Showing posts with label ተዋሕዶ ያለ ጥርጥር ታላቅ ምስጢር. Show all posts
Showing posts with label ተዋሕዶ ያለ ጥርጥር ታላቅ ምስጢር. Show all posts

Wednesday, January 30, 2019

ጥር 22-ወበዛቲ ዕለት

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 


ጥር 22-ዓለሙ ሁሉ የእግራቸውን ትቢያ ያህል እንኳን ዋጋ የሌለው የመነኮሳት ሁሉ አባት በገዳም ለሚኖሩ ቅዱሳን እንደ ኮከብ የሚያበሩላቸው ገድል ትሩፋታቸው በቃል ተነግሮ የማያልቅ እጅግ የከበሩ ርዕሰ መነኮሳት አቡነ እንጦንስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል በዓለ ሲመቱ ነው፡፡
ርዕሰ መነኮሳት አቡነ እንጦንስ፡- እንጦንስ አበ መነኮሳት በሌላኛው ስማቸው ‹‹የበረሃው ኮከብ›› እየተባሉም ይጠራሉ፡፡ ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ አቡነ እንጦንስ ገና በ7 ዓመታቸው ነው የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ተምረው አጠናቀው የጨረሱት፡፡ መልካም ትሩፋታቸውንና ታዛዥነታቸውን የልጅ አዋቂ መሆናቸውም በሁሉ ዘንድ በተሰማ ጊዜ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አባ ቲዎናስም የእንጦንስን የልጅነት ጸጋና ዕውቀት ተሩፋታቸውን ሰምተው መልእክተኞችን ልከው አስመጧቸው፡፡ ካስመጧቸውም በኋላ ዲቁና ሲሾሟቸው ‹‹ይህ ሕፃን በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናል፣ ዜናውም በዓለሙ ሁሉ ይዳረሳል›› በማለት ትንቢት ተናግረውላቸዋል፡፡ እንጦንዮስ (እንጦንስ) ግብፃዊ ወላጆቻቸው እጅግ ባለጸጎችና ደጋግ ነበሩ፡፡ ወላጆቻቸው ከሞቱ በኋላ አባ እንጦንስ የወላጆቻቸውን ሀብት ወርሰው ከአንዲት እኅታቸው ጋር መኖር ጀመሩ፡፡
አንድ ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው ወንጌል ሲነበብ ጌታችን ስለሀብታሙ ሰው የተናገረውን ምዕራፍ ሲነበብ አዳመጡ፡፡ ‹‹ልትጸድቅ ብትወድድ ሂደህ ያለህን ሁሉ ሽጥና ለድኆች ስጥ፤ መጥተህም ተከተለኝ በሰማያት መዝገብ ታከማቻለህ›› (ማቴ 19፡21) የሚለውን የጌታችንን ቃል በሰሙ ጊዜ ‹‹ይህ ስለእኔ የተነገረ ቃል ነው›› በማለት ከቤተ ክርስቲያን ወጥተው ወደ ቤታቸው በመሄድ ወላጆቻቸው ሲሞቱ ያወረሷቸውን ብዙ ንብረታቸውን በሙሉ ሸጠው መጸወቱ፡፡ የወረሱትንም 300 ሄክታር ወይም 12 ጋሻ መሬት ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች አከፋፈሉ፡፡ የቀረቻቸውን እኅታቸውንም ወስደው ሴቶች ገዳም አስገቧትና እሳቸውም ከመንደር ወጣ ብለው በመኖሪያ ቤታቸው አጠገብ በብሕትውና ሕይወት ብቻቸውን መኖር ጀመሩ፡፡
እንጦንስ አበ መነኮሳት በአንድ መቃብር ቤት ገብተው ኖሩ፡፡ ሰይጣናትም መጥተው ደብድበው ከመንገድ ላይ ጥለዋቸው ሄዱ፡፡ ከወደቁበት አንስተው ወደ ቤተ ክርስቲያን ወሰዷቸውና ጌታችን ፈወሳቸው፡፡ ተጋድሎአቸውንም እንደገና ጀመሩ፡፡ አሁንም ሰይጣናት በዱር አውሬዎች በአንበሳ፣ በተኩላ፣ በእባብና በጊንጥ እንተመሰሉ እየመጡ ይዋጓቸው ነበር፡፡ በዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ ምግባቸውን ያበስላሉ፡፡ ወደ በዓታቸውም ሰውን አያስገቡም ነበር-በውጭ ሆነው ያነጋግሯቸዋል አንጂ፡፡ እንዲህም ሆነው 20 ዓመት ተቀመጡ፡፡ ጌታችንም ተገልጦላቸው ወጥተው እንዲያስተምሩ አዘዛቸውና ወጥተው ደቀ መዛሙርትን ማፍራት ጀመሩ፡፡ የመከራ ዘመን በመጣ ሰዓት ሰማዕትነትን ለመቀበል ወደ እስክንድርያ ጎዳናዎች ወጥተው ታዩ፡፡ መኰንኑም እንዳይታዩ ብሎ መከራቸው ግን እሽ አላሉትም፡፡ ሰማዕትነት የእሳቸው ክፍል አልነበረምና ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ከተገደለ በኋላ በመልአኩ ትእዛዝ ወደ በዓታቸው ተመለሱ፡፡ ከዐረብ ነጋዴዎች ጋር ወደ ሩቅ ቦታ ሄደው በበረሃ ብቻውን መኖር ጀመሩ፡፡
አባ እንጦንስ በረሃ ለበረሃ ሲንከራተቱ አጋንንት ክፉኛ ይዋጓቸው ነበር፡፡ በረሃነቱም ጽኑ ነው፣ ከሐሩሩ ጽናት የተነሣ በቀትር ጊዜ ከደንጊያ ላይ ተልባ ቢያሰጡ ይቆላል፡፡ እርሳቸውም ከዚያ ሄደው ሲጋደሉ አጋንንት ጾር በማንሳት ግማሾቹ ‹‹ከዚህ በረሃ እንደምን ደፍረህ መጣህ?›› ሲሏቸው ሌሎቹ ደግሞ ተቀብለው ‹‹አዳም ከወጣበት ገነት እገባ ብሎ ነው…›› እያሉ ይዘብቱባቸው ነበር፡፡ አባ እንጦንስ ግን በፍጹም ትሕትና ይታገሷቸዋል፡፡ ‹‹መሆንማ ይሆን ብላችሁ ነውን? እናንተ ብዙ እኔ አንድ ብቻዬን፤ እናንተ ረቂቃን እኔ ግዙፍ፡፡ እናንተ ኀያላን እኔ ደካማ በኀይለ ክርስቶስ ብችላችሁ ነው እንጂ ያለዚያስ አልችላችሁም›› እያሉ በትሕትና ሲዋጓቸው ኖሩ፡፡ ከዕለታት ባንድ ቀን ‹‹ይኸን የአጋንንት ጾር አልቻልሁትም ልሂድ እንጂ›› ብለው ሲያስቡ አደሩ፡፡ በማለዳም ተነሥተው በትራቸውን ይዘው ከደጃፋቸው ላይ ቆሙ፡፡ እንዳይቀሩም ጾሩ ትዝ እያላቸው እንዳይሄዱም በዓታቸው እየናፈቃቸው አንድ እግራቸውን ከውስጥ፤ አንድ እግራቸውን ከአፍአ አድርገው ሲያወጡ ሲያወርዱ መልአኩ የሰሌን ቆብ ደፍቶ፤ የሰሌን መቋረፊያ ለብሶ፤ የሰሌን መታጠቂያ ታጥቆ ብትን ሰሌን ይዞ መጣ፡፡ ምን ሊያደርግ ይሆን? ሲሉም ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ ቆመ፡፡ ወዲያው ጸሎተ ወንጌልን፤ ነአኲቶን፤ ተሰሃለኒን፤ ደግሞ መጀመሪያ ለሥላሴ እጅ ነሳ፡፡ ከዚያ በኋላ አንድ አቡነ ዘበሰማያት ሰላሳ ስድስት ሰጊድ አድርሶ በመጨረሻ አንድ ጊዜ እጅ ነሥቶ ተቀመጠ፡፡ ወዲያው ያን ብትን ሰሌን አቅርቦ ይታታ ጀመር፡፡ ‹‹እንጦንስም እንግዲህማ የዚህን ፍጻሜ ሳላይ እንዴት እሄዳለሁ?›› ብለው ተቀምጠው ይመለከቱት ጀመር፡፡ ሰለስት ሲሆን ደግሞ ተነሥቶ አቡነ ዘበሰማያቱንም ሰጊዱንም ያንኑ ያህል አደረሰው፡፡ የቀሩትንም የሰዓቱንም የሠርኩንም እንደዚሁ አድርጎ አሳያቸው፡፡ ‹‹እንጦኒ ሆይ እንደዚህ ሥራ፤ ይህንን ከሠራህ ከአጋንንት ጠብ ትድናለህ›› አላቸው፡፡ እርሳቸውም የአጋንንትን ጦር መከላከያውን ሁሉ መልአኩ ባሳያቸው መሠረት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እንዲሁ የሚሠሩ ሆኑ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ስንፍናና የሰይጣን ውጊያ ወደሳቸው አልመጣም፡፡
ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም ከአባ እንጦንስ ይባረክ ዘንድ ብዙ ጊዜ ደብዳቤ ጻፈላቸው፡፡ እርሳቸውም ቸል ባሉት ጊዜ ልጆቻቸው ደግ ንጉሥ መሆኑን ስለነገሯቸውና ስለለመኗቸው አባ እንጦንስ ጽፈው በደብዳቤ ባርከውታል፡፡ የአፍርንጊያው ንጉሥም መጥተው እርሱንና ሠራዊቱን ሁሉ እንዲባርኳቸው በክርስቶስ መከራዎች አማጽኖ ደብዳቤ ጻፈላቸው፡፡ ጌታችንንም በጸሎት ሲጠይቁ ደመና መጥታ ወስዳ አደረሰቻቸውና ንጉሡንና ሕዝቡን ሁሉ ባርከዋቸዋል፡፡
አባታችን ሠላሳ ዓመት በሞላቸው ጊዜ ጌታችን በዕለተ ዓርብ የለበሰውን ልብስ አልብሷቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አባ እንጦንስ የአክሊለ ሦክ ምሳሌ የሆነውን ቆብን፤ የከለሜዳ ምሳሌ የሆነውን ቀሚስ፤ የሀብል ምሳሌ የሆነውን ቅናትን፤ እንዲሁም ሥጋ ማርያምን ከመልአክ ከተቀበሉ በኋላ ‹‹በዚህ ዓለም እኔ ብቻ ነኝን ወይስ ሌላም አለ?›› ብለው በጸሎት ወደ እግዚአብሔር አመለከቱ፡፡ ጌታችንም ‹‹አለ እንጂ፣ አንድ ጊዜ ተራምዶ ሁለተኛውን ሳይደግም የሚሠራውን ሥራ ዓለሙ ሁሉ ቢሰበሰብ የማይሠራው፣ በጸሎቱ ዝናም የሚያዘንም፣ ፀሐይን የሚያወጣ፤ እንደዚህ ያለ ወዳጅ አለኝ›› አላቸው፡፡ አባታችንም ‹‹ይኽን ሰው ለማየት ልሂድን ልቅር? ቢሉት እንዲሄዱ ፈቀደላቸው፡፡
የታዘዘ መልአክም እየመራ አባ ጳውሊ ካሉበት በዓት አደረሳቸው፡፡ እርሳቸውም ከአባ ጳውሊ ጋር ብዙ መንፈሳዊውን ነገር ተጨዋወቱ፡፡ ተጨዋውተውም ሲያበቁ አባ ጳውሊ ለአባ እንጦንስ ለብቻቸው በዓት ሰጧቸው፡፡ እንጦንዮስም ከዚያ ሆነው ጸሎታቸውን ሲያደርግ ዋሉ፡፡ ወትሮ ለአባ ጳውሊ ግማሽ ሰማያዊ ኅብስት ይወርድላቸው የነበረ ሲሆን ማታ ግን አንድ ሙሉ ኅብስት ወረደላቸው፡፡ አባ ጳውሊም በፈቃደ እግዚአብሔር ወደ እርሳቸው መምጣታቸውን ያን ጊዜ ዐወቁ፡፡ ወዲያው ያን ኅብስት ከሁለት ከፍለው እኩሌታውን ለራሳቸው አስቀርተው እኩሌታውን ለአባ እንጦንስ ሰጧቸው፡፡ ያን ተመግበው ሌሊት ሁለቱም በየሥራቸው ክብራቸው ተገልጾ ሲተያዩ አድረዋል፡፡ ጳውሊ ዓሥር ጣቶቹን እንደ ፋና ሆነው እያበሩለት አራቱን ወንጌል ሲያደርስ እንጦንዮስም እንደ ዓምደ ብርሃን ተተክለው ሲያበሩ ተያይተዋል፡፡ በዚያች ሌሊት ከዚያ ቦታ ጨለማ ጠፍቶ አድሯል፡፡
በነጋው ሠለስት እላፊ ሲሆን ጸሎታቸውን አድርሰው ሲያበቁ ተገናኝተው ሲጨዋወቱ ጳውሊ እንጦንዮስ ያረጉትን ቆብ አይተው ‹‹ይህ ከማን አገኘኸው?›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ‹‹እርሱ ባለቤቱ ሰጠኝ›› አሉ፡፡ ጳውሊም የጌታችንን ቸርነት ያደንቁ ጀመር፡፡ እንጦንዮስም ‹‹እስኪ በኔ ብቻ የሚቀር እንደሆነ ለሌላም የሚያልፍ እንደሆነ አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ሲያመለክቱ ወዲያው ተገለጸላቸውና ደስ አላቸው፡፡ ‹‹ምን አየህ?›› ቢሏቸው ‹‹ነጫጭ ርግቦች በጠፈር መልተው አንተ እየመራሃቸው ተከትለውህ ሲሄዱ አየሁ›› አሏቸው፡፡ ‹‹ይህስ ምንድን ነው?›› ቢሏቸው ‹‹እሊህማ በዚህ በቆቡ የምትወልዳቸው ንጹሐን ጻድቃን ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ ‹‹ሁለተኛ አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ካመለክቱ በኋላ አዝነውና ተከፍተው ተመለከቷቸው፡፡ ‹‹ምነው?›› ቢሏቸው ‹‹በክንፋቸው ጥቁር ተቀላቅሎባቸው አየሁ›› አሉ፡፡ ‹‹ምንድን ናቸው?›› ቢሏቸው ‹‹ጽድቅና ኀጢአት እየቀላቀሉ የሚሠሩ ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ካዘኑ በኋላ ‹‹ሦስተኛም አመልክትልኝ›› አሏቸው፡፡ አባ ጳውሊም ለሦስተኛ ጊዜ ካመለከቱ በኋላ በድንጋጤ ቃላቸውን ከፍ አድርገው ጮኹ፡፡ አባ እንጦንስም ‹‹ምነው?›› ቢሏቸው አባ ጳውሊ እንዲህ አሉ፡- ‹‹ነገር ግን በመጨረሻ ዘመን የሚነሡቱ እንደ ቁራ ጠቁረው አየሁዋቸው›› አሉ፡፡ ‹‹ምንድን ናቸው?›› ቢሏቸው ‹‹ሀሳሲያነ ሢመት (ሹመት ፈላጊዎች)፣ መፍቀሪያነ ንዋይ (ገንዘብ የሚወዱ) እና ከመኳንንትም ጋር በጥዋት ማዕድ የሚቀመጡ በፍጻሜ ዘመን የሚነሡ ኀጥአን ልጆችህ ናቸው›› አሏቸው፡፡ ይህን ጊዜ አባ እንጦንስ ‹‹ያለ ንስሓ ባይጠራቸው እስኪ አመልክትልኝ›› አሉ፡፡ አባ ጳውሊም አመለከቱ ነገር ግን የዚህ ምላሽ አልመጣላቸውም፡፡
ከዚህ በኋላ አባ ጳውሊ ስለ ቆቡ አባ እንጦንስን ‹‹እንግዲህ ይህን ከራስህ ያደረግኸውን ለኔ ስጠኝ ላንተ ሌላ ሠርተህ አድርግ›› አሏቸው፡፡ አባ እንጦንስም ‹‹ይህንንስ እንዳልሰጥህ ከባለቤቱ ተቀብዬዋለሁ፡፡ ነገር ግን ሥራውን ለምጄዋለሁ ሌላ ሠርቼ ላምጣልህ›› አሏቸው፡፡ ጳውሊም ‹‹እንግዲያስ አትዘግይ ቶሎ ሠርተህ አምጣልኝ›› አሏቸው፡፡ እንጦንስም ሠርተው ይዘው ሲመጡ ጳውሊ ዐርፈው ነፍሳቸውን መላእክተ ብርሃን ይዘዋት ሲያርጉ ተመለከቱ፡፡ መላእክቱም ‹‹ጳውሊ ዐርፏልና ሂደህ ቅበረው›› አሏቸው፡፡ ‹‹ይህንሳ የያዝኩትን ቆብ ልተወውን?›› ቢሏቸው፡፡ ‹‹አትተው አድርግለት›› ብለው መለሱላቸው፡፡ ይህም በምንኩስና የሠሩት ሥራ ከንቱ እንዳይደለ ለማጠየቅ ነው፡፡ አባ እንጦንስም ቢሄዱ አባ ጳውሊ መጽሐፋቸውን ታቅፈው፣ አጽፋቸውን ተጎናጽፈው፣ ከበዓታቸው ዐርፈው አገኟቸው፡፡ ከራስጌአቸው ቆመው ሲያለቅሱ ሁለት አንበሶች መጡ፡፡ ‹‹የመቃብሩን ነገር እንደምን ላድርግ?›› እያሉ ሲጨነቁ አንበሶቹ በእጃቸው እንደመጥቀስ አድርገው የመቃብራቸውን ቦታ አሳዩአቸው፡፡ እርሳቸውም ለክተው ሰጧቸው፡፡ አንበሶቹም ከቆፈሩላቸው በኋላ አባ ጳውሊን ቀብረው ‹‹እንግዲህ ከዚህ እኖራለሁ›› ብለው አሰቡ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ‹‹በዚህ መኖር አይሆንልህም ሂድ›› አላቸው፡፡ አጽፋቸውንና መጽሐፋቸውን ይዘው ሄደው እስክንድርያ ደርሰው ለሊቀ ጳጳሱ ለቅዱስ አትናቴዎስ ያዩትንና የሆነውን ሁሉ ነገሯቸው፡፡ አቡነ አትናቴዎስም ‹‹ልሄድና ከዚያ ልኑር?›› ሲሏቸው ‹‹አይሆንልህም አትሂድ እኔም አስቤ ነበር ነገር ግን የማይሆንልኝ ሆኖ መጣሁ እንጂ›› አሏቸው፡፡ ‹‹ባይሆን ለበረከት ያህል አጽፊቱን ጥለህልኝ ሂድ›› ብለው ሲለምኗቸው ትተውላቸው ሄዱ፡፡
አባ እንጦንስ ራሳቸውን ዝቅ በማድረግና በፍጹም ትሕትናቸው ይታወቃሉ፡፡ ምንም እንኳ ታላቅና በትሩፋት የበለጸጉ ቢሆኑም በጳጳሳትና በካህናት ፊት ራሳቸውን በትሕትና ዝቅ አድርገው እጅ ይነሷቸው ነበር፡፡ ዲያቆንም ቢሆን ወደ እርሳቸው በመጣ ጊዜ ከእርሱ ጠቃሚ ነጥብን ለማግኘት ይሞክራሉ፤ ላገኙትም ዕውቀት ሳያመሰግኑ አያልፉም፡፡ የእርሳቸውንም ምክር ሽተው ለሚመጡ ሁሉ እጅግ ጠቃሚ የሕይወት ምክሮችን ይሰጣሉ፡፡ ዓለምን ንቆ ገንዘብ ስለመውደድ ከመነኮሰ በኋላ ለድሆች አከፋፍሎ ለራሱም ጥቂት ንብረት ያስቀረ አንድ ወንድም ወደ አባ እንጦንስ መጣ፡፡ አባ እንጦንስም ይህን ካወቁ በኋላ እንዲህ አሉት፡- ‹‹መነኩሴ ለመሆን ከፈለግህ ወደ መንደር ሂድና ጥቂት ሥጋ ገዝተህ ራቁትህን በሰውነትህ ላይ ተሸክመህ ተመለስና ወደእኔ ና›› አሉት፡፡ ያም ወንድም ይህን ባደረገ ጊዜ ወፎችና ውሾች በሰውነቱ ያለውን ሥጋ ለመብላት ሲሉ በሰውነቱ ላይ በማንዣበብ እየሞነጨሩ አቆሰሉት፡፡ በደረሰም ጊዜ አባ እንጦንስ እንዳዘዙት ማድረጉን ጠየቁት፡፡ እርሱም የቆሰለውን ሰውነቱን ባሳያቸው ጊዜ እንጦንስ ‹‹ዓለምን ከናቁ በኋላ ገንዘብ የሚመኙትም እንደዚሁ በአጋንንት ይገደላሉ›› አሉት፡፡
አቡነ እንጦንስ ዕረፍታቸው በደረሰ ጊዜ ዕለተ ሞታቸውን ዐውቀው ደቀ መዛሙርቶቻቸውን ሲሰናበቱ እንዲህ ብለው መከሯቸው፡- ‹‹ይህ ከእናንተ ጋር የማደርገው የመጨረሻው ግንኙነት ነው፡፡ በዚህም ሕይወት ዳግመኛ እንዳንተያይ ዐውቃለሁ፡፡ አሁን እኔ የምሞትበት ጊዜ ነው፡፡ ከጥረታችሁ ግዴለሽ አትሁኑ፡፡ በብሕትውና ሕይወት ፍጹም ተስፋ አትቁረጡ፡፡ ዕለት ዕለት እንደምትሞቱ ሆናችሁ ኑሩ፡፡ አስቀድሜ እንደተናገርኩት ነፍስን ከርኩስ አሳቦች ለመጠበቅ በሥራ ትጉ፡፡ ቅዱሳንን ምሰሉ፡፡ ቅድስና የሌለውን የስንፍና ትምህርታቸውን ታውቃላችሁና ወደ መናፍቃን አትቅረቡ፣ ኑፋቄያቸው ለማንም ግልጽ ነውና፡፡››
ከዚህም በኋላ ጊዜ ዕረፍታቸው ሲደርስ ጌታችን ተገልጦላቸው ቃልኪዳን ገባላቸው፡፡ እርሳቸውም ለልጃቸው ለመቃርስ ስለ ወደፊቱ መነኮሳትና ገዳማት ትንቢትን ነገሩት፡፡ ወደፊት መነኮሳት ከበዓታቸው እየወጡ በዓለም እንደሚቅበዘበዙ ተናገሩ፡፡ ዕረፍታቸው በደረሰ ጊዜ በትራቸውን ለልጃቸው ለመቃርስ፣ ምንጣፋቸውን ለአቡነ አትናቴዎስ፣ የፍየል ሌጦ አጽፋቸውን ልጃቸው ለሊቀጳጳሱ ለሰራብዮን እንዲሰጡ አዘዙና በ120 ዓመታቸው በ356 ዓ.ም ጥር 22 በታላቅ ክብር ዐረፉ፡፡
ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን አሜን!
+ + + 


ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል፡- ኢዮር፣ ራማ እና ኤረር የተባሉ ሦስት የመላእክት ከተሞች አሉ፡፡ እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክት ከፈጠራቸው በኋላ በነገድ 100 በአለቃ 10 አድርጎ በሦስቱ ሰማያት አስፍሯቸዋል፡፡ ኢዮርን በ4፣ ራማን በ3፣ ኤረርንም በ3 ከፍሎ ነው በዓሥሩ ከተማ ያሰፈራቸው፡፡
በዚህም መሠረት ኢዮርን ላይና ታች አድርጎ በ4 ከተማ ከፍሏታል፡፡ በእርሷ ያሉትን መላእክትን በ40 ነገድ 4 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያው ነገድ ‹‹አጋእዝት›› ይባላሉ፡፡ አለቃቸው ሣጥናኤል ነበር፤ እርሱም የመላእክትን ሁሉ ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ያሳርግ ነበር፡፡ ከክብሩ ሲዋረድ ቅዱስ ሚካኤል በምትኩ ተሹሞበታል፡፡ ሁለተኛው ነገድ ‹‹ኪሩቤል›› ይባላሉ፡፡ እነርሱም መንበረ ሥላሴን ይሸከማሉ፡፡ የቀሳውስት አምሳል ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ሰብና ገጸ አንበስ ናቸው፡፡ በሦስተኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ሱራፌል ይባላሉ፡፡ የዲያቆናት አምሳል ናቸው፡፡ በትንቢተ ኢሳያስ በምዕራፍ 6 ላይ የተገለጹትና ኢሳያስን ከለምጹ እንዲፈወስ ያደረጉት ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ላህምና ገጸ ንስር ናቸው፡፡ (በነገራችን ላይ ‹‹ከሩቤል›› ወይም ‹‹ሱራፌል›› የሚባሉ የግለሰብ መጠሪያ ስሞች ስህተት ናቸው፡፡ አንደኛ እነዚህ ስሞች የብዙ መላእክት መጠሪያን የሚወክሉ ናቸው፡፡ ለአንዱ ሲሆን ‹‹ኪሩብ፣ ሱራፊ›› ይባላል፡፡ ‹ኪሩቤል› ወይም ‹ሱራፌል› ማለት ግን የብዙ ቁጥራቸው መጠሪያ ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የቅዱሳን መላእክትን ስም እንዳለ በቁሙ ወስዶ ለግል መጠሪያ ስም ማዋል ተገቢ አይደለም፡፡ ‹‹ወለተ ሚካኤ፣ ክብፈ ገብርኤል….›› እየተባሉ ይሰየማሉ እንጂ ቀጥታ ‹ሚካኤል›፣ ‹ገብርኤል› እያሉ ሰዎችን መሰየም ስህተት ነው፡፡ 4ኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ኃይላት ይባላሉ፡፡ የእሳት ሰይፍ ይዘው በሥሉስ ቅዱስ ፊት የሚቆሙ ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት የዛሉና የደከሙ ክርስቲያኖችን የሚያበረታቱ ናቸው፡፡ አለቃቸውም ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡)
ዳግመኛም እግዚአብሔር በራማ ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹አርባብ›› ይባላሉ፡፡ የሥላሴ እልፍኝ አስከልካዮች ናቸው፡፡ የእግዚአብሔርን መንበር በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ ሁለተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹መናብርት›› ይባላሉ፡፡ ለእግዚአብሔርን እጅግ ቅርብ የሆኑ ናቸው፡፡ የመብረቅ ጋሻቸውን የእሳት ጦራቸውን ይዘው የሥላሴ ጋሻ ጃግሬዎች ሆነው በተጠንቀቅ ይቆማሉ፡፡ የሰውን ችግር ለእግዚአብሔር ያቀርባሉ፡፡ መዝ 88፡6፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሦስተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹ሥልጣናት›› ይባላሉ፡፡ መላውን ፍጥረት ለመጠበቅ ሥልጣን የተሰጣቸውና የምጽአት ዕለት አዋጅ ነጋሪዎች ናቸው፡፡ ዳን 12፡1፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሱርያል ነው፡፡
ዳግመኛም እግዚአብሔር በኤረር ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹መኳንንት›› ይባላሉ፡፡ የስላሴ የእሳት ባለ ቀስት ናቸው፡፡ የሰው ልጅ ልዩ ጠባቂዎች ናቸው፤ በተለይ በአደጋ ጊዜ ሎጥን እንዳዳኑት ፈጥነው ይደርሳሉ፡፡ በዕለተ ምጽዓት የሰውን ሁሉ ዐፅም ሰብስበው ለትንሣኤ ዘጉባኤ ያበቃሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሰዳካኤል ነው፡፡ ሁለተኛዎቹ ‹‹ሊቃናት›› ይላሉ፡፡ የሥላሴ የእሳት ፈረሶች ናቸው፡፡ በእሳት ፈረስ ይመላለሳሉ፡፡ እነዚህም 24ቱ ካህናተ ሰማይ ሲሆኑ አለቃቸው ቅዱስ ሰላታኤል ነው፡፡ በኤረር ከተማ የሰፈሩት ሦስተኛዎቹ ‹‹መላእክት›› ይባላሉ፡፡ ፍጥረትን ሁሉ የሚጠብቁ ናቸው፡፡ አለቃቸው ቅዱስ አናንኤል ነው፡፡ በእነዚህ የማይጠበቅ ፍጥረት የለም፡፡ ከአዝርእት ጀምሮ ሁሉን ይጠብቃሉ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙ 7 መላእክትን አየሁ›› (ራዕ 8፡2) እንዳለ ሊቃነ መላእክት በቁጥር 7 ናቸው፡፡ እነርሱም፡- ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል፣ ቅዱስ ራጉኤል፣ ቅዱስ ዑራኤል፣ ቅዱስ ፋኑኤል እና ቅዱስ አፍኒን ናቸው፡፡
‹‹ዑራኤል›› የሚለው ስም ‹ዑር› እና ‹ኤል› ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል›› ማለት ትርጉሙ ‹‹የብርሃን ጌታ፣ የአምላክ ብርሃን›› ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዑራኤል ከ7ቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነው፡፡ በመሆኑም መጽሐፈ ሄኖክ እንደሚገልጸው መባርቅት ለጥጋብና ለበረከት እንዲበርቁ ነጎድጓድም ለሰላም እንዲሆን ያሰማራል፡፡ ምሥጢረ ሰማይንና ሰማያዊውን ዕውቀት ሁሉ ለሄኖክ የገለጸለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ የፀሐይን፣ የጨረቃን፣ የከዋክብትንና የሰማይ ሠራዊትን ብርሃንን የሚመራው ይኸው ገናና መልአክ ነው፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ 28፡13፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሆኖ በተሰቀለ ጊዜ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨው ይኸው ገናና መልአክ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ዕውቀት ተሠውሮበት ለነበረው ለኢትዮጵያዊው ሊቅ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም በእመቤታችን ትእዛዝ ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል የተባለ መልአክ ሊረዳኝ መጣ፡፡›› መጽሐፈ ዕዝራ 2፡1፡፡ አምላካችን እግዚአብሔር የሕይወትና የይቅርታ ዝናም በምድራችን ላይ ያዘንብ ዘንድ እንዲሁም የእርሻችንን አዝመራ በዝናም አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ለምግብነት እንዲበቃ ከፈጣሪ ዘንድ ምሕረትን የሚለምን መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ሊቁ አባ ጊዮርጊስም በመልአኩ አማላጂነት እጅግ ብዙ ድርሰቶችን የደረሱት መልአኩ ጽዋ ሕይወትን ካጠጣቸው በኋላ ነው፡፡ በመጀመሪያም አባ ጊዮርጊስ የተወለዱት በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት ነው፡፡ በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ የተመሠረቱ አብዛኞቹ ቅዱሳት ገዳማት በቅዱስ ዑራኤል መሪነት ነው፡፡ ድርሳኑ ላይ የማይጠቅሳቸው የሀገራችን የከበሩ ቅዱሳት ገዳማትና ቅዱሳን ነገሥታት የሉም፡፡
የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክን ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ስትሰደድ መንገድ እየመራ ወደ ግብጽ እና ወደ አገራችንን ኢትዮጵያ ያመጣቸው ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ እመቤታችንን ከተወደደ ልጇ ጋር በደመና ጭኖ መላ ኢትዮጵያን ካስጎበኛት በኋላ ቅድስት አገራችንን ለእመቤታችን የዓሥራት አገር እንድትሆን ያደረገው መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል በዓመት 3 ዓበይት በዓላት አሉት፡፡ ጥር 22 በዓለ ሲመቱ ነው፡፡ መጋቢት 27 የጌታችንን ክቡር የሆነ ወርቀ ደሙን ለዓለም የረጨበት ነው፡፡ ሐምሌ 22 ቀን ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበትና ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል የዕውቀትን ጽዋ ያጠጣበት ዕለት ነው፡፡
የሊቀ መላእክት የቅዱስ ዑራኤል ጥበቃው አይለየን! በጸሎቱ ይማረን !

Wednesday, January 23, 2019

ጥር 15 - ወበዛቲ ዕለት

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈሰ ቅዱስ ስም አሜን
 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it) 
ጥር 15-በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ የከበረች ወንጌልን ሰብኮ ጣዖት አምላኪዎችን በተአምራቱ ያሳመነውና ብዙ አሰቃቂ መከራዎችን የተቀበለው ሕፃኑ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ማኅበርተኞቹ የሆኑ ዓሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎችም አብረው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ 
+ በግራኝ ዘመን ከአንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር በእሳት ተቃጥሎ በሰማዕትነት ያረፈው አቡነ ቄርሎስ ዕረፍቱ ነው፡፡
+ የሶርያ ክርስቲያኖች በዚህች ዕለት በዓሉን በድምቀት የሚያከብሩለት የኑሲሱ አቡነ ጎርጎሪዮስ መታሰቢያ በዓሉ ነው፡፡ 
+ ነቢዩ ቅዱስ አብድዩ ዕረፍቱ ነው፡፡
አቡነ ቄርሎስ ኢትዮጵያዊ፡- አባታቸው ሳይንቱ እናታቸው ወለቃት ሲባሉ የመጀመሪያ ስማቸው መብዓ ሥላሴ ነው፡፡ በባሕታዊነታቸው መላ ገዳማቱ ሁሉ ያደንቋቸው የነበሩ ሲሆን እንደ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ 60 አንበሶችና 60 ነብሮች የተሰጣቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ጻድቁ በክፉው ግራኝ ዘመን ከአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጋር አብረው ተቃጥለው ነው በሰማዕትነት ያረፉት፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!


+++
ነቢዩ ቅዱስ አብድዩ፡- የስሙ ትርጓሜ ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋይ›› ማለት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ 1ኛ ነገ 18፡3 ላይ ‹‹አብደዩ እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር›› ተብሎ የተነገረለት እውነትም ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋይ›› የሆነ የነቢዩ ኤልያስ ደቀመዝሙር የነበረ ታላቅ ነቢይ ነው፡፡ ይህም ቅዱስ ነቢይ ከጠረፍ በረሃ አቅራቢያ ካለች ሱሳም በምትባል አገር ካሉ ሰዎች ወገን ነው፡፡ አባቱ ሐናንያ ይባላል፡፡ ለነቢዩ ኤልያስ ደቀ መዝሙሩ ሆኖ በንጉሡ በአክዓብምና በንግሥቲቱ በኤልዛቤል ምክንያት በእርሱ ላይ የመጣውን መከራ ሁሉ ታግሷል፡፡ ታላቁ ነቢይ ኤልያስ ከእነ ኤልዛቤል ሸሽቶ ወደ ተራራ ላይ ወጥቶ በዋሻ ተሸሽጎ ምግቡን አሞራ እያመጣለት በኖረበት ጊዜ እንኳን ነቢዩ አብድዩ ግን ብቻውን የእግዚአብሔርን ነቢያት ይንከባከብ ነበር፡፡ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥ የነበረ ቢሆንም ንግሥት ኤልዛቤል የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ አብድዩ መቶውን ነቢያት ወስዶ ሃምሳ ሃምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው የነበረ ታላቅ ባለውለታ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ታሪኩ እንዲህ ተብሎ ነው የተጻፈው፡-
‹‹ከብዙ ቀንም በኋላ በሦስተኛው ዓመት ‹‹ሂድ ለአክዓብ ተገለጥ፥ በምድር ላይም ዝናብ እሰጣለሁ›› የሚል የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኤልያስ መጣ፡፡ ኤልያስም ለአክዓብ ይገለጥ ዘንድ ሄደ፤ በሰማርያም ራብ ጸንቶ ነበር፡፡ አክዓብም የቤቱን አዛዥ አብድዩን ጠራ፤ አብድዩ እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤልም የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ እርሱ መቶውን ነቢያት ወስዶ አምሳ አምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው ነበር፡፡ አክዓብም አብድዩን ‹‹በአገሩ መካከል ወደ ውኃው ምንጭ ሁሉና ወደ ወንዝ ሁሉ ሂድ፤ እንስሶችም ሁሉ እንዳይጠፉ ፈረሶችንና በቅሎችን የምናድንበት ሣር ምናልባት እናገኛለን›› አለው፡፡ ሁለቱም የሚመለሱበትን አገር ተካፈሉ፤ አክዓብም ለብቻው በአንድ መንገድ አብድዩም ለብቻው በሌላ መንገድ ሄዱ፡፡
አብድዩም በመንገድ ሲሄድ እነሆ ኤልያስ ተገናኘው፤ አብድዩም አወቀው፣ በግምባሩም ተደፍቶ ‹‹ጌታዬ ሆይ! ኤልያስ አንተ ነህን? አለ፡፡ ኤልያስም ‹‹እኔ ነኝ ሄደህ ለጌታህ ‹ኤልያስ ተገኝቶአል› በል›› አለው፡፡ አብድዩም ‹‹እኔን ባሪያህን እንዲገድል በአክዓብ እጅ አሳልፈህ ትሰጠኝ ዘንድ ምን ኃጢአት አድርጌአለሁ? አምላክህ ሕያው እግዚአብሔርን! ጌታዬ ይፈልግህ ዘንድ ያልላከበት ሕዝብ ወይም መንግሥት የለም፤ ሁሉም ‹‹በዚህ የለም›› ባሉ ጊዜ አንተን እንዳላገኙ መንግሥቱንና ሕዝቡን አምሎአቸው ነበር፡፡ አሁንም እነሆ ‹ሂድ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር› ትለኛለህ፡፡ እኔም ከአንተ ጥቂት ራቅ ስል የእግዚአብሔር መንፈስ አንሥቶ ወደማላውቀው ስፍራ ይወስድሃል፤ እኔም ገብቼ ለአክዓብ ስናገር ባያገኝህ ይገድለኛል፤ እኔም ባሪያህ ከትንሽነቴ ጀምሬ እግዚአብሔርን እፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤል የእግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ መቶውን የእግዚአብሔር ነቢያት ወስጄ አምሳ አምሳውንም በዋሻ ውስጥ ሸሽጌ እንጀራና ውኃ የመገብኋቸው ነበር፡፡ ይህ ያደርግሁት ነገር በውኑ ለጌታዬ አልታወቀህምን? አሁንም ‹ሄደህ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር ትላለህ› እርሱም ይገድለኛል›› አለው፡፡
ኤልያስም ‹‹በፊቱ የቆምሁት የሠራዊት ጌታ ሕያው እግዚአብሔርን! እኔ ዛሬ ለእርሱ እገለጣለሁ›› አለ፡፡ አብድዩም አክዓብን ሊገናኘው ሄደ፣ ነገረውም፤ አክዓብም ኤልያስን ሊገናኘው መጣ፡፡ አክዓብም ኤልያስን ባየው ጊዜ ‹‹እስራኤልን የምትገለባብጥ አንተ ነህን?›› አለው፡፡ ኤልያስም ‹‹እስራኤልን የምትገለባብጡ፣ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ትታችሁ በኣሊምን የተከተላችሁ፣ አንተና የአባትህ ቤት ናችሁ እንጂ እኔ አይደለሁም›› አለው፡፡ 1ኛ ነገ 18፡1-20፡፡
ቅዱስ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥነቱን ትቶ የኤልያስ ቀደ መዝሙሩ ሆኖ በነቢይነት እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኖረ፡፡ በንጉሥ ኢዮሳፍጥ ዘመንም ትንቢትን ተናገረ፡፡ እግዚአብሔርም ስለ ትንሣኤና ስለ ፍርድ ቀን በቃሉ ነገረው፡፡ ሁለተኛም ከእስራኤል ልጆች የሚሆነውን ከአሕዛብም ለቀሩት አጸናቸው፣ አብዝቶ መከራቸው፣ ገሠጻቸውም፡፡ የትንቢቱም ወራት ሲፈጸም በዚህች ዕለት በሰላም በፍቅር አንድነት ዐርፏል፡፡ የትንቢቱም ወራት ሃያ ዓመት ነው፡፡ ይኸውም ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በ900 ዓመት ነው፡፡
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የሶርያ ክርስቲያኖች የኑሲሱን የአቡነ ጎርጎሪዮስን የዕረፍቱን በዓል በደማቅ ሁኔታ ያከበራሉ፡፡ በእኛ አቆጣጠር ግን ዕረፍቱ ጥር 21 ቀን ነው፡፡ (የጥር ሃያ አንዱን ይመለከቷል፡፡)
+ + +
ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ፡- ሦስት ዓመት እንኳን ሳይሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ታላቅ ሰማዕትነትን የተቀበለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አባቱ ቆዝሞስ (ስምዖን) እናቱ ኢየሉጣ ይባላሉ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ በኅዳር 15 ቀን የተወለደ ሲሆን ሀገሩ በታችኛው እስያ ልዩ ስሙ ሀንጌቤን ይባላል፡፡ ዘመኑ ዘመነ ሰማዕታት ነበርና መምለኬ ጣዖት የሆነው ንጉሥ እስክንድሮስ ቅድስት ኢየሉጣን ‹‹ለጣዖቴ ስገጂ›› ብሎ አስገደዳት፡፡ እርሷም ‹‹ሕፃኑ ልጄ መጥቶ ይመስክር›› ብላ ስትናገር ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጠራና ተጠየቀ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስም ‹‹ለጣዖት አንሰግድም፣ ዘላለማዊ የሆነ የማይሻር አምላክ ስላለ ለእርሱ ነው የምንሰግደው›› ብሎ የአምላኩን ክብር በሕፃን አንደበቱ መሰከረ፡፡ ሕፃኑም ይህንን በመሰከረ ጊዜ ዕድሜው ገና ሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወሩ ነበር፡፡
ነቢዩ ቅዱስ ዳዊትም ‹‹ከልጆችና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ›› ሲል እንደተናገረ (መዝ 10፡2፣ 118፡130) መድኃኔዓለም ክርስቶስም በቅዱስ ወንጌሉ ላይ ‹‹አባት ሆይ፣ የሰማይና የምድር ጌታ ይህን ከጥበበኞችና ከአስተዋዮች ሰውረህ ለሕፃናት ስለ ገለጥህላቸው አመሰግንሃለሁ›› ያለውን ቃል በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ሕይወት ተግባራዊ ሆኖ አይተነዋል፡፡ ማቴ 11፡27፡፡ በነቢዩም ትንቢት መሠረት በበዓለ ሆሣዕና ዕለት በእናታቸው እቅፍና ጀርባ ላይ የነበሩ እምቦቀቅላ ጨቅላ ሕፃናት ‹‹ሆሣዕና፤ በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው›› በማለት ጌታችንን አመስግነውታል፡፡
እንደዚሁ ሁሉ ቅዱስ ቂርቆስም በከሃዲው ንጉሥ ፊት የጌታችንን ክብር በመሰከረ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ 40 ጋን ውኃ የሚይዝ በርሜል አስጥዶ 40 ቀን ሙሉ እሳት አስነድዶ ቅንጭብ፣ ዘይት፣ ዝፍጥና ሌላም በእጅጉ የሚጎዱ ነገሮችን በውስጡ ጨምሮ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ወደዚያ እቶኑ እሳት እንዲከቷቸው አዘዘ፡፡ ንጉሡ እስክንድሮስ ጭፍሮቹን "ሰም፣ ጨው፣ ባሩድ፣ሙጫ፣ እርሳስ፣ ብረትን፣ ቅንጭብ፣ ቁልቋል ጨምሩበት" ብሎ አዘዛቸው፡፡ ጭፍሮችም ያዘዛቸውን ከፈጸሙ በኀላ መጥተው "ያዘዝከንን ሁሉ ጨምረንበት ነዶ ፈልቷል" አሉት፡፡ "ድምፁም እንደ ነጎድጓድ ይሰማል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ያንፀባርቃል፡፡ የፍላቱም ኃይል 14 ክንድ ያህል እየዘለለ ይወጣል፡፡ በውስጡ የሚጣሉትን ሰዎች እዘዝ" አሉት፡፡ ያንጊዜም ህፃን ቂርቆስንና እናቱን ኢየሉጣን ይዘው ከእስር ቤት አወጧቸው፡፡ በክርስቶስ ስም ስላመኑ በእስር ቤት አግብተው አስረዋቸው ነበርና ፍላቱ ወደ ላይ በሚዘል በብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ሲወስዷቸው በዚያን ጊዜም እልፍ ከአንድ ሺህ አራት መቶ ሰዎች እንዲወጡና በፈላው የብረት ጋን ውስጥ የቅዱሳንን አሟሟት እንዲያዩ ሹሙ አዘዘ፡፡ ቅድስት ኢየሉጣም የፍላቱን ግርማ ባየች ጊዜ ተሸበረች፡፡ ተጠብቆላት ያለውንም ዋጋ ትታ ልትክድ ፈለገች፡፡ ቅዱስ ቂርቆስም ይህን ባወቀ ጊዜ "እናቴ ሆይ ከብረት ጋን ግርማ የተነሳ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ" እያለ ከብሉይና ከሐዲስ እየጠቀሰ እንድትጸና አስተማራት፡፡
"ነገር ግን እናቴ ሆይ አናንያንና አዘርያን፣ ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከዕቶን እሳት እንዳወጣቸው እወቂ፤ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ውስጥ ሊያድነን ይችላል፡፡ እናት ሆይ ከሚያልፈው ከዚህ ዓለም ጭንቅ ልታመልጭ በሚያልፈው በዘለዓለም እሳት ልትቀጭ ትሻለች፡፡ እናት ሆይ ይህን አትሺ፤ ይቅርብሽ አሁን እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ ሶስናን ከሀጢያተኞች እጅ ያዳናት እኛንም ከብረት ጋን ያድነናል፡፡ ዳንኤልን ከአንበሶች አፍ ያዳነ እርሱ ያድነናል፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችን ልንፈፅም ፈቅዶም እንደሆነ የኢዮብን ነፃነት (ትእግስት) ልናገኝ ይገባናል፡፡ እርሱ ልጆቹንና ሚስቱን ያገኘው ገንዘብ ሁሉ አጥቶ በመጨረሻው ሰውነቱን አጥቶ ነበርና ምንም ምንም የቀረበለት አልነበረምና እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ ከማለት በቀር ያለው ነገር የለም እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔርም ወሰደ አለ፡፡ የእግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለም ይመስገን አለ፡፡ እኛም ይህንን መከራ ልንታገስና የተጠበቀልንን ልንከተል ይገባናል..." እያለ አብዝቶ መከራት፡፡ ነገርግን በዚህም ምክር እናቱን መመለስና ለሰማዕትነት ማዘጋቸት አልቻለም፡፡ ከዚህ በኋላ ቂርቆስ ዓይኖቹን ወደሰማይ አቅንቶ መጸለይ ጀመረ፡፡ "እግዚአብሔር ሆይ ይህች ባርያህ ከምትክድ ከህይወት መፅሐፍ እኔን ፋቀኝ አለ፡፡ አቤቱ ይህነን ነገር ልታደርግ አይገባህም፤ አቤቱ እርሻውን ልታቃጥል ፍሬውንም ልትባርክ ትወዳለህን፡፡ አቤቱ እንጨቱን ቁረጡና አንድዱት ቅጠሉን ጠብቁ ብለህ ልታዝ አይገባህም፡፡ እንጨቱንም ቅጠሉንም ጠብቁ ብለህ እዘዝ እንጂ ይህ አይገባህም ያመነብህ ሁሉ ይህን ያየ ዘንድ፡፡ ማዳን የሚችል አምላክ ኑሮአቸው ቢሆን ከዚህ ከእሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ እንዳይጠራጠር፡፡ ዲያብሎስ ከባለስልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ ቅዱሳኑም ድል ነሳኋቸው ብሎ እንዳይመካ፣ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ እንዳይል አቤቱ የኃይል መንፈስ ለእናቴ ስጣት አበርታት..." ብሎ ጸለየ፡፡ በዚያን ጊዜ ዲያብሎስ ከእርሷ ሸሽቶ ሄደ፡፡ ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ እንዲህ አለች፡- በመንግስተ ሰማያት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ጌታህ ኃይል ስጠኝ፡፡ የሚጠብቀንን ገድላችንን እንፈፅምና ድል እንነሣ" አለችው፡፡ የብረት ጋኑን ሲነድ ሳየው በምንጭ ላይ በዝቶ እንደሚወርድ ጠል ሁኖ አየዋለሁና፡፡ ቅዱሳንም ይህንን ሲነጋገሩ አንስተው ከብረት ጋኑ ውስጥ ጨመሯቸው፡፡ በውስጡም አንገትን የሚቆለምም ልብን የሚያጣምም ሆድን የሚሰነጥቅ ሥርንም የሚበጥስ መሣሪያ ነበረበት፡፡ ወዲያውም የራማው ልዑል ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ ከሰማይ ወረደና የብረት ጋኑን እሳት ፈጽሞ አበረደው፡፡ ከቅዱሳንም አንዱን እንኳን ሳይነካው የብረት ጋን ማቃጠሉና መፍላቱ ፀጥ አለ፡፡ እንደ ውኃም ሆነ፡፡
ንጉሡም እሳቱ እንዳልጎዳቸው ሲያውቅ ከዚያ አውጥቶ በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ አፍና አፍንጫ መርዝ ከተተበት፣ ነገር ግን መርዙ ምንም አልጎዳውም እንዳውም ምግብ ሆነው፡፡ ዳግመኛም ጨውና በርበሬ በዐይኑ አነደደበት፡፡ አሁንም ምንም አልነካውም፡፡ ከዚህም በኀላ ሹም እስክድሮስም አስራ አራት የተሳሉና የጋሉ ብረቶች ያመጡ ዘንድ ዳግመኛ አዘዘ፡፡ ሰባቱን በእናቱ አካል ሰባቱን በሱ አካል ውስጥ ይተክሉ ዘንድ ከነዚሁም ሁለቱን በጆሮዎቹ ሁለቱን በዓይኖቹ ሁለቱን በአፍንጫዎቹ አንዱን በልቡ ይተክሉ ዘንድ አዘዘ፡፡በሕፃኑም ላይ ሹሙ እንዳዘዘው አደረጉበት፡፡ አሁንም ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና ፈወሳቸው፡፡
ዳግመኛም የሕጻኑን እራስ ከነቆዳው ገፈው በእሳት ውስጥ ይጨምሩ አንድ ሹም አዘዘ፡፡ እንዲሁም አደረጉበት፡፡ ዳግመኛም ቅዱስ ገብርኤል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጥኖ መጥቶ ይህንን መከራ ከሕፃኑ አራቀለት፡፡ ዳግመኛም ሹሙ በመቃን ውስጥ ጨመረው በገመድ እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ከዚህም መከራ መልአኩ አዳነው፡፡ ሐምሌ 19 ቀን በዓሉን በታላቅ ድምቀት የምናከብረው ይህንን ሁሉ የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤልን ተራዳኢነት በማሰብ ነው፡፡
ንጉሡም በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በብዙ ጭንቅና ሥቃይ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ለ3 ዓመታት አሠቃያቸው፡፡ እነርሱም መከራን እየተቀበሉ በከሀዲው ንጉሥ ፊት የአምላካቸውን ስም እየጠሩ መሰከሩ፡፡ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና ክብሩን ይመሰክሩለት ዘንድ የቢታንያን ድንጋዮችና የበለዓምን አህያ አንደበት ከፍቶ ያናገረ አምላክ ሦስት ዓመት እንኳን ባለሞላው በሁለት ዓመት ከዘጠኝ ወር ሕፃን ልጅ ላይ አድሮ በወቅቱ የነበሩ ዓላውያን ነገሥታት ክብሩን እንዲያውቁ አደረገ፡፡
ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ሄሮድስ ላስፈጃቸው 144,000 የቤቴልሔም ሕፃናት አለቃቸው ነው፡፡ ይህስ እንደምን ነው ቢሉ ሄሮድስ ያስፈጃቸው እነኚያ እልፍ የቤቴልሔም ሕፃናት የተገደሉት ጌታችንን ለማግኘት በተደረገው ፍለጋ ምክንያት ስለሆነ ቅዱስ ቂርቆስን በመሞት ይተካከሉታል እርሱ ግን የአምላኩን ስምና ክብር በማስተማርና በመመስከር ሰማዕትነትን ስለተቀበለ በዚህ ይበልጣቸዋልና ለእነኚያ እልፍ የቤቴልሔም ሕፃናት አለቃ አድርጎ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሾሞታል፡፡ ቅዱስ ገድሉም እንደሚናገረው ‹‹መንገድ ጠራጊ ከተባለ ከዮሐንስ መጥምቅ በቀር ሴቶች ከወለዱዋቸው እንደ አንተ ያለ አልተገኘም›› በማለት ጌታችን በማይታበል ቅዱስ ቃሉ ታላቅ የሆነ ቃልኪዳኑን በመሐላ አጽንቶለታል፡፡ በመጨረሻም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ተጋድሎውን ፈጽሞ ጥር 15 ቀን በ3 ዓመት ከ1 ወር ከ3 ቀኑ አንገቱን በሰይፍ ተቆርጦ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡ ሲሰየፍም ከአንገቱም ደም፣ ውኃና ወተት የወጣ ሲሆን ሦስት አክሊላትም ወርደውለታል፡፡ ጌታችንም የመከራውን ጽናት የትዕግስቱን ብዛት አይቶ ከመከራ ሊያሳርፈው ፈቀደና ተገልጾለት ‹‹ሰላም ለከ ኦ ፍቁርየ ቂርቆስ›› አለው፡፡ ‹‹ሰላም ላንተ ይሁን፤ የመከራህን ጽናት፣ የትዕግስትህን ብዛት አይቼ ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍህ መጣሁ›› ብሎ ብዙ ቃልኪዳን ሰጠው፡፡ ‹‹…ስምህ በተጠራበት፣ ቤተመቅደስህ በታነጸበት፣ ስዕልህ ባለበት ቦታ ሁሉ የሕፃናት እልቂት፣ የከብት በሽታ፣ የእህል እጦት ርሀብ፣ ቸነፈር አይደርስም›› የሚል አስደናቂ ቃልኪዳንም ገብቶለታል፡፡ ሕፃኑም በምድር ላይ አልተቀበረም ይልቁንም ጌታችን በኤልያስ ሰረገላ ሥጋውን አሳርጎለታል፡፡ እናቱ ቅድስት ኢየሉጣም በጥር 16 ቀን ሰማዕትቷን በክብር ፈጽማለች፡፡ የቅዱስ ቂርቆስ ማኅበርተኞች የሆኑ ዓሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎች የጌታችንን ክብር እየመሰከሩ በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡
የቅዱስ ቂርቆስና ማኅበርተኞች የሆኑ የቅዱሳን ሰማዕታት ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!
ዳግመኛም ጥር 14 ቀን እነዚኽ ታላላቅ ቅዱሳን በዓመታዊ በዓላቸው ታስበው ውለዋል፡-
+ የዚህን ዓለም ሹመት ለመሾም ወደ ንጉሡ እየሄደ ሳለ ማዕበል የተፋው አንድ በድን ቢያገኝ በዚያው የዓለምን ኃላፊነትና የእርሱንም መሞት አስቦ የመነኮሰውና የሴትንም ፊት እንዳያይ ቃል ገብቶ በታላቅ ተጋድሎ የኖረው አቡነ አርከሌድስ ዕረፍቱ ነው፡፡ 
+ በ12 ዓመቷ ከከሃድያንን ነገሥታት ጋር ስለ እምነቷ ተጋድላ በሰማዕትነት ያረፈችው ቅድስት ምህራኤል ዕረፍቷ ነው፡፡ + መቋሚያቸው በሰው አንደበት የምትናገረውና የወይራ ዛፍ እንደተደገፉ ሳይንቀሳቀሱ 40 ዓመት ሙሉ የጸለዩት ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ አካለ ክርስቶስ ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ ዐፅማቸው ደብረ ዳሞ ያረፈው የወሎው አቡነ ዘድንግል ዕረፍታቸው ነው፡፡ 
+ ዐፅማቸው ዋልድባ ዳልሻ የሚገኘው የትግራይ ተወላጁ አቡነ ምሥራቃዊ ልደታቸው ነው፡፡ 
+ ቅዱስ መክሲሞስ በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡ 
+ ቅድስት እምራይስ በሰማዕትነት ዐረፈች፡፡ 
+ ከተሰዓቱ ቅዱሳን ውስጥ አንዱና ዋነኛው የሆኑት ጻድቁ አቡነ አረጋዊ ልደታቸው ነው፡፡
ሰማዕቷ ቅድስት ምህራኤል፡- ይህችውም የከበረችና የተመሰገነች ቅድስት ምህራኤል ጠምዋህ ከሚባል አገር የተገኘች ታላቅ ሰማዕት ናት፡፡ ወላጆቿ ካህኑ አባቷ ዮሐንስና እናቷ ኢላርያ እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ደገኞች ናቸውና እርሷንም በሃይማኖት በምግባር ኮትኩተው አሳደጓት፡፡ መጀመሪያውንም ልጅ ስላልነበራቸው በስዕለት ከብዙ ዘመን በኋላ ነው ያገኟት፡፡ ስዕለታቸውም ደርሶላቸው ቅድስት ምህራኤልን ከወለዷት በኋላ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ አሳደጓት፡፡
ቅድስት ምህራኤልም 12 ዓመት በሆናት ጊዜ በላይዋ ባደረ በመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን መሥራት ጀመረች፡፡ ከሃዲው ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ በነገሠና አምልኮተ ጣዖትን በአዋጅ ባወጀ ጊዜ ቅድስት ምህራኤል ስለ ጌታችን አምላክነት መስክራ ሰማዕት መሆንን ተመኘች፡፡ ከዚህም በኋላ በቁርጥ ሀሳብ ተነሥታ ወደ ባሕር ዳርቻ በመሄድ በመርከብ ተሳፍራ ሄዳ ስሙ ፍልፍልያኖስ የሚባለው የዲዮቅልጥያኖስ መኮንን ዘንድ ደረሰች፡፡ በመርከብም ስትጓዝ ሌሎች ስለ ቀናች እምነታቸው ሰማዕትነትን ለመቀበል የተዘጋጁ ሰማዕታትን አግኝታ ከእነርሱ ጋር ነበረች፡፡ በመኮንኑም ፊት ቆማ እውነተኛውና ሊመለክ የሚገባው አምላክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ መሆኑን መሰከረች፡፡ መኮንኑም ስለ ታናሽነቷ ራርቶላት ከሌሎቹ ለይቶ ሊተዋት ወደደ፡፡ ነገር ግን ቅድስት ምህራኤል መኮንኑ እንደተዋት ዐውቃ የተመኘችውን ሰማዕትነት ሊያስቀርባት መሆኑን ባየች ጊዜ ዳግመኛ መኮንኑንና የረከሱ አማልክቶቹን በድፍረት ረገመችበት፡፡
ከዚህም በኋላ መኮንኑ በጣም ተቆጥቶ ጽኑ በሆኑ የተለያዩ ሥቃዮች አሠቃያት፡፡ ከቀናች ሃይማኖቷም ሸንግሎ ይመልሳት ዘንድ እንዳልተቻለው ሲያውቅ መርዛማ እባቦች፣ ጊንጦችና እፉኝቶች ወዳሉበት ጉድጓት ጣላት፡፡ ከቅድስት ምህራኤልም ጋራ ሌሎች ብዙ ሰማዕታት አብረው ተጣሉ፡፡ በዚህም ጊዜ የታዘዘ የእግዚአብሔር መልአክ ለቅድስት ምህራኤል ተገለጸላትና ከጌታችን ዘንድ የተሰጣትን ቃልኪዳን አስረከባት፡፡ ከዚህም በኋላ ነፍሷን ለእግዚአብሔር አሳልፋ ሰጥታ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች፡፡ ምእመናንም የከበረ ሥጋዋን መርዛማ እባቦችና ጊንጦች ካሉበት ቦታ አውጥተው በክብር ቀበሯት፡፡ በኋላም ወላጆቿ ልጃቸው ቅድስት ምህራኤል ስለ እምነቷ መስክራ በክብር ሰማዕት መሆኗን በሰሙ ጊዜ ከብዙ የሀገራቸው ሕዝብ ጋር መጥተው የከበረ ሥጋዋን አፍልሰው ወደ አገራቸው ወሰዱት፡፡ ያመረች ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው ሥጋውን በውስጧ ባኖሩ ጊዜ ከሰማዕቷ ቅዱስ ሥጋ ብዙ አስገራሚ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡
+ + +
አቡነ አርከሌድስ ግብፃዊ፡- በትውልዱ ከሮሜ ሀገር ከታላላቅ ወገኖች ነው፡፡ አባቱ ዮሐንስ እናቱ ሰንደሊቃ ሲባሉ ሁለቱም የእግዚአብሔርን ሕግ የሚጠብቁ እውነተኞች ነበሩ፡፡ ቅዱስ አርከሌድስም ዕድሜው 12 ዓመት በሆነው ጊዜ አባቱ ዮሐንስ ሞተ፡፡ በኋላም እናቱ ግን ሚስት ልታጋባው አሰበች እርሱ ግን ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ አባቱ በሕይወት ሳለ ንጉሡ የሾመው ነበርና እናቱ አሁንም ወደ ንጉሡ ሄዶ የአባቱን ሹመት ይቀበል ዘንድ አርከሌድስን መከረችው፡፡ ለንጉሡ የሚሰጥ እጅ መንሻንና አገልጋዮችን አድርጋ ብዙ ገንዘብ አስይዛ ላከችው፡፡ እርሱም በመርከብም ተጭኖ ሲሄድ ታላቅ ንፋስ ተነሣና ማዕበሉ አየለባቸው፡፡ መርከቡም ተሰበረ፡፡
ቅዱስ አርከሌድም አንዲት የመርከብ ስባሪ ሠሌዳ ላይ ተንጠልጥሎ ወደ የብስ ደረሰ፡፡ ከባህሩ ሲወጣ ማዕበል የተፋው አንድ በድን አገኘና ተቀምጦ ስለ በድኑ አለቀሰ፡፡ የዓለምን ኃላፊነትና እርሱም ከሞተ በኋላ አፈርነቱን አሰበ፣ ነፍሱንም ገሠጻት፡፡ ወደ ቀና መንገድ ይመራውም ዘንድ ወደ ጌታችን ለመነ፡፡ ረጅም መንገድ ተጓዘና ሶርያ ውስጥ በቅዱስ ሮማኖስ ስም ወደተሠራች አንድ ተራራማ ገዳም ደረሰ፡፡ ከገንዘቡም ከእርሱ ጋር የቀረውን ሁለት መቶ የወርቅ ዲናር ለአበ ምኔቱ ሰጠው፡፡ እንዲያመነኩሰውም ጠየቀው፡፡ መጀመሪያውኑ አርኬሌድስ ከመምጣቱ በፊት ለአበምኔቱ መንፈስ ቅዱስ የመምጣቱን ነገር አስረድቶት ነበርና እርሱ በደረሰ ጊዜ ደስ አለው፡፡ መነኮሳቱም ሁሉ ከጸለዩለት በኋላ አመነኮሰው፡፡
ከዚህም በኋላ የከበረ አርከሌድስ ጽኑ ተጋድሎ መጋደል ጀመረ፡፡ ሲጸልይ ይውላል ሲጸልይ ያድራል፤ ሁልጊዜ በየሰባቱ ቀን የሚጾም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም ሀብተ ፈውስን ሰጥቶት ብዙ ሕመምተኞችን ፈወሳቸው፡፡ ከዚህም በኋላ የሴቶችን ፊት ከቶ እንዳያይ ከጌታችን ጋር ቃል ገባ፡፡ ። እናቱም ለ12 ዓመት ያህል የልጇን ወሬ ምንም ስላልሰማች በእርሱ የሆነውን አላወቀችም ነበርና የሞተም ስለመሰላት እጅግ አዘነች፡፡ የእንግዶችና የመጻተኞች መቀበያ የሚሆን ቤት ሠርታ የመንገደኞች ማደርያ አደረገችው፡፡ በአንዲት ዕለት ያሳደረቻቸው እንግዶች የቅዱስ አርከሌድስን ዜና ሲናገሩ ሰማቻቸው፡፡ እንግዶቹም ስለ ቅድስናው፣ ስለ ተጋድሎው የሚያሳያቸውን ምልክቶችና ተአምራቶቹን፣ የመልኩንም ደም ግባት ሲነጋገሩ ሰምታ ልጇ እንደሆነ ዐወቀች፡፡
መንገደኞቹንም ስለ ሥራው ጠየቀቻቸውና ሥራውን ሁሉ ነገሯት፡፡ ልጇ በሕይወት እንዳለና ሕያው እንደሆነ ተረዳች፡፡ በዚያን ጊዜ ተነሥታ ወደ ከበረ ሮማኖስ ገዳም ሄደች፡፡ ወደ ልጇዋ ወደ ቅዱስ አርከሌድስ ‹‹እነሆ ፊትህን አይ ዘንድ ወድጄ እኔ እናትህ መጥቻለሁ›› ብላ መልእክት ላከች፡፡ ልጇ ቅዱስ አርከሌድም ‹‹ከቶ የሴቶችን ፊት እንዳላይ ከክብር ባለቤት ከጌታዬ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃል ገብቻለሁና ቃልኪዳኔን ማፍረስ አይቻለኝም›› ብሎ መልሶ ወደእርሷ ላከ፡፡ እናቱም ‹‹ፊትህን ካላሳየኸኝ እኔ ወደ ዱር እሄዳለሁ፣ አራዊትም ይበሉኛል›› ብላ ላከችበት፡፡ ቅዱስ አርከሌድስም እናቱ ካላየችው እንደማትተወው እርሱም ለእግዚአብሔር የገባውን ቃልኪዳን ማፍረስ እንደማይቻለው ባወቀ ጊዜ ነፍሱን እንዲወስዳት ወደ ጌታችን ለመነ፡፡ ከዚህም በኋላ የበሩን ጠባቂ ‹‹እናቴን ወደእኔ ትገባ ዘንድ ፍቀድላት›› አለው፡፡ እናቱም ወደ ውስጥ በገባች ጊዜ ልጇን ቅዱስ አርከሌድስን ሙቶ አገኘችውና በታላቅ ድምፅ በመጮህ አለቀሰች፡፡ የእርሷንም ነፍስ ይወስድ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነች፡፡ ጌታችንም ልመናዋን ተቀብሎ ነፍሷን ወሰደ፡፡
እናትና ልጅም በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ካረፉ በኋላ የሁለቱን ሥጋቸውን ለይተው ሊቀብሯቸው ሲሉ የቅዱስ አርከሌደስ በድን በሰው አንደበት መናገር ጀመረ፡፡ ‹‹የእናቴን ሥጋ ከሥጋዬ አትለዩ በሕይወቷ ሳለች ታየኝ ዘንድ ልቧን ደስ አላሰኘሁምና›› የሚል ቃል ከአርከሌድስ በድን ወጣ፡፡ ይህንንም ቃል በሰሙ ጊዜ እጅግ አድንቀው እግዚአብሔርን ካመሰገኑት በኋላ ሁለቱንም በአንድ መቃብር ውስጥ ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም በቅዱስ አርከሌድና በእናቱ ሥጋ ላይ ታላቅ ፈውስን ገለጠና አስገራሚ ተአምራት መታየት ጀመሩ፡፡ በሞት ካረፈ በኋላ በድኑ አፍ አውጥታ የተናገረች ይህ ታላቅ ጻድቅ በስሙ የተሰየመው ትልቅ ገዳም ትግራይ ተንቤን ሀገረ ሰላም ይገኛል፡፡
+ + +
ቅድስት እምራይስ፡- ይኽችውም ቅድስት ከከበሩ ደገኛ ክርስቲያኖች የተወለደች ናት፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እየተማረች አደገች፡፡ በአንዲትም ዕለት ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ ወርዳ ሳለ ተይዘው ስለ ክርስቶስ ታስረው የሚሠቃዩ ሰማዕታትን አየች፡፡ እነርሱም ጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት ናቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ቅድስት እምራይስ ወደ መኮንኑ ጭፍራ ዘንድ ቀርባ ‹‹እኔም በእነዚህ ቅዱሳን አምላክ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝና ስሜን ከስማቸው ጋር ጽፈህ ወደ ሰማዕትነት አደባባይ አድርሰኝ›› አለቸው፡፡ እርሱም ስሟን ከሰማዕታቱ ስም ጋራ ጽፎ አብሮ አሰራትና በከሃዲው መኮንን ቁልቁልያስ ፊት አቆማት፡፡ መኮንኑም ለጣዖታቱ እንድትሰግድ በብዙ የስንገላ ቃላት አባበላት ነገር ግን ቅድስት እምራይስ የጌታችንን አምላክነት እየመሰከረች የመኮንኑን ጣዖታት ረገመችበት፡፡ መኮንኑም እጅግ ተቆጥቶ አንገቷን በሰይፍ አስረጠውና ሰማዕትነቷን በድል ፈጽማ የክብር አክሊልን ተቀዳጀች፡፡
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት የከበረ ሕፃን የቅዱስ ቂርቆስ ማኅበርተኞች የሆኑ አራት ሺህ ሠላሳ አራት ሰዎች በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ ዜና ገድላቸው ከአባታቸው ከሕፃኑ ከቅዱስ ቂርቆስ ዕረፍት ጋር ጥር 15 ተጽፏል፡፡
የእጅግ የከበረ የቅዱስ ዱማቴዎስ ወንድም ቅዱስ መክሲሞስም ዕረፍቱ በዚሁ ዕለት ነው ነገር ግን ገድሉን በዚሁ ወር በ17 ከወንድሙ ታሪክ ጋር እንጽፈዋለን፡፡
የቅዱሳን ሰማዕታት ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!
 

Thursday, January 17, 2019

እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ


አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን

ጥር 10 እና 11-ይህቺ ዕለት በዮናኒ ቋንቋ ኤጲፋንያ ትባላለች፣ ትርጓሜውም መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው፡፡ ልዑል እግዚአብሔር ልዩ የሆነች የሦስትነቱን ምሥጢር ገልጦባታልና ይህች ዕለት እጅግ የከበረች ናት፡፡ መጥምቁ ዮሐንስም ለዚኽ ነው ጌታችንን ከማጥመቁ በፊት ጌታችንን - "አቤቱ አምላኬ ሆይ! የአብ ስም በአንተው አለ፣ የወልድ ስም አንተው ነህ፣ የመንፈስ ቅዱስም ስም በአንተው ሕልው ሆኖ አለ፡፡ ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ፣ አንተን ግን በማን ስም አጠምቃለሁ? ብሎ የጠየቀው!



በዚኽች በከበረች የጥምቀት ዕለት በጥምቀት ወቅት የክብር ባለቤት ጌታችንና ያጠመቀው ቅዱስ ዮሐንስ ብለው እንደተነጋገሩ፡- ‹‹በዚያን ቀን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ ያጠምቀው ዘንድ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወደ ዮሐንስ መጣ፡፡ ዮሐንስም በእርሱ ላይ አድሮበት ባለው በመንፈስ ቅዱስ ፀጋ ጌታችን ወደ እርሱ ሲመጣ ባየው ጊዜ አሰምቶ ጮኸ፤ በታላቅ ቃልም እንዲህ አለ፡- እኛን ለማዳን የመጣው የእግዚአብሔር በግ እነሆ፡፡ ነቢያትም ስለ እርሱ ትንቢት የተናገሩለት ንጉሠ ነገሥት ይህ ነው፡፡ በዕውነት ቀዳሚና ተከታይ የሌለውና ለመንግሥቱም ፍጻሜ የሌለው አምላክ ይህ ነው፡፡ ዮሐንስም ይህን ቃል እየተናገረ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጠርቶ እንዲህ አለው፡- ዮሐንስ ሆይ! ስለ እኔ የተጻፈውን ሕግ ሁሉ ትፈጽም ዘንድ እነሆ ይገባሃል፤ እነሆ በአየኸው ሁሉ ምስክር ትሆን ዘንድ በአንተ እጅ የምጠመቅበት ጊዜ ስለደረሰ አጥምቀኝ አለው፡፡ ዮሐንስም ለጌታችን እንዲህ ብሎ መለሰለት፡- ወደ አንተ መጥቼ መጠመቅ ለእኔ ይገባኛል እንጂ እኔ ባሪያህ ሆኜ ሳለሁ በእኔ እጅ ትጠመቅ ዘንድ ስለምን ወደ እኔ መጣህ? አንተ ጌታ ሆነህ ይህ ነገር ፈጽሞ አይገባም አለው፡፡ ጌታችንም ዮሐንስ ሆይ! በአንተ እጅ ስለመጠመቄ ደስ መሰኘት ይገባሃል፤ አትፍራም፡፡ አንተ እጅህን በራሴ ላይ ታኖራለህ፤ ሰውነቴንም እኔ አጠምቃታለሁ፡፡ ዮሐንስ ሆይ! እንቢ አትበለኝ እነሆ ነቢያት ስለ እኔ የተናገሩትን ሕግና ትእዛዝን ሁሉ ልፈጽም መጥቻሁና አለው፡፡ ጌታችንም ይህን ቃል ለዮሐንስ ነግሮት ከጨረሰ በኋላ ወደ ዮርዳኖስ ውኃ ውስጥ ገባ፡፡ ያንጊዜ ዮርዳኖስ አርባ ክንድ ወደኋላው ተመለልሶ ሸሸ፣ ውኃውም በእሳት እንዳፈሉት ሆነ፡፡ በጸናችው የጥበቡ ኃይል አዳምን ከነልጆቹ ለማዳን ወደዚህ ዓለም ከመጣው ከጌታችን ፊት ዮርዳኖስ ስለ መሸሿና ወደ ኋላዋ ስለ መመለሷ ነቢዩ ዳዊት ትንቢት ተናግሮአል፡- አቤቱ ውኆች አዩህ፣ ውኆችም አይተውህ ፈሩ፡፡ አንቺ ባሕር የሸሸሽው፣ አንቺ ዮርዳኖስ ወደ ኋላ የተመለሽው ምን ሆናችኋል? ጌታችንም ዮርዳኖስን እንዲህ በማለት ገሠፀው፡- ዮርዳኖስ ሆይ! በጥምቀቴ ጊዜ አትሽሽ፣ ባለህበት ቦታም ተመልሰህ ቁም አለው፡፡ ጌታችንም ይህን ቃል በተናገረው ጊዜ የነቢዩ ዳዊት ትንቢት ይደርስ ዘንድ ውኃው ወደ ቦታው ተመልሶ ቆመ፤ ከጌታችንም ፊት ሰገደ፡፡ ዮሐንስም ዮርዳኖስ ወደ ኋላዋ ተመልሳ መሸሿንና በጌታችን ትእዛዝ ወደ ቀድሞ ቦታዋ ተመልሳ ከጌታችን ፊት ስትሰግድ ባየና በተመለከተ ጊዜ ፈራ፣ ደነገጠ፣ ታላቅ መንቀጥቀጥም አደረበት፣ በፊቱም ሰገደለት፡፡እነሆ አንተ ጌታዬና ፈጣሪዬና ነህ እኔ አገልጋይህ ባሪያህ ነኝ፣ አቤቱ ጌታዬ ሆይ! ይህን ሁሉ ደካማነቴን ተመልክተህ እጁን በራስህ ላይ ያኖር ዘንድ ባሪያህን አታስገድደው አለው፡፡ ጌታችንም ለዮሐንስ እንዲህ አለው፡- ይህ ለእኛ ተድላ ደስታ ነውና እውነትን ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና ያዘዝኩህን አድርግ አለው፡፡ አንተም መጥምቀ መለኮት ተብለህ ክብርህ ይነገራልና እኔም በባሪያው እጅ ተጠመቀ ተብዬ ትሕትናዬ ይነገራልና አለው፡፡ ይህንንም ሲናገረው ዮሐንስ ተወው፡፡ ዮሐንስም እንዲህ አለው፡- የአብ ስም በአንተው አለ፣ የወልድ ስም አንተው ነህ፣ የመንፈስ ቅዱስም ስም በአንተው ሕልው ሆኖ አለ፡፡ ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ፣ አንተን ግን በማን ስም አጠምቃለሁ? አለው፡፡ ጌታም ዮሐንስን እንዲህ እያልክ አጥምቀኝ አለው፡- እንደ መልከጼዴቅ ሹመት የዓለሙ ካህን፣ ብርሃንን የምትገልጽ፣ የአብ የባሕርይ ልጅ፣ አቤቱ ይቅር በለን፣ የዓለምን ኃጢአት የምታስወግደው የእግዚአብሔር በግ ይቅር በለን እያልክ አጥምቀኝ አለው፡፡ ያንጊዜ ዮሐንስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ጥር ዐሥራ አንድ ቀን ከሌሊቱ በአሥር ሰዓት አጠመቀው፡፡››


ከበዓሉ ረድኤት ይክፈለን!


(ምንጭ፡- ሚጣቅ አማኑኤል ያሳተመው የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ ገድል)


እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሰን!


LIKE OUR PAGE

https://www.facebook.com/tewadhdohaimanotachin




https://www.youtube.com/watch?v=3fnWuuHj5ZM