Wednesday, June 19, 2019

ሰኔ 13 እና 14


አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን

<3 ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it)

ሰኔ 13 እና 14

+ ከታላቁ ጻድቅ ከቅዱስ ኤጲፋንዮስ ጋር በታናሽነቱ በአባ ኤስድሮስ ገዳም መንኩሶ በታላቅ ተጋድሎ የኖረው የኢየሩሳሌሙ ቅዱስ አባ ዮሐንስ ዕረፍቱ ነው፡፡ ዮሐንስም በሹመቱ ሳለ ገንዘብን በመውደድ ጌታችንን ቢያሳዝነው ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዐይኖቹን አሳውሮ በኋላም እንደገና መልሶ አንድ ዐይኑን በማብራት በተአምራት ወደ ንስሓ የመለሰው ነው፡፡

+ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት የሄኖስ ልጅ ቃይናን የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ቃይናንም 170 ዓመት ኖሮ መላልዔልን ወደለደው፡፡ መላልዔልንም ከወለደው በኋላ 740 ዓመት ኖረ፡፡ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለደ፡፡ የቃይናንም መላ ዘመኑ 910 ዓመት ሲሆነው በዚህች ዕለት ዐረፈ፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡

+ + + + +
አቡነ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም፡- ይኸውም ቅዱስ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ሲሆን ከታላቁ ጻድቅ ከአቡነ ኤጲፋንዮስ ጋር በታናሽነቱ በአባ ኤስድሮስ ገዳም መንኩሶ በታላቅ ተጋድሎ ይኖር የነበረ ነው፡፡ የእርሱም ደግነቱ፣ ትሩፋቱ፣ ቅድስናውና ታላቅ ተጋድሎው በቦታው ሁሉ ተሰማ፡፡ ከዚህም በኋላ አቡነ ኤጲፋንዮስን በቆጵሮስ ሀገር ኤጲስቆጶስ አድርገው ሲሾሙት አቡነ ዮሐንስን ደግሞ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አድገው ሾሙት፡፡

አቡነ ዮሐንስም በሹመት በነበረ ጊዜ ሰይጣን በገንዘብ ፍቅርና በዚህ ዓለም ክብር አሳተው፡፡ የቀድሞ ግብሩን እረስቶ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች የማይራራ ሆነና ቁራሽ እንጀራን እንኳን የማይሰጣቸው ሆነ፡፡ ይልቁንም ለራሱ ብዙ ገንዘብ ሰብስቦ ለማዕዱ የሚመገብበትን የወርቅና የብር ሣህን አሠራና በድሎት የሚኖር ሆነ፡፡
አቡነ ኤጲፋንዮስም ይህን በሰማ ጊዜ የአቡነ ዮሐንስን የቀድሞውን ተጋድሎውንና የዓለም መናኒነቱን፣ ፍቅሩንም አስታውሶ እጅግ አዘነ፡፡ እርሱም ከመጀመሪያው ጊዜ ጀምሮ መንፈሳዊ ወንድሙና ወዳጁ ነበር፡፡ ስለዚህም ብፁዕ ኤጲፋንዮስ ከቆጵሮስ ተነሥቶ ወደ ኢየሩሰሌም ወደ አቡነ ዮሐንስ መጣ፡፡ ከስሕተቱ ይመልሰውና በጥበብ ያድነው ዘንድ አስቦ የጌታችን መቃብር ባለበት ቤተ መቅደስ ለመስገድ እንደመጣ ነገረው፡፡ በተገናኙም ጊዜ አቡነ ዮሐንስ አቡነ ኤጲፋንዮስን ወደ ቤቱ አስገብቶ ማዕድ አዘጋጀለት፡፡ በማዕዱም ላይ በወርቅና በብር ያሠራቸውን ሣህኖቹን አስቀመጠ፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስ ከእርሱ ዘንድ ወጥቶ ወደ አንዱ ገዳም ሄዶ አደረ፡፡ ወደ አቡነ ዮሐንስ እንዲህ ብሎ መልእክት ላከ፡- ‹‹ወንድሜ ሆይ ከቆጵሮስ ሀገር ሽማግሎችና የሕዝቡ መምህራን ወደ እኔ መጥተዋልና በእነርሱ ፊት ታከብረኝ ዘንድ ከወርቅና ከብር ያሠራሃቸውን የማዕድ ዕቃዎችህን ይመገቡባቸው ዘንድ እንድትክልኝ›› ብሎ መልእክት ላከበት፡፡ አቡነ ዮሐንስም የከበሩ ዕቃዎቹን ላከለት፡፡

አቡነ ኤጲፋንዮስም የከበሩ የማዕድ ዕቃዎቹን ወስዶ ሸጣቸውና ገንዘቡን ሁሉ ለድኆችና ለምስኪኖች መጸወተው፡፡ ሁለቱም በተገናኙ ጊዜ አቡነ ዮሐንስ ‹‹የላኩልህን የከበሩ የማዕድ ዕቃዎቼን መልስልኝ›› አለው፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስም ‹‹እሺ›› አለው፡፡ በሌላ ጊዜም እስከ ሦስት ጊዜ ደጋግሞ ጠየቀው፡፡ በአንዲት ዕለትም የጌታችን መቃብር ካለበት ቤተ መቅደስ ሲወጣ አግኝቶ ያዘውና ‹‹ንብረቶቼን ካልሰጠኸኝ›› ብሎ ያዘው፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስም ወደ ጌታችን ቢጸልይ የአቡነ ዮሐንስ ሁለት ዐይኖቹ ወዲያው ታወሩ፡፡ እርሱም እጅግ ደንግጦ ይቅር ይለው ዘንድ አቡነ ኤጲፋንዮስን ለመነው፡፡ አቡነ ኤጲፋንዮስም የእውነት መጸጸቱን አይቶ አንዲቱን ዐይኑን አበራለት፡፡ እንዲህም አለው፡- ‹‹ነፍስህን ታስብ ዘንድ አንዲቷን ዐይንህን ዕውር እንደሆነች ትቀር ዘንድ ጌታችን ትቶልሃል›› ብሎ ገሠጸው፡፡ ‹‹እነሆ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የቀድሞ ድካምህንና ተጋድሎን አስቦ እራርቶልሃልና ከስሕተትህም አድኖሃል›› አለው፡፡
ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ አቡነ ዮሐንስ ከእንቅልፉ እንደነቃ ሆኖ የቀድሞ መልካም ሥራውንም መሥራት ጀመረ፡፡ ምንም ሳያስቀር ጥሪቱን ሁሉ አውጥቶ በመሸጥ መጸወተው፡፡ ተጋድሎውንም እንደበፊቱ በጽኑ ጀመረ፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን የመፈወስ ሀብት ሰጠው፡፡ ብዙ አስገራሚ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ብዙ ካገለገለና ጌታችንም ታላቅ ቃልኪዳን ከገባለት በኋላ በዚህች ዕለት በሰላም ዐረፈ፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡
+ + + + +

ሰኔ 14-የከበሩ ቅዱሳን አክራ፣ ዮሐንስ፣ አብጥልማ እና ፊሊጶስ በሰማዕትነት ዐረፉ፡፡ እነዚህም አራት የከበሩ ቅዱሳን በጌታችን ስም ሰማዕት ይሆኑ ዘንድ በምክር ተስማሙ፡፡ አክራና ፊሊጶስ ወንድማማቾች ሲሆኑ እነርሱም የከበሩ ባለጸጎች ናቸው፡፡ ዮሐንስና አብጥልማ ግን የከበሩ ቀሳውስት ናቸው፡፡ አራቱም ሰማዕት ይሆኑ ዘንድ ከተስማሙ በኋላ ቀርጥስ ወደሚባል አገር ሄደው በከሃዲው መኮንንነ ፊት ቆመው የጌታችንን አምላክነት መሰከሩ፡፡ መኮንኑም በቀስት እንዲነድፏቸው አዘዘ፡፡ ነገር ግን ቀስቶቹ ሳይነኳቸው ቀሩ፡፡
ዳግመኛም በእቶን እሳት ውስጥ ጨመሯቸው፣ ጌታችንም መልአኩን ልኮ አዳናቸው፡፡ ከዚህም በኋላ በፈረሶች ጅራት ላይ አሥረው ከቀርጥስ እስከ ይምንሑር አገር ድረስ ጎተቷቸው፡፡ አሁንም ጌታችን ፈውሳቸውና ምንም ጉዳት እንዳላገኛቸው ሆኑ፡፡ ከዚህም በኋላ መኮንኑ ማሠቃየት በሰለቸው ጊዜ ራስ ራሶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘ፡፡ እንደትእዛዙም ከይምንሑር ከተማ አውጥተው በሰይፍ አንገታቸውን ቆረጧቸውና የሰማዕትነታቸው ፍጻሜ ሆነ፡፡ እነርሱም የክብርን አክሊል ተቀዳጁ፡፡
ፃ ከምትባል አገር ሰዎቸ መጥተው የቅዱስ አክራን ሥጋ ወሰዱ፡፡ ከይምንሑር ከተማ የመጡ ሰዎች ደግሞ የቅዱስ ፊሊጶስን፣ የቅዱስ ዮሐንስንና የቅዱስ አብጥልማ ሥጋቸውን ወስደው ለሁሉም የተዋቡ አብያተ ክርስቲያናትን ሠርተውላቸው የሰማዕታትን ሥጋቸውን በውስጣቸው አኖሩ፡፡ ከቅዱሳኑም ሥጋ አስገራሚ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/tewadhdohaimanotachin
https://ttewahdo.blogspot.com/

No comments:

Post a Comment