አንቺ በእውነት ድንግል ይሆንሽ በእኔ ላይ ይቅርታ ታደርጊ ዘንድ አለምንሻለሁ፡፡›› በሐዋርይትም ልመና እጆቹ ተመልሰው እንደቀድሞው ደኅነኞች ሆኑ፡፡ 
ሐዋርያትም እመቤታችንን በቀብሯት ጊዜ ከዚያ ሶስት ቀን ኖሩ፣ ዕረፍቷም የሆነው እሑድ ቀን ጥር ወር በ21 ቀን ነበረ፡፡ ጌታችንም ብርሃናውያን መላእክትን ላከ፣ እነርሱም ሥጋዋን ከመቃብር ወስደው በገነት ውስጥ በዕፀ ሕይወት ሥር አኖሯት፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ግን ያን ጊዜ አልነበረም በደመና ላይ ተጭኖ እርሱ ሲመጣ መላእክት ሲያሳርጓት እመቤታችንን አገኟት፡፡ ቅዱሳን መላእክትም ‹‹ለአምላክ እናት ለእመቤታችን ድንግል ማርይም ና እጅ ንሣ›› አሉት፡፡ እርሱም ሰገደላትና ተሳለማት ከእርሷም ተባረከ፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሐዋርያት ደረሰ፡፡ እነርሱም እመቤታችንን ማርያምን እንዳረፈችና እንደ ቀበሯት ነገሩት፡፡ ቶማስም ‹‹ሥጋዋን እስከማይ አላምንም›› አላቸው፡፡ ሥጋውንም ያሳዩት ዘንድ ወደ መቃብሯት ባደረሱት ጊዜ በመቃብሩ ውስጥ ሥጋዋን አላገኙም፤ እነርሱም ደንግጠው እያደነቁ ሳለ ያን ጊዜ ቶማስ ከመላእክት ጋር ወደ ሰማይ ስታርግ እመቤታችን እንዳገኛት ነገራቸው፡፡ ሐዋርያትም ይህን በሰሙ ጊዜ የእመቤታችንን ዕርገቷን ስላላዩ እጅግ አዘኑ፡፡ ሥጋዋን በምድር ውስጥ ይተው ዘንድ እንዳልወደደ መንፈስ ቅዱስ አስገነዘባቸው፡፡ ከዚህም በኋላ አንድ ጊዜ ደግሞ እርሷን ያሳያቸው ዘንድ እንዳለው ጌታችን ቃል ኪዳን በማድረግ ተስፋ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም በተስፋ እስከ ነሐሴ 16 በተስፋ ኖሩ፡፡
አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችን ፍቅሯን ጣዕሟን ታሳድርብን!
+ + + 
ዳግመኛም በዚህች ዕለት ጥር 21 
+ እመቤታችን ተገልጣለት ‹‹ዕረፍትህ በዕረፍቴ ቀን ነውና ተዘጋጅ›› ብላ የነገረችው የኑሲሱ አቡነ ጎርጎሪዮስ ዕረፍቱ ነው፡፡ 
+ አርሲ ፈንታሌ ተራራ ላይ ሠሪቲ ለምትባል ጠንቋይ እየተላላኩ ሕዝቡን የሚያስቱና የሚያሰቃዩ አራት መቶ ሰባ ሺህ ሦስት መቶ አጋንንትን በጸሎታቸው እሳት ከሰማይ አውርደው ያቃጠሏቸው የመሐግሉ አቡነ ቀውስጦስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+ የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ ታላቅ ወንድም የሆኑት ዋሸራን ገዳምን የመሠረቱት በሱባኤ ስለ ዋሸራ ሕዝብ ታላቅ ምሥጢር የተነገራቸው አቡነ ተስፋ ኢየሱስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+ በሐይቅ ሲያጥኑ የማዕጠንታቸው ሽታ እስከ ጣና ቂርቆስ ድረስ ይሸት ስለነበር ቅዱሳን ሲሸታቸው አባ ኤልያስ ዛሬ ቅዳሴ ገባ ይሏቸው የነበሩትና በሞት ማረፋቸውን የሚያጥንባት ጽንሐቸው አፍ አውጥታ የተናገረችላቸው የመርጦው አቡነ ኤልያስም ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ የሮሜው አገር ንጉሥ ልጅ የሆነችው ቅድስት ኢላርያ ዕረፍቷ ነው፡፡ 
+ የደብረ ጽላልሽዋ ቅድስት ማርያም ክብራም ዕረፍቷ ነው፡፡ 
+ ነቢዩ ኤርምያስ መታሰቢያ በዓሉ ነው፡፡ 
+ በሰማዕትነት ያረፈ በዋሻ የሚኖር ቅዱስ ኒቆላዎስ መታሰቢያ በዓሉ መሆኑን ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል፡፡ 
+ በመናፍቁ ንጉሥ በመርቅያን ዘመን መኮንኑ ጳውሎስና ቀሲስ ሲላስ ምስክር ሆነው በዚህች ዕለት ዐርፈዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን የዕረፍቷ በዓል ዕለት በጌቴሴማኒ ከምእመናን ጋር ሆነው ተሰብስበው ሳሉ ከሃዲው መኮንን መጥቶ በዚያ ካሉት አንድም ሰው ሳያስቀር የገደላቸው መሆኑን ስንክሳሩ በአጭሩ ይጠቅሳቸዋል፡፡ 
አቡነ ተስፋ ኢየሱስ ዘጎጃም፡- የትውልድ ሀገራቸው ጎጃም ሲሆን የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ ዘግሽ ዓባይ ታላቅ ወንድም ናቸው፡፡ እንደ ወንድማቸው የተወለዱት በመልአክ ብስራት ነው፡፡ አቡነ ተስፋ ኢየሱስን መልአክ እየመራ ወስዶ ጣና ሐይቅ ገዳም አደረሳቸውና በዚያ የቤተ ክርስቲያን ትምህርትና ሥርዓቷን ሁሉ በሚገባ ተማሩ፡፡ የዋሸራን ገዳም በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው ከመሠረቱት 300 ቅዱሳን መነኮሳት ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡ በ300ው መነኮሳትም ተመርጠው የገዳሟ ባራኪ ሆነው ተሹመው አገልግለዋል፡፡ ሱባኤ ገብተው ስለ ዋሸራ ገዳምና ስለ አካባቢው ሕዝብ ምሥጢር የተገለጠላቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ገዳሟ ፈለፈ ሊቃውንት እንደምትሆን ተገልጦላቸዋል፡፡ ደግመው ሱባኤ ቢገቡ ገዳሟ በስተኋላ እንደምትቀዘቅዝ ተገለጠላቸው፡፡ ለ3ኛም ጊዜ ሱባኤ ቢገቡ ገዳሟ እስከ ዕለተ ምዕዓት ጸንታ እንደምትኖር ተገልጦላቸው በዚህም ደስ ተሰኝተዋል፡፡ ዋሸራ ገዳም በመጀመሪያ በባሐር የተከበበች ብትሆንም አቡነ ተስፋ ኢየሱስ ባሕሩን ቢባርኩት ተስተካክሎ እንደ ጸበል ሆኖላቸዋል፡፡ እመቤታችንም ዕለት ዕለት እየተገለጠችላቸው ትባርካቸው ነበር፡፡ ጻድቁ በተጋድሎ ብዙ ካገለገሉና ከጌታችን ታላቅ ቃል ኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ጥር 21 ቀን ዐርፈው በዚያው ተቀብረዋል፡፡ 
ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን፡፡ 
+ + + 
አቡነ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ፡- ይኸውም የቅዱስ ባስልዮስ ወንድም ነው፡፡ ሀገሩ ቂሳርያ ሲሆን የተሾመው ኑሲስ በተባለች ደሴት ላይ ነው፡፡ መናፍቁ ሰባልዮስ ‹‹አንድ ገጽ›› በማለቱ ሌሎቹ መናፍቃንም መቅዶንዮስና አቡሊናርዮስ ‹‹መንፈስ ቅዱስ ህጹፅ›› እና ‹ወልድ ሥጋ እንጂ ነፍስ አልነሳም› በማለታቸው በ381 ዓ.ም 150ው ሊቃውንት በቍስጥንጥንያ ተሰብስበው መናፍቃኑን ተከራክረው እረተው ሃይማኖትን ሲያጸኑ ከጢሞቲዎስ ጋር አንድ ላይ የጉባኤው አፈ ጉባዔ የነበረው ሊቁ ጎርጎሪዮስ ዘኑሲስ ነበር፡፡ እርሱም በጉባኤው ላይ እነ መቅዶንዮስንና አቡሊናርዮስን ተከራክሮ በመርታት መልስ አሳጥቷቸዋል፡፡ ሃይማኖትንም አጽንቷል፡፡ 
ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ቅዳሴ ሲቀድስ ጌታችን በርግብ አምሳል ሲወርድ ያየው ስለነበር ዘወትር እያለቀሰ ይቀድሳል፡፡ ከተጋድሎውም ጽናት የተነሣ ታማሚ ሆኖ ነበር፡፡ በኤጲስ ቆጶስነት ተሹሞ 33 ዓመት ኖሯል፡፡ ከተጋድሎውም ብዛት ድካም አጋጥሞት ነበርና አንድ ቀን ወንድሙ ባስልዮስ ሊጠይቀው መጣ፡፡ ቅዱስ ጎርጎርዮስም እንደልማዱ ሊቀድስ ወደ መሠዊያው በወጣ ጊዜ እመቤታችን ተገለጠችለትና ‹‹ዕረፍትህ በዕረፍቴ ቀን ነውና ዛሬ ወደእኔ ትመጣለህ›› አለችው፡፡ ጎርጎርዮስም የቁርባኑን ቅዳሴ ሲጨርስ ሕዝቡን በቀናች ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ ለመምከር ተነሣ ነገር ግን ከድካምና ሕመም ብዛት ሰውነቱ መቆም ስላልቻለ ወንደሙን ባስልዮስን ‹‹ዛሬ አንተ አስተምራቸው›› አለው፡፡ ወዲያውም እንደሚያንቀላፋ ሆነና ዐረፍ አለ፡፡ በቀሰቀሱትም ጊዜ በሞት ዐርፎ አገኙት፡፡ ይኸውን ጥር 21 ቀን ነው፡፡ በስሙ የተጠራ አንድ ቅዳሴና ገድለ ዜና አለው፡፡ በትንቢት ተናጋሪነቱ፣ በደራሲነቱና በመምህርነቱ መጽሐፍ ‹‹ጎርጎሪዮስ ዐቃቤ ሥራይ ቁስለ መድኃኒት ዘነፍስ›› ይለዋል፡፡ ከሃዲው ንጉሥ ዑልያኖስ ወንድማማቾቹን ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን በጸሎታቸው ሰዓት ደርሶባቸው እነርሱን ገድሎ መሥዋዕታቸውን ሊበላባቸው ሲመጣባቸው የቅዱስ መርቆሬዎስን ሥዕል በጸሎት ቢማጸኑ ሥዕሉ በገዘፈ ሥጋ ሆኖ በተአምራት ዑልያኖስን በጦር ወግቶ ገድሎላቸዋል፡፡
የቅዱስ ጎርጎሪዎስ ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን፡፡ 
+ + + 
አቡነ ኤልያስ ዘመርጦ፡- ትውልድ ሀገራቸው ጎጃም መርጡ ለማርያም ነው፡፡ አባታቸው መሠረተ ጽዮን መርጡ ለማርያምን በሹመት ብዙ ዘመን አገልግለዋል፡፡ አቡነ ኤልያስ 7 ዓመት ሲሆናቸው ለታላቁ ጻድቅ መቋሚያቸው እንደ ሰው አፍ አውጥታ ለምትናገረው ለአቡነ ተክል አልፋ ሰጧቸው፡፡ አቡነ ተክል አልፋም ብሉያቱን፣ ሐዲሳቱን፣ ቀኖናውንና ዶግማውን ሁሉ በሥርዓት ካስተማሯቸው በኋላ አመንኩሰዋቸዋል፡፡ ጻድቁ ወደ ሐይቅ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ሄደው 14 ዓመት በገዳሙ አገልግለዋል፡፡ 
አቡነ ኤልያስ በሚያጥኑበት ጊዜ የዕጣኑ ሽታ እስከ ጣና ቂርቆስ ድረስ ይሸት ነበርና ቅዱሳን ሲሸታቸው ‹‹ዛሬ አባ ኤልያስ ቅዳሴ ገባ›› ይላሉ፡፡ ጻድቁ ባረፉ ጊዜ በሞት መለየታቸውን ለመነኮሳቱ የተናገረችው ያጥኑባት የነበረችው ጽንሐ ናት፡፡ እንደ ሰው አፍ አውጥታ ‹‹አባታችን ዐረፉ›› ብላ ተናግራለች፡፡ መነኮሳቱም ወስደው በተድባበ ማርያም ቀብረዋቸዋል፡፡ በስማቸው የተቀረጹ ታቦታት በተደባበ ማርያም፣ በቸር ተከል ማርያምና በየህላ ቅዱስ ሚካኤል እንደሚገኝ ሊቀ ብርሃናት መርቆሬዎስ አረጋ ጽፈዋል፡፡
የአቡነ ኤልያስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን፡፡
+ + + 
ቅድስት ማርያም ክብራ ዘጽላልሽ፡- ትውልዷ ሸዋ ደብረ ጽላልሽ ሲሆን በወቅቱ የትልቅ ባለስልጣን የመስፍን ልጅ ነበረች፡፡ ወደ ደብረ በግዕ ገዳም ገብታ መነኮሳቱን በብዙ ድካም ስታገለግል ከኖረች በኋላ በአቡነ ሕፃን ሞዐ እጅ መንኩሳለች፡፡ 
አቡነ ሕፃን ሞዐ ማለት የደብረ በግዕህ ገዳምን የመሠረቱት ታላቅ አባት ሲሆኑ እንደበሬ በመታረስ ሰማዕትነት የተቀበሉ ናቸው፡፡ ጻድቁን ከአንድ በሬ ጋር ጠምደው ቀኑን ሙሉ ሲያርሷቸው በድካም ሆነው በኋይል የተነፈሱበት ቦታ ላይ ምድሪቱ ዛሬም ድረስ እንደእርሳቸው ስትተነፍስ የእስትንፋሷ ድምጹና ሙቀቱ ይሰማል፡፡ ለአስም ሕመም መድኃኒት ነው፡፡ ቦታውም ከደብረ ብርሃን በእግር የሁለት ሰዓት ተኩል መንገድ ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን የጻድቁ ቤተ ክርስቲያኑ ከወይንዬ ተክለ ሃይማኖት ገዳም አጠገብ ይገኛል፡፡ 
ቅድስት ማርያም ክብራ በጻድቁ ሕፃን ሞዐ እጅ ከመነኮሰች በኋላ ወደ አቡነ ዜና ማርቆስ ገዳም ገብታ በታላቅ ተጋድሎ ስትኖር ሰይጣን ብዙ ጊዜ በሰው አምሳል እየተገለጠ በፈተና ሊጥላት ይሞክር ነበር፡፡ የእግዚአብሔርም መልአክ እየተገለጠ ያበረታት ነበር፡፡ እርሷም በበትረ መስቀሏ ሰይጣንን እያሳደደች ታባርረው ነበር፡፡ ረድኤት በረከቷ ይደርብን በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + 
ቅድስት ኢላርያ፡- ይኽችም ቅድስት የሮሜው አገር ንጉሥ የዘይኑን ልጅ ናት፡፡ እርሱም እግዚአብሔርን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ነው፡፡ ልጁ ቅድስት ኢላርያንም ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እያስተማረ አሳደጋት፡፡ ከሁለት ሴቶቹ ለጆቹ በቀር ወንድ ልጅ የለውም ነበር፡፡ 
ቅድስት ኢላርያም ዕድሜዋ ከፍ ሲል ዓለምን ፍጹም ንቃለችና የምንኩስናን ልብስ የመላእክትንም አስኬማ ትለብስ ዘንድ ወደደች፡፡ ከቤተ መንግሥትም ተደብቃ ወጥታ የወንድ ልብስ በመልበስ ወደ ግብጽ አገር ሄደች፡፡ ወደ አስቄጥስ ገዳምም ገብታ ስሙ አባ ባውሚን የሚባል ፍጹም ሽማግሌ ጻድቅ ሰውን አግኝታ የምንኩስና ሀሳቧን ነገረችው፡፡ እርሷም ሴት እንደሆነች ስትነግረው ምሥጢሯን ጠብቆ ለብቻዋ ከዋሻ ውስጥ አስገባት፡፡ እየጎበኛትም ልትሠራው የሚገባትን ሁሉ ያስተምራት ነበር፡፡ እንዲህም ሆና በዚያ ዋሻ ውስጥ 12 ዓመት ኖረች፡፡ ቅድስት ኢላርያ ፂም ስለሌላት ለአረጋውያን መነኮሳት ጃንደረባ ትመስላቸው ነበር፡፡ በወንድ ስም አጠራርም አባ ኢላርዮን ብለው ይጠሯት ነበር፡፡ 
ከአባቷ ዘንድ ያለችው ታናሽ እኅቷ ርኩስ መንፈስ አደረባትና ብዙ አሠቃያት፡፡ ያድኗትም ዘንድ አባቷ ብዙ በመድከም ገንዘቡን አወጣ ነገር ግን ልትድን አልቻለችም፡፡ መኳንንቶቹም ወደ ግብጽ አስጥስ ገዳም እንዲልካት ለንጉሡ ነገሩት-በዚያ ያሉ መነኮሳት ክብራቸውና ጸጋቸው በሮም አገሮች ሁሉ ታውቋልና፡፡ ንጉሡም የታመመችውን ልጁን ከብዙ ሠራዊት ጋር ወደ ግብጽ ላካት፡፡ ለመነኮሳቱም ‹‹… ሁለት ሴቶች ልጆችን ወለድኩ ነገር ግን አንደኛዋ ጥላኝ ጠፋች፣ ሁለተኛዋንም ርኩስ መንፈስ ይዞ መጨወቻ አደረገብኝ፡፡ ቅዱሳን አባቶቼ ሆይ ልጄን በጸሎታቸሁ ትፈውሱልኝ ዘንድ ቅድስናችሁን እለምናለሁ›› የምትል ደብዳቤ ጽፎ ላከላቸው፡፡ መነኮሳቱም የንጉሡን ደብዳቤ ካነበቡ በኋላ በልጅቱ ላይ ጸለዩ፡፡ ነገር ግን ያደረባት ርኩስ መንፈስ ሊለቃት አልቻለም፡፡ ከዚህም በኋላ አረጋውያኑ መነኮሳት ጃንደረባ የሚሏትን ኢላርያን ጠርተው ‹‹እግዚአብሔር እስካዳናት ድረስ የንጉሡን ልጅ ወስደህ በላይዋ ላይ ጸልይ›› ብለው ሰጧት፡፡ እርሷም ‹‹ይህ ለእናንተ እንጂ ለእኔ አይቻለኝም›› ብትላቸውም ግድ አሏት፡፡ 
ከዚህም በኋላ ቅድስት ኢላርያ የታመመችውን ልጅ ወደ በዓቷ ወስዳ ጸሎት አደረገችላት፡፡ ሰይጣኑም ወዲያው ጥሏት ሸሸ፡፡ በጥቂት ቀንም ውስጥ ፈጽማ ዳነች፡፡ ቅድስት ኢላርያም እኅቷ እንደሆነች ታውቃለችና አቅፋ ትስማት ነበር ስለ ፍቅሯና ናፍቆቷም ወደ ውጭ እየወጣች ታለቅስ ነበር ነገር ግን ታማ የነበረችው እኅቷ አላወቀቻትም፡፡ ቅድስት ኢላርያም በጸሎቷ ከፈወሰቻ በኋላ ወደ አረጋውያኑ መነኮሳት ወስዳ ‹‹እነሆ በጸሎታች እግዚአብሔር ፈውሷታልና ወደ ንጉሡ አባቷ መልሷት›› ብላ ሰጠቻቸው፡፡ እነርሱም እጅግ ደስ ብሏቸው ወደ አባቷ መለሷት፡፡ ሮሜ አገር በደረሰችም ጊዜ ልጃቸው ስለዳነችላቸው ንጉሡና መኳንንቱ የአገሩም ሰዎች ሁሉ ተደስተው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ከዚህም በኋላ አባቷ በገዳም ስለነበራት ቆይታ ልጁን ጠየቃት፡፡ እርሷም ‹‹ያ በጸሎቱ ያዳነኝ አባ ኢላርዮን የሚባል መነኩሴ አብዝቶ ይወደኛል፤ አቅፎም ይስመኛል›› አለችው፡፡ ንጉሡም ይህንን ሲሰማ ልቡ ታወከና ‹‹መነኩሴ እንዴት ሴትን ለመሳም ይገባዋል/›› አለ፡፡ በዚህም ጊዜ ‹‹በእኔ ላይ ይጸልይ ዘንድ አገሬንም ይባርክ ዘንድ ልጄን ያዳናትን አባ ኢላርዮንን ወደኔ ላኩልኝ›› ብሎ ደብዳቤ ጽፎ ወደ አስቄጥስ ገዳም ላከ፡፡ 
አረጋውያኑም ቅድስት ኢላርያ ጠርተው ወደ ንጉሡ አገር ሄዳ እንድትባርከው አዘዟት፡፡ እርሷም ይተዋት ዘንድ እያለቀሰች ብትለምናቸውም እነርሱ ግን ‹‹ይህ ንጉሥ ክርስቲያኖችን የሚወድ ጻድቅ ነው፣ ቅዱሳት መጻሕፍትም እንደሚያዙን ትእዛዙን መተላለፍ የለብንም›› ብለው አስገድደው ላኳት፡፡ 
ወደ ንጉሡም በደረሰች ጊዜ ሁሉም በክብር ተቀብለው ተሳለሟት፡፡ ንጉሡና ንግሥቲቱም ለብቻቸው ሆነው ወደ ውስጠኛ ክፍል አስገቧትና ንጉሡ እንዲህ ብሎ ጠየቃት፡- ‹‹ልጄን ትስማት እንደነበር በሰማሁ ጊዜ በሀሳቤ ታውኬያለሁ፤ መነኩሴ ሴትን መሳም አይገባውምና ይህን ነገር ትገልጥልኝ ዘንድ እወዳለሁ›› አላት፡፡ የከበረች ቅድስት ኢላርያም በነገርኳችሁ ጊዜ ወደ አስጥስ ገዳም መሄድን ላትከለክሉኝ የከበረ ወንጌልን አምጥታችሁ ማሉልኝ›› አለቻቸው፡፡ እነርሱም ማሉላት፡፡ በዚህም ጊዜ እርሷ ማለት ልጃቸው ኢላርያ መሆኗን ነገረቻቸው፡፡ እንዴት ከቤተ መንግሥት እንደወጣችም አስረዳቻቸውና በአካሏ ላይ ያለውን ምልክት አሳየቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ በቤተ መንግሥቱ ታላቅ ጩኸት ሆነ፡፡ አቅፈውም እየሳሟት አለቀሱ፡፡ ‹‹ከእኛ ዘንድ እንድትሄጂ ከቶ አንተውሽም›› አሏት፡፡ እርሷም ‹‹በከበረ ወንጌል የማላቸሁትን መሐላ አስቡ›› አለቻቸው፡፡ እሺ ብለው ግን እስከ 40 ቀን አብራቸው እንድትቆይ ለመኗት 40 ቀን አብራቸው ቆየች፡፡
ቅድስት ኢላርያም ወደ አስቄጥስ ገዳም ከተመለሰች በኋላ ንጉሡ ዘይኑን ለገዳሙ መነኮሳት ለፍላጎታቸው ይሆን ዘንድ የግብጽን ምድር ግብር እንዲሰጧቸው አዘዘ፡፡ በዚያም ወራት በአባ መቃርስ ገዳም 400 የመነኮሳት ቤቶች ተሠሩ፡፡ በአባ ዮሐንስ ገዳም 700 በአባ ሙሴ ገዳም 300 ቤቶቸ ተሠሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ቅድስት ኢላርያ 5 ዓመት ኖራ በሰላም ዐረፈች፡፡ ከዕረፍቷም አስቀድሞ እርሷ ሴት እንደሆነች ያወቀ የለም፡፡ 
የቅድስት ኢላርያ ረድኤት በረከቷ ይደርብን በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + 
አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል፡- ቅዱሳን አባቶቻችን እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖትና እነ አቡነ ዜና ማርቆስ ሌሎቹም እነ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ ሕፃን ሞዐ፣ አቡነ አኖሪዮስ(ትልቁ)፣ አቡነ ገላውዲዮስ፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋርና አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል በሥጋም ዘመዳሞች ናቸው፡፡ ይኸውም የመሐግሉ አቡነ ቀውስጦስ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የቅርብ ዘመድ ናቸው፡፡ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት እናት እግዚእ ኀረያና የአቡነ ቀውስጦስ እናት እብነ ጽዮን ታላቅና ታናሸ ናችው፡፡ በአባትም በኩል ወረደ ምሕረት ዘካርያስን ወለደ፡፡ ዘካርያስም የእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አባት የሆኑ 6 ወንድማማች ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም እንድርያስ፣ አርከሌድስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብ፣ ቀሲስ ዮሐንስና ቀሲስ ዮናስ ናቸው፡፡ እንድርያስም ሳሙኤል ዘወገግን ወለደ፤ አርከሌድስም ሕፃን ሞዐን ወለደ፤ ዘርዐ አብርሃምም ታላቁን አኖርዮስን ወለደ፤ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብም ተክለ ሃይማኖትን ወለደ፤ ቀሲስ ዮሐንስም ዜና ማርቆስን ወለደ፣ ቀሲስ ዮናስ ደግሞ የፈጠጋሩን ማትያስንና ገላውዲዮስን ወለዳቸው፡፡ ገላውዲዮስም የመሐግሉ ቀውስጦስን ወለደ፡፡
አቡነ ቀውስጦስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከሾሙአቸው ከ12ቱ ንብረ ዕድ ወስጥ አንዱ ሲሆኑ ደብረ ሊባኖስንም የሚያጥኑበትም ወር በመጋቢት ወር ነበር። ሕዝቡ አጥብቆ የሚወዳቸውና የሚያከበራቸው አባት ናቸው፡፡
ግብፃዊው አቡነ ያዕቆብ ከግብፅ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የደብረ ሊባኖሱን እጨጌ አቡነ ፊልጶስን አስጠርተው፤ ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት “ኢትዮጵያ በአንድ ጳጳስ መወሰን የለባትም፡፡ ስለዚህ ዐሥራ ሁለት አበው መርጠን ክርስትና ይስፋፋ” ብለው ባቀረቡት ሐሳብ መሠረት፤ አቡነ ፊልጶስ ዘደብረ ሊባኖስ /ኤጲስ ቆጶስ/፣ አቡነ አኖሬዎስ ዘሞረት፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋር፣ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ አኖሬዎስ ዘወረብ፣ አቡነ ታዴዎስ ዘጽላልሽ፣ አቡነ ገብረ ክርስቶስ ዘግድም፣ አቡነ መርቆሬዎስ ዘመርሐ ቤቴ፣ አቡነ አድኃኒ ዘዳሞት፣ አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል፣ አቡነ ኢዮስያስ ዘወጅ፣ አቡነ ዮሴፍ ዘእናርያን መርጠው ሀገረ ስብከት ተሰጥቷቸው ለሐዋርያዊ ተልእኮ ተሠማሩ፡፡ ዐሥራ ሁለቱን ንቡራነ ዕድ ለስብከተ ወንጌል በመላዋ አገሪቱ ሲሠማሩ፡፡
ጻድቁ አቡነ ቀውስጦስ አርሲ ፈንታሌ ተራራ ላይ ሠሪቲ ለምትባል ጠንቋይ እየተላላኩ ሕዝቡን የሚያስቱና የሚያሰቃዩ 470300 (አራት መቶ ሰባ ሺህ ሦስት መቶ) አጋንንትን በጸሎታቸው እሳት ከሰማይ አውርደው ተራውንን ደምስሰው አጋንንቱን ያቃጠሉ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ የታናሽ ወንድማቸው የዐፄ ይኩኖ አምላክ ልጅ ዐፄ አምደ ጽዮን በክፉዎች ምክር የአባቱን እቁባት በማግባቱ አቡነ ቀውስጦስ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ ሄደው ንጉሡን ስለገሠፁት በግዞት ወስዶ ጎናቸው በጦር ወግቶ ገድሏቸዋል፡፡ ጻድቁ ልደታቸውም ሆነ ዕረፍታቸው ከእመቤታችን ልደትና ዕረፍት ጋር የተባበረላቸው ናቸው፡፡ ግንቦት አንድ ቀን ተወልደው ጥር 21 ቀን ዐርፈዋል፡፡ 
የአቡነ ቀውስጦስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን፡፡
LIKE OUR PAGE https://www.facebook.com/tewadhdohaimanotachin

Wednesday, January 23, 2019

ጥር 15 - ወበዛቲ ዕለት

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈሰ ቅዱስ ስም አሜን
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 
ጥር 15-በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ የከበረች ወንጌልን ሰብኮ ጣዖት አምላኪዎችን በተአምራቱ ያሳመነውና ብዙ አሰቃቂ መከራዎችን የተቀበለው ሕፃኑ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ማኅበርተኞቹ የሆኑ ዓሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎችም አብረው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ 
+ በግራኝ ዘመን ከአንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር በእሳት ተቃጥሎ በሰማዕትነት ያረፈው አቡነ ቄርሎስ ዕረፍቱ ነው፡፡
+ የሶርያ ክርስቲያኖች በዚህች ዕለት በዓሉን በድምቀት የሚያከብሩለት የኑሲሱ አቡነ ጎርጎሪዮስ መታሰቢያ በዓሉ ነው፡፡ 
+ ነቢዩ ቅዱስ አብድዩ ዕረፍቱ ነው፡፡
አቡነ ቄርሎስ ኢትዮጵያዊ፡- አባታቸው ሳይንቱ እናታቸው ወለቃት ሲባሉ የመጀመሪያ ስማቸው መብዓ ሥላሴ ነው፡፡ በባሕታዊነታቸው መላ ገዳማቱ ሁሉ ያደንቋቸው የነበሩ ሲሆን እንደ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ 60 አንበሶችና 60 ነብሮች የተሰጣቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ጻድቁ በክፉው ግራኝ ዘመን ከአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጋር አብረው ተቃጥለው ነው በሰማዕትነት ያረፉት፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!


+++
ነቢዩ ቅዱስ አብድዩ፡- የስሙ ትርጓሜ ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋይ›› ማለት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ 1ኛ ነገ 18፡3 ላይ ‹‹አብደዩ እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር›› ተብሎ የተነገረለት እውነትም ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋይ›› የሆነ የነቢዩ ኤልያስ ደቀመዝሙር የነበረ ታላቅ ነቢይ ነው፡፡ ይህም ቅዱስ ነቢይ ከጠረፍ በረሃ አቅራቢያ ካለች ሱሳም በምትባል አገር ካሉ ሰዎች ወገን ነው፡፡ አባቱ ሐናንያ ይባላል፡፡ ለነቢዩ ኤልያስ ደቀ መዝሙሩ ሆኖ በንጉሡ በአክዓብምና በንግሥቲቱ በኤልዛቤል ምክንያት በእርሱ ላይ የመጣውን መከራ ሁሉ ታግሷል፡፡ ታላቁ ነቢይ ኤልያስ ከእነ ኤልዛቤል ሸሽቶ ወደ ተራራ ላይ ወጥቶ በዋሻ ተሸሽጎ ምግቡን አሞራ እያመጣለት በኖረበት ጊዜ እንኳን ነቢዩ አብድዩ ግን ብቻውን የእግዚአብሔርን ነቢያት ይንከባከብ ነበር፡፡ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥ የነበረ ቢሆንም ንግሥት ኤልዛቤል የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ አብድዩ መቶውን ነቢያት ወስዶ ሃምሳ ሃምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው የነበረ ታላቅ ባለውለታ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ታሪኩ እንዲህ ተብሎ ነው የተጻፈው፡-
‹‹ከብዙ ቀንም በኋላ በሦስተኛው ዓመት ‹‹ሂድ ለአክዓብ ተገለጥ፥ በምድር ላይም ዝናብ እሰጣለሁ›› የሚል የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኤልያስ መጣ፡፡ ኤልያስም ለአክዓብ ይገለጥ ዘንድ ሄደ፤ በሰማርያም ራብ ጸንቶ ነበር፡፡ አክዓብም የቤቱን አዛዥ አብድዩን ጠራ፤ አብድዩ እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤልም የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ እርሱ መቶውን ነቢያት ወስዶ አምሳ አምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው ነበር፡፡ አክዓብም አብድዩን ‹‹በአገሩ መካከል ወደ ውኃው ምንጭ ሁሉና ወደ ወንዝ ሁሉ ሂድ፤ እንስሶችም ሁሉ እንዳይጠፉ ፈረሶችንና በቅሎችን የምናድንበት ሣር ምናልባት እናገኛለን›› አለው፡፡ ሁለቱም የሚመለሱበትን አገር ተካፈሉ፤ አክዓብም ለብቻው በአንድ መንገድ አብድዩም ለብቻው በሌላ መንገድ ሄዱ፡፡
አብድዩም በመንገድ ሲሄድ እነሆ ኤልያስ ተገናኘው፤ አብድዩም አወቀው፣ በግምባሩም ተደፍቶ ‹‹ጌታዬ ሆይ! ኤልያስ አንተ ነህን? አለ፡፡ ኤልያስም ‹‹እኔ ነኝ ሄደህ ለጌታህ ‹ኤልያስ ተገኝቶአል› በል›› አለው፡፡ አብድዩም ‹‹እኔን ባሪያህን እንዲገድል በአክዓብ እጅ አሳልፈህ ትሰጠኝ ዘንድ ምን ኃጢአት አድርጌአለሁ? አምላክህ ሕያው እግዚአብሔርን! ጌታዬ ይፈልግህ ዘንድ ያልላከበት ሕዝብ ወይም መንግሥት የለም፤ ሁሉም ‹‹በዚህ የለም›› ባሉ ጊዜ አንተን እንዳላገኙ መንግሥቱንና ሕዝቡን አምሎአቸው ነበር፡፡ አሁንም እነሆ ‹ሂድ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር› ትለኛለህ፡፡ እኔም ከአንተ ጥቂት ራቅ ስል የእግዚአብሔር መንፈስ አንሥቶ ወደማላውቀው ስፍራ ይወስድሃል፤ እኔም ገብቼ ለአክዓብ ስናገር ባያገኝህ ይገድለኛል፤ እኔም ባሪያህ ከትንሽነቴ ጀምሬ እግዚአብሔርን እፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤል የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ መቶውን የእግዚአብሔር ነቢያት ወስጄ አምሳ አምሳውንም በዋሻ ውስጥ ሸሽጌ እንጀራና ውኃ የመገብኋቸው ነበር፡፡ ይህ ያደርግሁት ነገር በውኑ ለጌታዬ አልታወቀህምን? አሁንም ‹ሄደህ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር ትላለህ› እርሱም ይገድለኛል›› አለው፡፡
ኤልያስም ‹‹በፊቱ የቆምሁት የሠራዊት ጌታ ሕያው እግዚአብሔርን! እኔ ዛሬ ለእርሱ እገለጣለሁ›› አለ፡፡ አብድዩም አክዓብን ሊገናኘው ሄደ፣ ነገረውም፤ አክዓብም ኤልያስን ሊገናኘው መጣ፡፡ አክዓብም ኤልያስን ባየው ጊዜ ‹‹እስራኤልን የምትገለባብጥ አንተ ነህን?›› አለው፡፡ ኤልያስም ‹‹እስራኤልን የምትገለባብጡ፣ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ትታችሁ በኣሊምን የተከተላችሁ፣ አንተና የአባትህ ቤት ናችሁ እንጂ እኔ አይደለሁም›› አለው፡፡ 1ኛ ነገ 18፡1-20፡፡
ቅዱስ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥነቱን ትቶ የኤልያስ ቀደ መዝሙሩ ሆኖ በነቢይነት እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኖረ፡፡ በንጉሥ ኢዮሳፍጥ ዘመንም ትንቢትን ተናገረ፡፡ እግዚአብሔርም ስለ ትንሣኤና ስለ ፍርድ ቀን በቃሉ ነገረው፡፡ ሁለተኛም ከእስራኤል ልጆች የሚሆነውን ከአሕዛብም ለቀሩት አጸናቸው፣ አብዝቶ መከራቸው፣ ገሠጻቸውም፡፡ የትንቢቱም ወራት ሲፈጸም በዚህች ዕለት በሰላም በፍቅር አንድነት ዐርፏል፡፡ የትንቢቱም ወራት ሃያ ዓመት ነው፡፡ ይኸውም ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በ900 ዓመት ነው፡፡
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የሶርያ ክርስቲያኖች የኑሲሱን የአቡነ ጎርጎሪዮስን የዕረፍቱን በዓል በደማቅ ሁኔታ ያከበራሉ፡፡ በእኛ አቆጣጠር ግን ዕረፍቱ ጥር 21 ቀን ነው፡፡ (የጥር ሃያ አንዱን ይመለከቷል፡፡)
+ + +
ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ፡- ሦስት ዓመት እንኳን ሳይሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ታላቅ ሰማዕትነትን የተቀበለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አባቱ ቆዝሞስ (ስምዖን) እናቱ ኢየሉጣ ይባላሉ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ በኅዳር 15 ቀን የተወለደ ሲሆን ሀገሩ በታችኛው እስያ ልዩ ስሙ ሀንጌቤን ይባላል፡፡ ዘመኑ ዘመነ ሰማዕታት ነበርና መምለኬ ጣዖት የሆነው ንጉሥ እስክንድሮስ ቅድስት ኢየሉጣን ‹‹ለጣዖቴ ስገጂ›› ብሎ አስገደዳት፡፡ እርሷም ‹‹ሕፃኑ ልጄ መጥቶ ይመስክር›› ብላ ስትናገር ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጠራና ተጠየቀ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስም ‹‹ለጣዖት አንሰግድም፣ ዘላለማዊ የሆነ የማይሻር አምላክ ስላለ ለእርሱ ነው የምንሰግደው›› ብሎ የአምላኩን ክብር በሕፃን አንደበቱ መሰከረ፡፡ ሕፃኑም ይህንን በመሰከረ ጊዜ ዕድሜው ገና ሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ነበር፡፡
ነቢዩ ቅዱስ ዳዊትም ‹‹ከልጆችና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ›› ሲል እንደተናገረ (መዝ 10፡2፣ 118፡130) መድኃኔዓለም ክርስቶስም በቅዱስ ወንጌሉ ላይ ‹‹አባት ሆይ፣ የሰማይና የምድር ጌታ ይህን ከጥበበኞችና ከአስተዋዮች ሰውረህ ለሕፃናት ስለ ገለጥህላቸው አመሰግንሃለሁ›› ያለውን ቃል በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ሕይወት ተግባራዊ ሆኖ አይተነዋል፡፡ ማቴ 11፡27፡፡ በነቢዩም ትንቢት መሠረት በበዓለ ሆሣዕና ዕለት በእናታቸው እቅፍና ጀርባ ላይ የነበሩ እምቦቀቅላ ጨቅላ ሕፃናት ‹‹ሆሣዕና፤ በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው›› በማለት ጌታችንን አመስግነውታል፡፡
እንደዚሁ ሁሉ ቅዱስ ቂርቆስም በከሃዲው ንጉሥ ፊት የጌታችንን ክብር በመሰከረ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ 40 ጋን ውኃ የሚይዝ በርሜል አስጥዶ 40 ቀን ሙሉ እሳት አስነድዶ ቅንጭብ፣ ዘይት፣ ዝፍጥና ሌላም በእጅጉ የሚጎዱ ነገሮችን በውስጡ ጨምሮ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ወደዚያ እቶኑ እሳት እንዲከቷቸው አዘዘ፡፡ ንጉሡ እስክንድሮስ ጭፍሮቹን "ሰም፣ ጨው፣ ባሩድ፣ሙጫ፣ እርሳስ፣ ብረትን፣ ቅንጭብ፣ ቁልቋል ጨምሩበት" ብሎ አዘዛቸው፡፡ ጭፍሮችም ያዘዛቸውን ከፈጸሙ በኀላ መጥተው "ያዘዝከንን ሁሉ ጨምረንበት ነዶ ፈልቷል" አሉት፡፡ "ድምፁም እንደ ነጎድጓድ ይሰማል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ያንፀባርቃል፡፡ የፍላቱም ኃይል 14 ክንድ ያህል እየዘለለ ይወጣል፡፡ በውስጡ የሚጣሉትን ሰዎች እዘዝ" አሉት፡፡ ያንጊዜም ህፃን ቂርቆስንና እናቱን ኢየሉጣን ይዘው ከእስር ቤት አወጧቸው፡፡ በክርስቶስ ስም ስላመኑ በእስር ቤት አግብተው አስረዋቸው ነበርና ፍላቱ ወደ ላይ በሚዘል በብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ሲወስዷቸው በዚያን ጊዜም እልፍ ከአንድ ሺህ አራት መቶ ሰዎች እንዲወጡና በፈላው የብረት ጋን ውስጥ የቅዱሳንን አሟሟት እንዲያዩ ሹሙ አዘዘ፡፡ ቅድስት ኢየሉጣም የፍላቱን ግርማ ባየች ጊዜ ተሸበረች፡፡ ተጠብቆላት ያለውንም ዋጋ ትታ ልትክድ ፈለገች፡፡ ቅዱስ ቂርቆስም ይህን ባወቀ ጊዜ "እናቴ ሆይ ከብረት ጋን ግርማ የተነሳ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ" እያለ ከብሉይና ከሐዲስ እየጠቀሰ እንድትጸና አስተማራት፡፡
"ነገር ግን እናቴ ሆይ አናንያንና አዘርያን፣ ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከዕቶን እሳት እንዳወጣቸው እወቂ፤ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ውስጥ ሊያድነን ይችላል፡፡ እናት ሆይ ከሚያልፈው ከዚህ ዓለም ጭንቅ ልታመልጭ በሚያልፈው በዘለዓለም እሳት ልትቀጭ ትሻለች፡፡ እናት ሆይ ይህን አትሺ፤ ይቅርብሽ አሁን እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ ሶስናን ከሀጢያተኞች እጅ ያዳናት እኛንም ከብረት ጋን ያድነናል፡፡ ዳንኤልን ከአንበሶች አፍ ያዳነ እርሱ ያድነናል፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችን ልንፈፅም ፈቅዶም እንደሆነ የኢዮብን ነፃነት (ትእግስት) ልናገኝ ይገባናል፡፡ እርሱ ልጆቹንና ሚስቱን ያገኘው ገንዘብ ሁሉ አጥቶ በመጨረሻው ሰውነቱን አጥቶ ነበርና ምንም ምንም የቀረበለት አልነበረምና እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ ከማለት በቀር ያለው ነገር የለም እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔርም ወሰደ አለ፡፡ የእግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለም ይመስገን አለ፡፡ እኛም ይህንን መከራ ልንታገስና የተጠበቀልንን ልንከተል ይገባናል..." እያለ አብዝቶ መከራት፡፡ ነገርግን በዚህም ምክር እናቱን መመለስና ለሰማዕትነት ማዘጋቸት አልቻለም፡፡ ከዚህ በኋላ ቂርቆስ ዓይኖቹን ወደሰማይ አቅንቶ መጸለይ ጀመረ፡፡ "እግዚአብሔር ሆይ ይህች ባርያህ ከምትክድ ከህይወት መፅሐፍ እኔን ፋቀኝ አለ፡፡ አቤቱ ይህነን ነገር ልታደርግ አይገባህም፤ አቤቱ እርሻውን ልታቃጥል ፍሬውንም ልትባርክ ትወዳለህን፡፡ አቤቱ እንጨቱን ቁረጡና አንድዱት ቅጠሉን ጠብቁ ብለህ ልታዝ አይገባህም፡፡ እንጨቱንም ቅጠሉንም ጠብቁ ብለህ እዘዝ እንጂ ይህ አይገባህም ያመነብህ ሁሉ ይህን ያየ ዘንድ፡፡ ማዳን የሚችል አምላክ ኑሮአቸው ቢሆን ከዚህ ከእሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ እንዳይጠራጠር፡፡ ዲያብሎስ ከባለስልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ ቅዱሳኑም ድል ነሳኋቸው ብሎ እንዳይመካ፣ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ እንዳይል አቤቱ የኃይል መንፈስ ለእናቴ ስጣት አበርታት..." ብሎ ጸለየ፡፡ በዚያን ጊዜ ዲያብሎስ ከእርሷ ሸሽቶ ሄደ፡፡ ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ እንዲህ አለች፡- በመንግስተ ሰማያት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ጌታህ ኃይል ስጠኝ፡፡ የሚጠብቀንን ገድላችንን እንፈፅምና ድል እንነሣ" አለችው፡፡ የብረት ጋኑን ሲነድ ሳየው በምንጭ ላይ በዝቶ እንደሚወርድ ጠል ሁኖ አየዋለሁና፡፡ ቅዱሳንም ይህንን ሲነጋገሩ አንስተው ከብረት ጋኑ ውስጥ ጨመሯቸው፡፡ በውስጡም አንገትን የሚቆለምም ልብን የሚያጣምም ሆድን የሚሰነጥቅ ሥርንም የሚበጥስ መሣሪያ ነበረበት፡፡ ወዲያውም የራማው ልዑል ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ ከሰማይ ወረደና የብረት ጋኑን እሳት ፈጽሞ አበረደው፡፡ ከቅዱሳንም አንዱን እንኳን ሳይነካው የብረት ጋን ማቃጠሉና መፍላቱ ፀጥ አለ፡፡ እንደ ውኃም ሆነ፡፡
ንጉሡም እሳቱ እንዳልጎዳቸው ሲያውቅ ከዚያ አውጥቶ በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አፍና አፍንጫ መርዝ ከተተበት፣ ነገር ግን መርዙ ምንም አልጎዳውም እንዳውም ምግብ ሆነው፡፡ ዳግመኛም ጨውና በርበሬ በዐይኑ አነደደበት፡፡ አሁንም ምንም አልነካውም፡፡ ከዚህም በኀላ ሹም እስክድሮስም አስራ አራት የተሳሉና የጋሉ ብረቶች ያመጡ ዘንድ ዳግመኛ አዘዘ፡፡ ሰባቱን በእናቱ አካል ሰባቱን በሱ አካል ውስጥ ይተክሉ ዘንድ ከነዚሁም ሁለቱን በጆሮዎቹ ሁለቱን በዓይኖቹ ሁለቱን በአፍንጫዎቹ አንዱን በልቡ ይተክሉ ዘንድ አዘዘ፡፡በሕፃኑም ላይ ሹሙ እንዳዘዘው አደረጉበት፡፡ አሁንም ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና ፈወሳቸው፡፡
ዳግመኛም የሕጻኑን እራስ ከነቆዳው ገፈው በእሳት ውስጥ ይጨምሩ አንድ ሹም አዘዘ፡፡ እንዲሁም አደረጉበት፡፡ ዳግመኛም ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ መጥቶ ይህንን መከራ ከሕፃኑ አራቀለት፡፡ ዳግመኛም ሹሙ በመቃን ውስጥ ጨመረው በገመድ እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ከዚህም መከራ መልአኩ አዳነው፡፡ ሐምሌ 19 ቀን በዓሉን በታላቅ ድምቀት የምናከብረው ይህንን ሁሉ የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤልን ተራዳኢነት በማሰብ ነው፡፡
ንጉሡም በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በብዙ ጭንቅና ሥቃይ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ለ3 ዓመታት አሠቃያቸው፡፡ እነርሱም መከራን እየተቀበሉ በከሀዲው ንጉሥ ፊት የአምላካቸውን ስም እየጠሩ መሰከሩ፡፡ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና ክብሩን ይመሰክሩለት ዘንድ የቢታንያን ድንጋዮችና የበለዓምን አህያ አንደበት ከፍቶ ያናገረ አምላክ ሦስት ዓመት እንኳን ባለሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወር ሕፃን ልጅ ላይ አድሮ በወቅቱ የነበሩ ዓላውያን ነገሥታት ክብሩን እንዲያውቁ አደረገ፡፡
ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ሄሮድስ ላስፈጃቸው 144,000 የቤቴልሔም ሕፃናት አለቃቸው ነው፡፡ ይህስ እንደምን ነው ቢሉ ሄሮድስ ያስፈጃቸው እነኚያ እልፍ የቤቴልሔም ሕፃናት የተገደሉት ጌታችንን ለማግኘት በተደረገው ፍለጋ ምክንያት ስለሆነ ቅዱስ ቂርቆስን በመሞት ይተካከሉታል እርሱ ግን የአምላኩን ስምና ክብር በማስተማርና በመመስከር ሰማዕትነትን ስለተቀበለ በዚህ ይበልጣቸዋልና ለእነኚያ እልፍ የቤቴልሔም ሕፃናት አለቃ አድርጎ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሾሞታል፡፡ ቅዱስ ገድሉም እንደሚናገረው ‹‹መንገድ ጠራጊ ከተባለ ከዮሐንስ መጥምቅ በቀር ሴቶች ከወለዱዋቸው እንደ አንተ ያለ አልተገኘም›› በማለት ጌታችን በማይታበል ቅዱስ ቃሉ ታላቅ የሆነ ቃልኪዳኑን በመሐላ አጽንቶለታል፡፡ በመጨረሻም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጋድሎውን ፈጽሞ ጥር 15 ቀን በ3 ዓመት ከ1 ወር ከ3 ቀኑ አንገቱን በሰይፍ ተቆርጦ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡ ሲሰየፍም ከአንገቱም ደም፣ ውኃና ወተት የወጣ ሲሆን ሦስት አክሊላትም ወርደውለታል፡፡ ጌታችንም የመከራውን ጽናት የትዕግስቱን ብዛት አይቶ ከመከራ ሊያሳርፈው ፈቀደና ተገልጾለት ‹‹ሰላም ለከ ኦ ፍቁርየ ቂርቆስ›› አለው፡፡ ‹‹ሰላም ላንተ ይሁን፤ የመከራህን ጽናት፣ የትዕግስትህን ብዛት አይቼ ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍህ መጣሁ›› ብሎ ብዙ ቃልኪዳን ሰጠው፡፡ ‹‹…ስምህ በተጠራበት፣ ቤተመቅደስህ በታነጸበት፣ ስዕልህ ባለበት ቦታ ሁሉ የሕፃናት እልቂት፣ የከብት በሽታ፣ የእህል እጦት ርሀብ፣ ቸነፈር አይደርስም›› የሚል አስደናቂ ቃልኪዳንም ገብቶለታል፡፡ ሕፃኑም በምድር ላይ አልተቀበረም ይልቁንም ጌታችን በኤልያስ ሰረገላ ሥጋውን አሳርጎለታል፡፡ እናቱ ቅድስት ኢየሉጣም በጥር 16 ቀን ሰማዕትቷን በክብር ፈጽማለች፡፡ የቅዱስ ቂርቆስ ማኅበርተኞች የሆኑ ዓሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎች የጌታችንን ክብር እየመሰከሩ በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡
የቅዱስ ቂርቆስና ማኅበርተኞች የሆኑ የቅዱሳን ሰማዕታት ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!
ዳግመኛም ጥር 14 ቀን እነዚኽ ታላላቅ ቅዱሳን በዓመታዊ በዓላቸው ታስበው ውለዋል፡-
+ የዚህን ዓለም ሹመት ለመሾም ወደ ንጉሡ እየሄደ ሳለ ማዕበል የተፋው አንድ በድን ቢያገኝ በዚያው የዓለምን ኃላፊነትና የእርሱንም መሞት አስቦ የመነኮሰውና የሴትንም ፊት እንዳያይ ቃል ገብቶ በታላቅ ተጋድሎ የኖረው አቡነ አርከሌድስ ዕረፍቱ ነው፡፡ 
+ በ12 ዓመቷ ከከሃድያንን ነገሥታት ጋር ስለ እምነቷ ተጋድላ በሰማዕትነት ያረፈችው ቅድስት ምህራኤል ዕረፍቷ ነው፡፡ + መቋሚያቸው በሰው አንደበት የምትናገረውና የወይራ ዛፍ እንደተደገፉ ሳይንቀሳቀሱ 40 ዓመት ሙሉ የጸለዩት ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ አካለ ክርስቶስ ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ ዐፅማቸው ደብረ ዳሞ ያረፈው የወሎው አቡነ ዘድንግል ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ ዐፅማቸው ዋልድባ ዳልሻ የሚገኘው የትግራይ ተወላጁ አቡነ ምሥራቃዊ ልደታቸው ነው፡፡ 
+ ቅዱስ መክሲሞስ በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡ 
+ ቅድስት እምራይስ በሰማዕትነት ዐረፈች፡፡ 
+ ከተሰዓቱ ቅዱሳን ውስጥ አንዱና ዋነኛው የሆኑት ጻድቁ አቡነ አረጋዊ ልደታቸው ነው፡፡
ሰማዕቷ ቅድስት ምህራኤል፡- ይህችውም የከበረችና የተመሰገነች ቅድስት ምህራኤል ጠምዋህ ከሚባል አገር የተገኘች ታላቅ ሰማዕት ናት፡፡ ወላጆቿ ካህኑ አባቷ ዮሐንስና እናቷ ኢላርያ እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ደገኞች ናቸውና እርሷንም በሃይማኖት በምግባር ኮትኩተው አሳደጓት፡፡ መጀመሪያውንም ልጅ ስላልነበራቸው በስዕለት ከብዙ ዘመን በኋላ ነው ያገኟት፡፡ ስዕለታቸውም ደርሶላቸው ቅድስት ምህራኤልን ከወለዷት በኋላ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ አሳደጓት፡፡
ቅድስት ምህራኤልም 12 ዓመት በሆናት ጊዜ በላይዋ ባደረ በመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን መሥራት ጀመረች፡፡ ከሃዲው ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ በነገሠና አምልኮተ ጣዖትን በአዋጅ ባወጀ ጊዜ ቅድስት ምህራኤል ስለ ጌታችን አምላክነት መስክራ ሰማዕት መሆንን ተመኘች፡፡ ከዚህም በኋላ በቁርጥ ሀሳብ ተነሥታ ወደ ባሕር ዳርቻ በመሄድ በመርከብ ተሳፍራ ሄዳ ስሙ ፍልፍልያኖስ የሚባለው የዲዮቅልጥያኖስ መኮንን ዘንድ ደረሰች፡፡ በመርከብም ስትጓዝ ሌሎች ስለ ቀናች እምነታቸው ሰማዕትነትን ለመቀበል የተዘጋጁ ሰማዕታትን አግኝታ ከእነርሱ ጋር ነበረች፡፡ በመኮንኑም ፊት ቆማ እውነተኛውና ሊመለክ የሚገባው አምላክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ መሆኑን መሰከረች፡፡ መኮንኑም ስለ ታናሽነቷ ራርቶላት ከሌሎቹ ለይቶ ሊተዋት ወደደ፡፡ ነገር ግን ቅድስት ምህራኤል መኮንኑ እንደተዋት ዐውቃ የተመኘችውን ሰማዕትነት ሊያስቀርባት መሆኑን ባየች ጊዜ ዳግመኛ መኮንኑንና የረከሱ አማልክቶቹን በድፍረት ረገመችበት፡፡
ከዚህም በኋላ መኮንኑ በጣም ተቆጥቶ ጽኑ በሆኑ የተለያዩ ሥቃዮች አሠቃያት፡፡ ከቀናች ሃይማኖቷም ሸንግሎ ይመልሳት ዘንድ እንዳልተቻለው ሲያውቅ መርዛማ እባቦች፣ ጊንጦችና እፉኝቶች ወዳሉበት ጉድጓት ጣላት፡፡ ከቅድስት ምህራኤልም ጋራ ሌሎች ብዙ ሰማዕታት አብረው ተጣሉ፡፡ በዚህም ጊዜ የታዘዘ የእግዚአብሔር መልአክ ለቅድስት ምህራኤል ተገለጸላትና ከጌታችን ዘንድ የተሰጣትን ቃልኪዳን አስረከባት፡፡ ከዚህም በኋላ ነፍሷን ለእግዚአብሔር አሳልፋ ሰጥታ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች፡፡ ምእመናንም የከበረ ሥጋዋን መርዛማ እባቦችና ጊንጦች ካሉበት ቦታ አውጥተው በክብር ቀበሯት፡፡ በኋላም ወላጆቿ ልጃቸው ቅድስት ምህራኤል ስለ እምነቷ መስክራ በክብር ሰማዕት መሆኗን በሰሙ ጊዜ ከብዙ የሀገራቸው ሕዝብ ጋር መጥተው የከበረ ሥጋዋን አፍልሰው ወደ አገራቸው ወሰዱት፡፡ ያመረች ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው ሥጋውን በውስጧ ባኖሩ ጊዜ ከሰማዕቷ ቅዱስ ሥጋ ብዙ አስገራሚ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡
+ + +
አቡነ አርከሌድስ ግብፃዊ፡- በትውልዱ ከሮሜ ሀገር ከታላላቅ ወገኖች ነው፡፡ አባቱ ዮሐንስ እናቱ ሰንደሊቃ ሲባሉ ሁለቱም የእግዚአብሔርን ሕግ የሚጠብቁ እውነተኞች ነበሩ፡፡ ቅዱስ አርከሌድስም ዕድሜው 12 ዓመት በሆነው ጊዜ አባቱ ዮሐንስ ሞተ፡፡ በኋላም እናቱ ግን ሚስት ልታጋባው አሰበች እርሱ ግን ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ አባቱ በሕይወት ሳለ ንጉሡ የሾመው ነበርና እናቱ አሁንም ወደ ንጉሡ ሄዶ የአባቱን ሹመት ይቀበል ዘንድ አርከሌድስን መከረችው፡፡ ለንጉሡ የሚሰጥ እጅ መንሻንና አገልጋዮችን አድርጋ ብዙ ገንዘብ አስይዛ ላከችው፡፡ እርሱም በመርከብም ተጭኖ ሲሄድ ታላቅ ንፋስ ተነሣና ማዕበሉ አየለባቸው፡፡ መርከቡም ተሰበረ፡፡
ቅዱስ አርከሌድም አንዲት የመርከብ ስባሪ ሠሌዳ ላይ ተንጠልጥሎ ወደ የብስ ደረሰ፡፡ ከባህሩ ሲወጣ ማዕበል የተፋው አንድ በድን አገኘና ተቀምጦ ስለ በድኑ አለቀሰ፡፡ የዓለምን ኃላፊነትና እርሱም ከሞተ በኋላ አፈርነቱን አሰበ፣ ነፍሱንም ገሠጻት፡፡ ወደ ቀና መንገድ ይመራውም ዘንድ ወደ ጌታችን ለመነ፡፡ ረጅም መንገድ ተጓዘና ሶርያ ውስጥ በቅዱስ ሮማኖስ ስም ወደተሠራች አንድ ተራራማ ገዳም ደረሰ፡፡ ከገንዘቡም ከእርሱ ጋር የቀረውን ሁለት መቶ የወርቅ ዲናር ለአበ ምኔቱ ሰጠው፡፡ እንዲያመነኩሰውም ጠየቀው፡፡ መጀመሪያውኑ አርኬሌድስ ከመምጣቱ በፊት ለአበምኔቱ መንፈስ ቅዱስ የመምጣቱን ነገር አስረድቶት ነበርና እርሱ በደረሰ ጊዜ ደስ አለው፡፡ መነኮሳቱም ሁሉ ከጸለዩለት በኋላ አመነኮሰው፡፡
ከዚህም በኋላ የከበረ አርከሌድስ ጽኑ ተጋድሎ መጋደል ጀመረ፡፡ ሲጸልይ ይውላል ሲጸልይ ያድራል፤ ሁልጊዜ በየሰባቱ ቀን የሚጾም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም ሀብተ ፈውስን ሰጥቶት ብዙ ሕመምተኞችን ፈወሳቸው፡፡ ከዚህም በኋላ የሴቶችን ፊት ከቶ እንዳያይ ከጌታችን ጋር ቃል ገባ፡፡ ። እናቱም ለ12 ዓመት ያህል የልጇን ወሬ ምንም ስላልሰማች በእርሱ የሆነውን አላወቀችም ነበርና የሞተም ስለመሰላት እጅግ አዘነች፡፡ የእንግዶችና የመጻተኞች መቀበያ የሚሆን ቤት ሠርታ የመንገደኞች ማደርያ አደረገችው፡፡ በአንዲት ዕለት ያሳደረቻቸው እንግዶች የቅዱስ አርከሌድስን ዜና ሲናገሩ ሰማቻቸው፡፡ እንግዶቹም ስለ ቅድስናው፣ ስለ ተጋድሎው የሚያሳያቸውን ምልክቶችና ተአምራቶቹን፣ የመልኩንም ደም ግባት ሲነጋገሩ ሰምታ ልጇ እንደሆነ ዐወቀች፡፡
መንገደኞቹንም ስለ ሥራው ጠየቀቻቸውና ሥራውን ሁሉ ነገሯት፡፡ ልጇ በሕይወት እንዳለና ሕያው እንደሆነ ተረዳች፡፡ በዚያን ጊዜ ተነሥታ ወደ ከበረ ሮማኖስ ገዳም ሄደች፡፡ ወደ ልጇዋ ወደ ቅዱስ አርከሌድስ ‹‹እነሆ ፊትህን አይ ዘንድ ወድጄ እኔ እናትህ መጥቻለሁ›› ብላ መልእክት ላከች፡፡ ልጇ ቅዱስ አርከሌድም ‹‹ከቶ የሴቶችን ፊት እንዳላይ ከክብር ባለቤት ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃል ገብቻለሁና ቃልኪዳኔን ማፍረስ አይቻለኝም›› ብሎ መልሶ ወደእርሷ ላከ፡፡ እናቱም ‹‹ፊትህን ካላሳየኸኝ እኔ ወደ ዱር እሄዳለሁ፣ አራዊትም ይበሉኛል›› ብላ ላከችበት፡፡ ቅዱስ አርከሌድስም እናቱ ካላየችው እንደማትተወው እርሱም ለእግዚአብሔር የገባውን ቃልኪዳን ማፍረስ እንደማይቻለው ባወቀ ጊዜ ነፍሱን እንዲወስዳት ወደ ጌታችን ለመነ፡፡ ከዚህም በኋላ የበሩን ጠባቂ ‹‹እናቴን ወደእኔ ትገባ ዘንድ ፍቀድላት›› አለው፡፡ እናቱም ወደ ውስጥ በገባች ጊዜ ልጇን ቅዱስ አርከሌድስን ሙቶ አገኘችውና በታላቅ ድምፅ በመጮህ አለቀሰች፡፡ የእርሷንም ነፍስ ይወስድ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነች፡፡ ጌታችንም ልመናዋን ተቀብሎ ነፍሷን ወሰደ፡፡
እናትና ልጅም በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ካረፉ በኋላ የሁለቱን ሥጋቸውን ለይተው ሊቀብሯቸው ሲሉ የቅዱስ አርከሌደስ በድን በሰው አንደበት መናገር ጀመረ፡፡ ‹‹የእናቴን ሥጋ ከሥጋዬ አትለዩ በሕይወቷ ሳለች ታየኝ ዘንድ ልቧን ደስ አላሰኘሁምና›› የሚል ቃል ከአርከሌድስ በድን ወጣ፡፡ ይህንንም ቃል በሰሙ ጊዜ እጅግ አድንቀው እግዚአብሔርን ካመሰገኑት በኋላ ሁለቱንም በአንድ መቃብር ውስጥ ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም በቅዱስ አርከሌድና በእናቱ ሥጋ ላይ ታላቅ ፈውስን ገለጠና አስገራሚ ተአምራት መታየት ጀመሩ፡፡ በሞት ካረፈ በኋላ በድኑ አፍ አውጥታ የተናገረች ይህ ታላቅ ጻድቅ በስሙ የተሰየመው ትልቅ ገዳም ትግራይ ተንቤን ሀገረ ሰላም ይገኛል፡፡
+ + +
ቅድስት እምራይስ፡- ይኽችውም ቅድስት ከከበሩ ደገኛ ክርስቲያኖች የተወለደች ናት፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እየተማረች አደገች፡፡ በአንዲትም ዕለት ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ ወርዳ ሳለ ተይዘው ስለ ክርስቶስ ታስረው የሚሠቃዩ ሰማዕታትን አየች፡፡ እነርሱም ጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት ናቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ቅድስት እምራይስ ወደ መኮንኑ ጭፍራ ዘንድ ቀርባ ‹‹እኔም በእነዚህ ቅዱሳን አምላክ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝና ስሜን ከስማቸው ጋር ጽፈህ ወደ ሰማዕትነት አደባባይ አድርሰኝ›› አለቸው፡፡ እርሱም ስሟን ከሰማዕታቱ ስም ጋራ ጽፎ አብሮ አሰራትና በከሃዲው መኮንን ቁልቁልያስ ፊት አቆማት፡፡ መኮንኑም ለጣዖታቱ እንድትሰግድ በብዙ የስንገላ ቃላት አባበላት ነገር ግን ቅድስት እምራይስ የጌታችንን አምላክነት እየመሰከረች የመኮንኑን ጣዖታት ረገመችበት፡፡ መኮንኑም እጅግ ተቆጥቶ አንገቷን በሰይፍ አስረጠውና ሰማዕትነቷን በድል ፈጽማ የክብር አክሊልን ተቀዳጀች፡፡
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የከበረ ሕፃን የቅዱስ ቂርቆስ ማኅበርተኞች የሆኑ አራት ሺህ ሠላሳ አራት ሰዎች በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ ዜና ገድላቸው ከአባታቸው ከሕፃኑ ከቅዱስ ቂርቆስ ዕረፍት ጋር ጥር 15 ተጽፏል፡፡
የእጅግ የከበረ የቅዱስ ዱማቴዎስ ወንድም ቅዱስ መክሲሞስም ዕረፍቱ በዚሁ ዕለት ነው ነገር ግን ገድሉን በዚሁ ወር በ17 ከወንድሙ ታሪክ ጋር እንጽፈዋለን፡፡
የቅዱሳን ሰማዕታት ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!
 

Friday, January 18, 2019

እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ

እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ



ጥምቀት


ጥምቀት በጽርዕ ቋንቋ ኤጲፋኒያ በግእዝ አስተርዮ በአማርኛ መገለጥ ይባላል፡፡ ቃሉ በቀጥታ ሲተረጎም በውኃ ውስጥ ገብቶ መውጣት፣ መነከር፣ መዘፈቅ፣ መጥለቅ ማለት ነው፡፡ ጥምቀት ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተክርስቲያን (ምሥጢረ ጥምቀት፣ ምሥጢረ ሜሮን፣ ምሥጢረ ቁርባን፣ ምሥጢረ ንስሐ፣ ምሥጢረ ክህነት፣ ምሥጢረ ተክሊል፣ ምሥጢረ ቀንዲል) አንዱና ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ በዮሐ. 3፥5 ላይ ‹‹እውነት እውነት እልሀለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡›› ብሎ እንደተናገረው ከውኃና ከመንፈስ ተወልደን የሥላሴን ልጅነት የምናገኝበት መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት ኃጢአታችን የሚደመሰስበት ድኅነትን የምናገኝበት ዐቢይ ምሥጢር ነው፡፡ ጥምቀት በምሥጢረ ሥላሴና በምሥጢረ ሥጋዌ አምኖ ለሚፈጽመው ሰው ሁሉ ለኃጢአት መደምሰሻ ከሥላሴ የጸጋ ልጅነት ለመቀበልና የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የተሰጠ ልዩ የሕይወት መንገድ ነው፡፡

የጥምቀት አመጣጥ

የምሥጢረ ጥምቀት መስራች ራሱ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ነገር ግን ከጌታችን ጥምቀት በፊት አይሁድ ለመንጻትና ለኃጢአት ሥርየት (ይቅርታ) የሚጠመቁት ጥምቀት ነበራቸው፡፡ ይኸውም እግዚአብሔር በረድኤት የሚገለጥባቸው የተቀደሱ ዕለታትና ቦታዎች ሁሉ ሰውነትንና ልብስን ማጠብ የእግዚአብሔር ቤት ማገልገያ የሆኑ ዕቃዎችን ሁሉ ማጠብ ማንጻት ሥርዓትና ልማድ ነበር፡፡ የእግዚአብሔርም ፈቃድ ያለበት አሠራር ነበር፡፡ ወደ እግዚአብሔር ቤት ከመቅረባቸውና ለተቀደሰው አገልግሎት ከመግባታቸው አስቀድመው እግሮቻቸውንና እጆቻቸውን የመታጠብ ግዴታም ነበራቸው፡፡ ሰውነታቸውን ከአፍአዊ (ከውጫዊ) እድፍ በማጠብና ንጹሕ በማድረግ በባሕርይ ንጹሕና ቅዱስ በሆነው አምላክ ፊት ውስጣዊ ሕይወትን ንጹሕ አድርጎ የመቅረብን ሥርዓትና ምሥጢር የሚያመለክት ልማድ ነበር፡፡
‹‹አሮንንና ልጆቹን ወደ ምስክሩ ድንኳን ደጃፍ ታቀርባቸዋለህ፤ በውኃም ታጥባቸዋለህ›› /ዘፀ. 29፥4/
‹‹ሙሴም አሮንንና ልጆቹን አቀረበ፣ በውኃም አጠባቸው፡፡›› /ዘሌ. 8፥6/
በብሉይ ኪዳን ዘመን የጥምቀት ምሳሌዎች

1. አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ መልከጼዴቅ መሄዱ የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡ አብርሃም የምእመናን መልከጼዴቅ የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ናቸው፡፡ /ዘፍ. 14፥17/

2. ኢዮብ በዮርዳኖስ ተጠምቆ ከደዌው ተፈውሷል፡፡ ይህም ምእመናን ተጠምቀው ከደዌ ሥጋ ከደዌ ነፍስ የመፈወሳቸው ምሳሌ ነው፡፡

3. ንዕማን ሶርያዊ ተጠምቆ ከለምጽ ድኗል፡፡ 2ነገ. 5፥14 ይኸውም ምእመናን ተጠምቀው ከመርገመ ሥጋ ከመርገመ ነፍስ የመዳናቸው ምሳሌ ነው፡፡

4. የኖኅ መርከብ የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡ ዘፍ. 6፥13 ይኽንንም ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍሳት በውኃ የዳኑባትን መርከብ ሲሠራ በኖኅ ዘመን የእግዚአብሔር ትዕግሥት በዘገየ ጊዜ ቀድሞ ክደውት ለነበሩት ሰበከላቸው፡፡ አሁንም እኛን በዚያው አምሳል በጥምቀት ያድነናል ሥጋን ከዕድፍ በመታጠብ አይደለም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመነሣቱ በእግዚአብሔር እንድናምን መልካም ግብርን ያስተምረን ዘንድ ነው እንጂ፡፡›› /1ጴጥ. 3፥20/

5. እስራኤል በደመና ተጋርደው ቀይ ባሕርን መሻገራቸው የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡ /ዘፀ. 14፥15/ ይኽንንም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹አባቶቻችን ሁሉ ደመና እንደ ጋረዳቸው ሁሉም በባሕር መካከል አልፈው እንደ ሄዱ ልታውቁ እወዳለሁ፡፡ ሁሉንም ሙሴ በደመናና በባሕር አጠመቃቸው›› /1ቆሮ. 10፥1/

6. ለአብርሃም ሕግ ሆኖ የተሰጠው ግዝረት የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡ አብርሃም ከአረጀ በኋላ ቢገረዝም ልጆቹ ግን በተወለዱ በስምንተኛው ቀን እንዲገረዙ እግዚአብሔር አዞ ነበር /ዘፍ. 17፥9/ ‹‹በሰው እጅ የአልተደረገ መገረዝን በእርሱ ሆናችሁ ተገረዛችሁ፡፡ በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችኋል በእርስዋም ከሙታን ለይቶ ባስነሣው በእግዚአብሔር ረዳትነትና በሃይማኖት ከእርሱ ጋር ተነሥታችኋል፡፡›› /ቈላ. 2፥11/

ጌታችን ለምን ተጠመቀ?

1. ሚሥጢርን ለመግለጥ፡- ጌታችን በፈለገ ዮርዳኖስ ሲጠመቅ ሚስጢረ ሥላሴ ግልፅ ሆኗል፡፡ አብ በደመና “የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው” በማለቱ አብ የወልድ አባት መሆኑ ታወቀ፡፡ መንፈስ ቅዱስም የባሕርይ ሕይወቱ መሆኑን ሲያስረዳ በአምሳለ ርግብ በራሱ ላይ ተቀመጠ ወልድም በተለየ አካሉ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ ታየ፡፡ ስለዚህ ምሥጢርን ለመግለጥ ስንል የአንድነት የሦስትነት ምስጢር በጐላ ሁኔታ እንዲታወቅ ተጠመቀ ማለት ነው፡፡ /ማቴ. 3፥16/

2. ትንቢቱን ለመፈፀም፡- በመዝ 46/77/፤16 ላይ “አቤቱ ውሆች አዩህ፣ ውሆችም አይተውህ ፈሩ ጥልቆች ተነዋወጡ ውሆችም ጮኹ፡፡” ተብሎ በቅዱስ ዳዊት የተነገረውን ትንቢት ለመፈፀም ተጠመቀ፡፡

3. አርአያ ሊሆነን፡- ተጠምቆ እንድንጠመቅ አደረገን ሥርዓትን ሠራልን ቀድሞ በአርአያውና በአምሳሉ እንደፈጠረን አሁንም አርአያ ምሳሌ ሆነን፡፡ ለዚህም ነው ምሳሌን ከእኔ ተማሩ ያለን፡፡ /ማቴ 11፤29/ ለትምህርት ለአርአያ /ዮሐ. 13፥1-17/

4. የዕዳ ደብዳቤያችንን ለመደምሰስ፡- አዳምና ሔዋን ፍዳው በፀናባቸው መከራው በበዛባቸው ጊዜ የሚያቃልልላቸው መስሏቸው ዲያብሎሰ ስመ ግብርናችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ ባላቸው ጊዜ አዳም ገብሩ ለዲያቢሎስ (አዳም የዲያብሎስ የወንድ አገልጋይ) ሔዋን ዓመቱ ለዲያብሎስ (ሔዋን የዲያብሎስ ሴት አገልጋይ) ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ዲያብሎስም ይህንን ደብዳቤ አንዱን በሲኦል አንዱን በዮርዳኖስ አስቀመጠው፡፡ በዮርዳኖስ ያስቀመጠውን ጌታችን ሲጠመቅ እንደሰውነቱ ረግጦ ደምስሶታል፡፡ ይህንን ጽሕፈት ለመደምሰስ ነው ጌታችን በዮርዳኖስ የተጠመቀው፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተፃፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፡፡” ያለው ቆላ 2፤14

ጌታችን መች ተጠመቀ?

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀው በ5531 ዓመተ ዓለም ዘመነ ሉቃስ ማክሰኞ ጥር 11 ቀን ከሌሊቱ በ10ኛው ሰዓት ነበር፡፡ ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 19 በተጠመቀም ጊዜ ዕድሜው 30 ዓመት ከ13 ቀን ነበር፡፡ /ሉቃ. 3፥23/

ጌታችን ስለምን በ30 ዓመት ተጠመቀ?

በብሉይ ኪዳን ሥርዓትና ልማድ ካህናት ለቤተ እግዚአብሔር ተልእኮ እና መንፈሳውያን አገልግሎቶች ከ30 ዓመት ዕድሜ በፊት አደባባይ አይወጡም ነበር፡፡ እጅግ አስፈላጊ እንኳ ቢሆን ከ20 እና 25 ዓመት አስቀድሞ ለአገልግሎት መሰየም ልማድ አልነበረም፡፡ የቤተ እግዚአብሔር አገልጋዮች በዕድሜና በዕውቀት የበሰሉ፣ በጠባይና በሥራ ልምድ የተፈተኑ ተልዕኳቸውን በብቃት ለመወጣት በተገልጋዩ ሕዝብ ዘንድ የተመሰከረላቸው መሆን ነበረባቸው፡፡ /ዘፀ. 4፥3፤1ዜና መዋ. 23፥24፤ 1ጢሞ. 3፥6-10/ ያንን ሥርዓት ለመፈጸም ጌታችን የተጠመቀውና ለትምህርተ ወንጌል የተገለጠው በ30 ዓመቱ ነበር፡፡ ዮሐንስ መጥምቅም የጌታን መምጣት ለማወጅ በዮርዳኖስ ይሁዳ ምድረ በዳዎች ወጥቶ የታየው ከ30 ዓመት ዕድሜው በኋላ ነው፡፡ ሌላው ዐቢይ ምክንያት የሰው ሁሉ መጀመሪያ አዳም የ30 ዓመት ጎልማሳ ሆኖ ተፈጥሮ በ40ኛ ቀን ተሰጥቶት ኋላም በኃጢአት ምክንያት ያስወሰደውን ልጅነት ለማስመለስ ነው፡፡ ክርስቶስ የተጠመቀው ክብር ሽቶ ሳይሆን የአብ የባሕርይ ልጅነቱን (የባሕርይ አምላክነቱን) ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ለማስመስከር፣ ውኃውን ለመቀደስ፣ የአዳምን ልጆች የእዳ ደብዳቤ ለመደምሰስና በስህተት የጠፋውን የልጅነት ክብር ለመመለስ ነው፡፡ ጌታ ተጠምቆ ከውኃው ከወጣ በኋላ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ በማረፍ አብ በደመና ‹‹ይህ ልጄ ነው›› ብሎ ሲመሰክርለት ምሥጢረ ሥላሴ አንድነትና ሦስትነት በጉልህ ተረጋግጧል፡፡ /ማቴ. 3፥16/

ጌታችን በዮሐንስ እጅ ለምን ተጠመቀ?

ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ ሲሆን በአገልጋዩ በቅዱስ ዮሐንስ እጅ ይጠመቅ ዘንድ በፍጹም ትሕትና ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ ይህንንም ያደረገልን አብነት ሊሆነን ነው፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ቅዱስ ዮሐንስን ‹‹መጥተህ አጥምቀኝ ›› ብሎት ቢሆን ኖሮ ነገ ነገሥታቱና መኳንንቱ ካህናቱን መጥታችሁ አጥምቁን ባሉ ነበር ስለዚህ እንዲህ እንዳይሆን ነው፡፡ ጌታችን ‹‹ጌታ ስሆን በባርያዬ እጅ እንደተጠመቅሁ እናንተም ወደ ቤተክርስቲያን ሄዳችሁ በካህናት እጅ ተጠመቁ›› ሲል ነው፡፡

ጌታችን በዮርዳኖስ የተጠመቀው ልጅነትን የምታሰጥ ጥምቀትን ባርኮ ቀድሶ ሊሰጠን እንጂ ክብር እንዲሆነው አይደለም፡፡ ምክንያቱም፡- እርሱ እከብር አይል ክቡር እጸድቅ አይል ጻድቅ ነውና፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን በማን ስም አጠመቀው?

ጌታችን ዮሐንስን አጥምቀኝ ባለው ጊዜ ‹‹ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ አንተን በማን ስም ላጥምቅህ? በአብ ስም እንዳላጠምቅህ አብ አባትህ ባንተ ሕልው ነው በወልድ ስም እንዳላጠምቅህ ወልድ አንተ ነህ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንዳላጠምቅህ መንፈስ ቅዱስ ሕይወትህ ባንተ ሕልው ነው ታዲያ በማን ስም ላጥምቅህ?›› ብሎ ቢጠይቀው ጌታም ‹‹እንደ መልከጼዴቅ ሥርዓት አንተ የዓለም ካህን ብርሃንን የምትገልጥ የአብ የባሕርይ ልጅ ሆይ ይቅር በለኝ›› ብለህ አጥምቀኝ አለው፡፡

ዮሐንስ ጌታን ሲያጠምቀው እጁን ለምን አልጫነበትም?

- ዮሐንስ በጥምቀት አከበረው /ልዕልና ሰጠው/ እንዳይባል፡፡
- መለኮትን በእጅ መንካት ስለማይቻል

ጌታችን ጥምቀቱን ለምን በዮርዳኖስ አደረገው?

በኢየሩሳሌም አካባቢ ብዙ ወንዞች ኩሬዎችና ሐይቆች መኖራቸው የታወቀ ነው፡፡ ጌታ ጥምቀቱን በዮርዳኖስ ያደረገው ስለዚሁ አስቀድሞ የተነገረውን ትንቢት መፈጸሙን ለማረጋገጥ ነው፡፡ ‹‹ባሕር አይታ ሸሸች ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ›› /መዝ. 113፥3/ ከዚህም ጋር ከላይ ምንጩ አንድ የሆነው ዮርዳኖስ ዝቅ ብሎ በደሴት ተከፍሎ እንደገና እንደሚገናኝ በግዝረት በቁልፈት (በመገዘርና ባለመገዘር) ተለያይተው የነበሩ ሕዝብና አሕዛብ መላው የአዳም ልጆች በጌታችን ጥምቀት አንድ መሆናቸውን የሚገልጽ ትርጉም አለው፡፡ እስራኤል ዮርዳኖስን ተሻግረው ምደረ ርስት ገብተዋል፡፡ ያመኑ የተጠመቁ ምዕመናንም በጥምቀት ገነት መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉ፡፡ ሌላው በዮርዳኖስ ተጥሎ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤ ይደመስስልን ዘንድ /ቈላ. 2፥14/

ጌታችን ለምን በሌሊት ተጠመቀ?

በኃጢአት ጨለማ ስለነበረ ሕዝብ የጽድቅ ብርሃን እንዲወጣለትና በጨለማ የሚመስል ኦሪት ይኖር ስለነበረ ለሕዝብ ብርሃን የሆነ ወንጌል መገለጡን ለማሳየት ነው፡፡ ኢሳ. 9፥2

- አንድም ጌታ ልደቱ፣ ጥምቀቱ፣ ትንሣኤው እንዲሁም ምጽአቱ በሌሊት ነው፡፡ ይኽም የሆነበት ምክንያት፡- ሌሊቱን ተከትሎ የሚመጣው ብርሃን በመሆኑ ከሞት ወደ ሕይወት ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሲኦል ወደ ገነት የመሸጋገራችን ምሳሌ ነው፡፡

- አንድም መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል የሚወርድ ነውና በጌታ ላይ የወረደው ርግብ እንጂ መንፈስ ቅዱስ አይደለም ባሉ ነበር፡፡ በሌሊት ርግብ የለም ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ይታወቅ ዘንድ፡፡
መንፈስ ቅዱስ ለምን ጌታ ከውኃ ከወጣ በኋላ ወረደ?

ሀ. ዮሐንስን ያከብሩት ነበርና መንፈስ ቅዱስ የወረደው ለዮሐንስ እንጂ ለጌታ አይደለም ይሉ ነበርና ምክንያቱን ጌታ ውኃ ውስጥ እያለ ከዮሐንስ አልተለየም ነበርና፡፡

ለ. ውኃን የሚባርክ መልአክ እንዳለ ያውቁ ነበርና ውኃውን ለመባረክ አንጂ ለጌታ አይደለም እንዳይባል፡፡

ሐ. ማረፊያ ያጣች ርግብ በባሕር ስትበር አረፈችበት ባሉ ነበርና ሐሳባቸውን በሙሉ ያጠፋ ዘንድ ከውኃ ውስጥ ከወጣ በኋላ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወረደ፡፡ 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl





https://www.youtube.com/watch?v=3fnWuuHj5ZM

Thursday, January 17, 2019

እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ


አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን

ጥር 10 እና 11-ይህቺ ዕለት በዮናኒ ቋንቋ ኤጲፋንያ ትባላለች፣ ትርጓሜውም መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው፡፡ ልዑል እግዚአብሔር ልዩ የሆነች የሦስትነቱን ምሥጢር ገልጦባታልና ይህች ዕለት እጅግ የከበረች ናት፡፡ መጥምቁ ዮሐንስም ለዚኽ ነው ጌታችንን ከማጥመቁ በፊት ጌታችንን - "አቤቱ አምላኬ ሆይ! የአብ ስም በአንተው አለ፣ የወልድ ስም አንተው ነህ፣ የመንፈስ ቅዱስም ስም በአንተው ሕልው ሆኖ አለ፡፡ ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ፣ አንተን ግን በማን ስም አጠምቃለሁ? ብሎ የጠየቀው!



በዚኽች በከበረች የጥምቀት ዕለት በጥምቀት ወቅት የክብር ባለቤት ጌታችንና ያጠመቀው ቅዱስ ዮሐንስ ብለው እንደተነጋገሩ፡- ‹‹በዚያን ቀን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ ያጠምቀው ዘንድ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወደ ዮሐንስ መጣ፡፡ ዮሐንስም በእርሱ ላይ አድሮበት ባለው በመንፈስ ቅዱስ ፀጋ ጌታችን ወደ እርሱ ሲመጣ ባየው ጊዜ አሰምቶ ጮኸ፤ በታላቅ ቃልም እንዲህ አለ፡- እኛን ለማዳን የመጣው የእግዚአብሔር በግ እነሆ፡፡ ነቢያትም ስለ እርሱ ትንቢት የተናገሩለት ንጉሠ ነገሥት ይህ ነው፡፡ በዕውነት ቀዳሚና ተከታይ የሌለውና ለመንግሥቱም ፍጻሜ የሌለው አምላክ ይህ ነው፡፡ ዮሐንስም ይህን ቃል እየተናገረ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጠርቶ እንዲህ አለው፡- ዮሐንስ ሆይ! ስለ እኔ የተጻፈውን ሕግ ሁሉ ትፈጽም ዘንድ እነሆ ይገባሃል፤ እነሆ በአየኸው ሁሉ ምስክር ትሆን ዘንድ በአንተ እጅ የምጠመቅበት ጊዜ ስለደረሰ አጥምቀኝ አለው፡፡ ዮሐንስም ለጌታችን እንዲህ ብሎ መለሰለት፡- ወደ አንተ መጥቼ መጠመቅ ለእኔ ይገባኛል እንጂ እኔ ባሪያህ ሆኜ ሳለሁ በእኔ እጅ ትጠመቅ ዘንድ ስለምን ወደ እኔ መጣህ? አንተ ጌታ ሆነህ ይህ ነገር ፈጽሞ አይገባም አለው፡፡ ጌታችንም ዮሐንስ ሆይ! በአንተ እጅ ስለመጠመቄ ደስ መሰኘት ይገባሃል፤ አትፍራም፡፡ አንተ እጅህን በራሴ ላይ ታኖራለህ፤ ሰውነቴንም እኔ አጠምቃታለሁ፡፡ ዮሐንስ ሆይ! እንቢ አትበለኝ እነሆ ነቢያት ስለ እኔ የተናገሩትን ሕግና ትእዛዝን ሁሉ ልፈጽም መጥቻሁና አለው፡፡ ጌታችንም ይህን ቃል ለዮሐንስ ነግሮት ከጨረሰ በኋላ ወደ ዮርዳኖስ ውኃ ውስጥ ገባ፡፡ ያንጊዜ ዮርዳኖስ አርባ ክንድ ወደኋላው ተመለልሶ ሸሸ፣ ውኃውም በእሳት እንዳፈሉት ሆነ፡፡ በጸናችው የጥበቡ ኃይል አዳምን ከነልጆቹ ለማዳን ወደዚህ ዓለም ከመጣው ከጌታችን ፊት ዮርዳኖስ ስለ መሸሿና ወደ ኋላዋ ስለ መመለሷ ነቢዩ ዳዊት ትንቢት ተናግሮአል፡- አቤቱ ውኆች አዩህ፣ ውኆችም አይተውህ ፈሩ፡፡ አንቺ ባሕር የሸሸሽው፣ አንቺ ዮርዳኖስ ወደ ኋላ የተመለሽው ምን ሆናችኋል? ጌታችንም ዮርዳኖስን እንዲህ በማለት ገሠፀው፡- ዮርዳኖስ ሆይ! በጥምቀቴ ጊዜ አትሽሽ፣ ባለህበት ቦታም ተመልሰህ ቁም አለው፡፡ ጌታችንም ይህን ቃል በተናገረው ጊዜ የነቢዩ ዳዊት ትንቢት ይደርስ ዘንድ ውኃው ወደ ቦታው ተመልሶ ቆመ፤ ከጌታችንም ፊት ሰገደ፡፡ ዮሐንስም ዮርዳኖስ ወደ ኋላዋ ተመልሳ መሸሿንና በጌታችን ትእዛዝ ወደ ቀድሞ ቦታዋ ተመልሳ ከጌታችን ፊት ስትሰግድ ባየና በተመለከተ ጊዜ ፈራ፣ ደነገጠ፣ ታላቅ መንቀጥቀጥም አደረበት፣ በፊቱም ሰገደለት፡፡እነሆ አንተ ጌታዬና ፈጣሪዬና ነህ እኔ አገልጋይህ ባሪያህ ነኝ፣ አቤቱ ጌታዬ ሆይ! ይህን ሁሉ ደካማነቴን ተመልክተህ እጁን በራስህ ላይ ያኖር ዘንድ ባሪያህን አታስገድደው አለው፡፡ ጌታችንም ለዮሐንስ እንዲህ አለው፡- ይህ ለእኛ ተድላ ደስታ ነውና እውነትን ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና ያዘዝኩህን አድርግ አለው፡፡ አንተም መጥምቀ መለኮት ተብለህ ክብርህ ይነገራልና እኔም በባሪያው እጅ ተጠመቀ ተብዬ ትሕትናዬ ይነገራልና አለው፡፡ ይህንንም ሲናገረው ዮሐንስ ተወው፡፡ ዮሐንስም እንዲህ አለው፡- የአብ ስም በአንተው አለ፣ የወልድ ስም አንተው ነህ፣ የመንፈስ ቅዱስም ስም በአንተው ሕልው ሆኖ አለ፡፡ ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ፣ አንተን ግን በማን ስም አጠምቃለሁ? አለው፡፡ ጌታም ዮሐንስን እንዲህ እያልክ አጥምቀኝ አለው፡- እንደ መልከጼዴቅ ሹመት የዓለሙ ካህን፣ ብርሃንን የምትገልጽ፣ የአብ የባሕርይ ልጅ፣ አቤቱ ይቅር በለን፣ የዓለምን ኃጢአት የምታስወግደው የእግዚአብሔር በግ ይቅር በለን እያልክ አጥምቀኝ አለው፡፡ ያንጊዜ ዮሐንስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ጥር ዐሥራ አንድ ቀን ከሌሊቱ በአሥር ሰዓት አጠመቀው፡፡››


ከበዓሉ ረድኤት ይክፈለን!


(ምንጭ፡- ሚጣቅ አማኑኤል ያሳተመው የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ ገድል)


እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሰን!


LIKE OUR PAGE

https://www.facebook.com/tewadhdohaimanotachin




https://www.youtube.com/watch?v=3fnWuuHj5ZM