Wednesday, November 28, 2012

ትምህርተ ጋብቻ ክፍል ፦ ፩

፩፦ « መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር ነው፤» ዕብ ፲፫፥፬

          ጋብቻን ባርኮና ቀድሶ ለሰው ልጅ የሰጠው እግዚአብሔር ነው። በመሆኑም ጋብቻ የእግዚአብሔር ጸጋ ነው። ስለዚህ በዓይን ምኞት ተጋርደው፥ በሥጋ ፍላጐት ተነድተው በስሜት ፈረስ ጋልበው የሚገቡበት ሳይሆን በጸሎት እና በምልጃ ፈቃደ እግዚአብሔርን ጠይቀው የሚፈጽሙት ታላቅ ምሥጢር ነው።

          ጋብቻ የሰው ሁሉ ሕልም ነው። የማይመኘው፥የማይፈልገው የለም። የሰው ሁሉ ጸሎት፥ የሰው ሁሉ ስእለት ነው። ለመሆኑ፦ ህልሙ የተፈታለት ጸሎቱ የደረሰለት ስዕለቱ የሰመረለት ስንቱ ይሆን? ያላገባው ይናፍቃል ያገባው ደግሞ ያማርራል። ከጋብቻ በፊት « መልአክ » የተባለ የትዳር ጓደኛ ከጋብቻ በኋላ «ሰይጣን» ይባላል። «እኔ የመረጥኩትን ካላገባሁ እሰቀላለሁ፤» እንዳልተባለ «ካልተፋታሁ መርዝ እጠጣለሁ፤» ለማለት ችግር የለም። ከጋብቻ በፊት ምክር ላለመስማት አሳብ ላለመቀበል፦ «ስለ እኔ ማንም አያገባውም፤» ተብሎ በር እንዳልተዘጋ ሁሉ ከጋብቻ በኋላ ግን ጣልቃ የማያስገቡት ሰው  የለም «ምን በወጣህ ምን በወጣሽ፤» የሚለውን ፈጥኖ ለመቀበል በሩ ለሁሉም ክፍት ነው።

፪፦ ጋብቻ እንዴት ተጀመረ?

          ጋብቻ በአዳምና በሔዋን እንደተጀመረ የጎላ፥ የተረዳ የታወቀ ነገር ነው። «ተባዕተ ወአንስተ ገብሮሙ፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው፤ » እንዲል፦ አዳም ሲፈጠር ሔዋን በውስጡ ነበረች። ዘፍ ፩፥፳፰። ይህም በባህርዩ ነበረች ማለት ነው። አንድ አካል፥ አንድ ሥጋ ከሚያሰኛቸው ምሥጢር አንዱና ዋነኛውም ይኸው ነው።

          ጋብቻ የተጀመረው በአዳም ጥያቄ ነው፤ ጥያቄዎም የኅሊና ማለትም ውሳጣዊ ነበር። ምክንያቱም፦ ከላይ እንደተ መለከትነው፦ የትዳር ጓደኛው በውስጡ ስለነበረች ነው። « እግዚአብሔር አምላክም፦ ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም፤ የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት፥አለ፤»ይላል። እግዚአብሔር እንዲህ ማለቱ፦ በአዳም ኅሊና ውስጥ ይህ ጥያቄ እንደሚነሣ ስለሚያውቅ ነው። መናገሩም ለአዳም ኅሊና እንጂ ሔዋን ለአዳም እንደምትፈጠርለት አስቀድሞ በእግዚአብ ሔር ዘንድ የተወሰነ ነው።

          እግዚአብሔር፦ የምድር አራዊትንና የሰማይ ወፎችን ሁሉ፦ ሕያው ነፍስ ላለውም ሁሉ ስም ያወጣላቸው ዘንድ ወደ አዳም አመጣቸው። ይላል። ሂደቱም እንደሚከተለው ነው። እግዚአብሔር ዓርብ በነግህ አዳምን ከፈጠረ በኋላ ቅዳሜ መፍጠሩን ተወ። እሑድ እንስሳትን አራዊትን አመጣለት ሰኞ ማክሰኞ አዕዋፋትን አመጣለት፤ ረቡዕ በየብስ የተጠፈጠሩ ፍጥረታትን አመጣለት፤ ሐሙስ በባሕር የተፈጠሩ ፍጥረታትን አመጣለት፤ ለሁሉም ስም አወጣላቸው። በዚህን ጊዜ አዳም፦ ሁሉም ተባዕትና አንስት (ወንድና ሴት) መሆናቸውን አይቶ « ከእኔ በቀር ብቻውን የተፈጠረ የለም፤» ብሎ አዘነ። «ነገር ግን ለአዳም እንደ እርሱ ያለ ረዳት አልተገኘለትም ነበር » ይላል።

፥፩ ሐዘነ አዳም፤

          እግዚአብሔር አዳም እስኪያዝን የጠበቀው ያለ ምክንያት አይደለም። አጭቶ፥ ወድዶ፥ ፈቅዶ እንዲገባበት ነው። ይህም፦ ወደፊት ሔዋን ስታሳስተው ለኃጢአቱ እግዚአብሔርን ምክንያት እንዳያደርግ ይጠብቀዋል። አዳም ሳያዝን ሔዋንን ፈጥሮለት ቢሆን ኖሮ፦ « ይኼ እግዚአብሔር ፍጠርልኝ ሳልለው ሔዋንን ፈጥሮ ምክንያተ ስሕተት ሆነችብኝ፤» ባለ ነበር። እግዚአብሔር ግን አዳም እስኪፈልግ ጠብቆ ከጎኑ አንዲት አጥንት ወስዶ ሴት አድርጎ ሠራለት። አዳምም፦ «ይህች አጥ ንት ከአጥንቴ ናት ሥጋም ከሥጋዬ ናት፤ እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል። ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፥ ከሚስቱም ይጣበቃል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ።» ብሎ እግዚአብሔር የሰጠውን በጸጋ ተቀበለ። ዘ፪፥፲፰-፳፬።

፪፥፪፦ አንድ ሥጋ መሆን፤

          አዳምና ሔዋን በጋብቻ አንድ አካል መሆናቸው፦ ሔዋን ከአዳም የጎን አጥንት በመፈጠሯ ብቻ አይደለም። አንድ ክብር በመውረስም ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ፦ «እናንተ ባሎች ሆይ ደካማ ፍጥረት ስለሆኑ ከሚስቶቻችሁ ጋር በማስተዋል አብራችሁ ኑሩ፤ ጸሎታችሁ እንዳይከለከል አብረው ደግሞ የሕይወትን ጸጋ እንደሚወርሱ አድረጋችሁ አክብሩ አቸው።» ያለው ለዚህ ነው። ፩ኛ ጴጥ ፫፥፯። ከዚህም ሌላ አንድነታቸው አንድ ልብስ በመልበስ ነው። ፈቃደ ሥጋቸው በጠ የቃቸው ጊዜም በግብር አንድ ይሆናሉ። ወንድ ቢወለድ ያንተ ነው፥ ሴት ብትወለድ ያንቺ ነው አይባባሉም። ሁለት ሆነው አንድ ልጅ ያስገኛሉ። አንድም፦ ከእናት ደም ከአባት ዘር ተከፍሎ አንድ ሰው ሁኖ ይወለዳል።

፪፥፫፦ ሁለቱም ዕራቁታቸውን ነበሩ፤

          አዳምና ሔዋን ከዚህ ዓለም ልብስ ዕራቁታቸውን ነበሩ። አዳም ከሱፍ የተሠራ ሙሉ ልብስ አልለበሰም ሔዋንም ዋጋው እጅግ ውድ የሆነ ቬሎ አልለበሰችም። መጫሚያም አልነበራቸውም። የጣት ቀለበት የጆሮ ጌጥ የእጅ አንባር የእግር አልቦ አላደረጉም። ቅዱስ ጴጥሮስ ይኽንን ይዞ ነው፥ «ለእናንተም ጠጉርን በመሸረብና ወርቅን በማንጠልጠል ወይም ዋጋው ብዙ የሆነ ልብስን በመጐናጸፍ የውጭ ሽልማት አይሁንላችሁ። ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ ፥የዋህና፦ ጸጥ ያለ መንፈስ ያለው የማይጠፋና የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ፤» ያለው። ፩ኛ ጴጥ ፫፥፫። ሐዋ ርያው ቅዱስ ጳውሎስም፦ « እንዲሁም ደግሞ ሴቶች በሚገባ ልብስ ከእፍረትና ራሳቸውን ከመግዛት ጋር ሰውነታቸውን ይሸ ለሙ፤ እግዚአብሔርን እንፈራለን ለሚሉት ሴቶች እንደሚገባ መልካም በማድረግ እንጂ በሹሩባና በወርቅ ወይም በዕንቊ ወይም ዋጋው እጅግ በከበረ ልብስ አይሸለሙ።» ብሏል። ፩ኛ ጢሞ ፪፥፱።

          አዳምና ሔዋን ብርሃን ለብሰው ስለነበር ዕራቁታቸውን ሆነው አይተፋፈሩም ነበር። «ብርሃን የተሰወረውን ይገል ጻል እንጂ የተገለጸውን ይሰውራልንቢሉ እግዚአብሔር ሰውር ካለው ይሰውራል። አንድም አዳምና ሔዋን ከልብሰ ጢአት ዕራቊታቸውን ነበሩ። ( ኃጢአት በደል አልነበረባቸውም) ማለት ነው። አይተፋፈሩም ነበር ማለትም ለሰባት ዓመታት ኃፍረተ ነፍስ አልነበረባቸውም ነበር ማለት ነው።

፫፦ የጋብቻ ዓላማ፤

          የጋብቻ ዓላማዎች ሦሰት ናቸው። የመጀመሪያው። « የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት፤» እንዲል፦ ለመረዳዳት ነው። መረዳዳት ሲባልም በሥጋ ብቻ አይደለም በነፍስም ጭምር ነው። ለሥጋቸው በሥራ ሲረዳዱ ለነፍሳችው ደግሞ በጸ ሎት ይረዳዳሉ። ለምሳሌ፦ ይስሐቅ፦ ሚስቱ ርብቃ ለሃያ ዓመታት መክና ልጅ አልወለደችለትም ነበር። በዚህም ምክንያት ስለ ርብቃ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ እግዚአብሔርም ተለመነው፥ ርብቃም መንታ ፀነሰች ይላል። ዘፍ ፳፭ ፥፳፩። ሁለተ ኛው በፍትወተ ሥጋ ላለመቸገር ነው። ሦስተኛው ደግሞ፦ «ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው ፥እግዚአብሔርም ባረካቸው ፥እንዲህም አላቸው፦ ብዙ ተባዙ ፥ምድርንም ሙሉአት።» እንዲል፦ ዘር ለመተካት ነው። ዘፍ ፩፥፳፰። እነዚህም እንደ ሦስት ጉልቻዎች የሚቆጠሩ ናቸው።

፬፦ ከመጀመሪያው ጋብቻ ምን እንማራለን?

          አዳምና ሔዋን ወደዚህ ዓለም ከመምጣታቸው በፊት፦ እግዚአብሔር በሥጋም በነፍስም የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ አዘጋጅቶላቸዋል። ከሁሉም በላይ በጸጋ አክብሮአቸዋል። ፍጥረታት ሁሉ ይታዘዙላቸውና ይገዙላቸው ነበር። እግዚአብሔር በልግስና ከሰጣቸው ሀብት በስተቀር በራሳቸው ያመጡት የራሳቸው የሆነ ምንም አልነበራቸውም። ሁለቱም ዕርቃናቸውን ነበሩ። ትልቁ ሀብት እግዚአብሔር በአርአያውና በመልኩ ፈጥሮ የሰጣቸው አካል ነው። አዳም በአርባ ቀኑ ሔዋንም በሰማ ንያ ቀኗ ወደ ገነት የገቡት ይህን አካላቸውን ይዘው ነው። ከገነት በተባረሩም ጊዜ ከአካላቸው በስተቀር ይዘውት የወጡት ምንም ነገር የለም። ስለዚህ ጋብቻን በምናስብበት ጊዜ ሁሉን ነገር እግዚአብሔር የሚያዘጋጅ መሆኑን ማመን ያስፈልጋል። ለጋብቻ የመረጥነውም ሰው ዕራቁቱን ቢሆንም (ምንም ባይኖረው) እርሱነቱን ወይም እርሷነቷን ብቻ ለመቀበል መዘጋጀት አለብን። ወደዚህ ዓለም የመጣነው ዕርቃናችንን መሆኑን ለአፍታም መርሳት የለብንም። ዓለምን ጥለን የምንሄደውም ዕርቃናችንን ነው። ጻድቁ ኢዮብ፦ «ከእናቴ ማኅጸን ራቁቴን ወጥቻለሁ ራቁቴንም ወደ ምድር እመለሳለሁ፤ እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔር ነሣ እግዚአብሔርም እንደፈቀደ ሆነ የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን » ያለው ለዚህ ነው። ኢዮ ፩፥፳፩።

፭፦ ምክር

          ጋብቻን በምናስብበት ጊዜ ከቤተሰብ ጋር ከንስሐ አባትም ጋር መምከር ያስፈልጋል። ይኽንን በተመለከተ ጠቢቡ ሰሎሞን፦ «ልጄ ሆይ የአባትህን ምክር ስማ የእናትህንም ሕግ አትተው፤ ለራስህ የሞገስ ዘውድ ለአንገትህም ድሪ ይሆን ልሃልና።» ብሏል። ምሳ ፩፥፰። የጥበብ፥ የማስተዋል የምክር የኃይል የዕውቀትና የእውነት መንፈስ ከእግዚአብሔር ውና። ኢሳ ፲፩፥፪። እግዚአብሔር የሽማግሌዎችን ምክር ያውቃል። ኢዮ ፲፪፥፳። «የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላ ል፦ ይህ ምክር አይጸናምና አይሆንም » እንዲል፦ የማይጸናውንም ምክር እርሱ ያውቃል። ኢሳ ፯፥፯። ጌታችንም በወን ጌል፦ «የዋሃን ብፁዓን ናቸው፤ » ያለው በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን የሚኖሩትን ነው። ማቴ ፭፥፭።

          ምክር ሲባል ከራሱ ጥቅም አንፃር ብቻ የሚመክርም ስላለ ማመዛዘን ያስፈልጋል። ይኽንን በተመለከተ « መካር ሁሉ ይመክራል፤ ነገር ግን ራሱን ይጠቅም ዘንድ የሚመክር አለ። ከሚመክርህ ሰው ልቡናህን ጠብቅ። ስለ ራሱ ይመክርሃልና፤ ይወድድህም ዘንድ አስቀድመህ ፍላጎቱን ዕወቅበት። ገንዘብህን የሚያጠፋብህን ነገር ያመጣብሃል በጎ ነገር አደረግህ ይል ሃል፤ በተቸገርህም ጊዜ አይቶ ይስቅብሃል። ከሚጠባበቅህ ሰው ጋር አትማከር፤ ለሚመቀኝህም ሰው ነገርህን ሰውር።» የሚል በመጽሐፈ ሲራክ ተጽፏል። ሲራ ፴፯፥፯። ምክንያቱም ምክራቸው፦ ምክረ አኪጦፌል የሆኑ ብዙ ሰዎች አሉና ነው። አኪ ጦፌል የንጉሥ ዳዊት አማካሪ ነበር። ነገር ግን ልጁ አቤሴሎም አባቱን ንጉሥ ዳዊትን ባሳደደው ጊዜ፦ ከአቤሴሎም ጋር ሆኖ ክፉ ምክር ይመክረው ነበር። ፪ኛ ሳሙ ፲፭፥፲፪ ፲፯፥፩-፳፫። የሃያ ሁለት ዓመት ልጅ አካዝያስም በነገሠ ጊዜ፦ ጎቶልያ የተባለች እናቱ ብዙ ጊዜ ክፉ እንዲያደርግ ትመክረው ነበር። ፪ኛ ዜና ፳፪፥፩። ንጉሥ አክዓብ ናቡቴን አስገድሎ ርስቱን የነጠቀው በሚስቱ ምክር ነው። ፩ኛ ነገ ፪፥፩-፲፮።

፮፦ ፈቃደ እግዚአብሔርን መጠየቅ።

          ፈቃደ እግዚአብሔር የሚጠየቀው በጸሎት ነው። አዳም ከሐዘን ጋር የጸለየው በኅሊናው ነው። በመሆኑም ከልብ መጸለይ ያስፈልጋል። «ፈቃድህ በሰማይ (በመላእክት ዘንድ) እንደሆነ እንዲሁም በምድር (በደቂቀ አዳም ዘንድ) ይሁን፤» ማለት ይገባል። ማቴ ፮፥፲። እንደ ፈቃዱም ስንለምነው ይሰማናል። ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ « በእግዚአብሔር ዘንድ ያለችን መውደድ ይህች ናት፤ በስሙ ከእርሱ ዘንድ የምንለምነውን ይሰማናልና። የምንለምነውንም እንደሚሰማን ካወቅን እንግዲያስ በእርሱ ዘንድ የለመነውን ልመና እንደተቀበልን እናውቃለን። » ያለው ለዚህ ነው። ፩ኛ ዮሐ ፭፥፲፬። ለምሳሌ፦ ሁለት ማየት የተሳናቸው ሰዎች፦ የዳዊት ልጅ ሆይ ፥ማረን፤ እያሉ በእምነት በለመኑ ጊዜ፦ «እንደ እምነታችሁ ይሁንላችሁ፤» ብሎ ዓይኖቻቸውን ዳሰሰላቸው ዓይኖቻቸውም ተከፈቱ ይላል። ማቴ ፱፥፳፯። ጥሩ የትዳር ጓደኞችም እንደ ዓይን ናቸው። ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል የትዳር ጓደኛን በዓይን መስሎ ተናግሯል። ማቴ ፲፰፥፱። በተጨማሪም የሰውነት መብራት ዓይን እንደሆነ፥ ዓይን ብሩህ ከሆነ ሰውነት ሁሉ ብሩህ እንደሚሆን ዓይን ግን ታማሚ ከሆነ ሰውነት ሁሉ ጨለማ እንደሚወርሰው ተናግሯል። ማቴ -፥፳፪። ስለዚህ ትዳራችን በውስጥ በአፍአ ብርሃን እንዲሆን ዓይን የሆነ የትዳር ጓደኛ እንዲሰጠን በእምነት ከለመንነው ይሰማናል። ልመናችንን እንደሰማን ካወቅንና ካመንን የለመንነውን ሁሉ በጊዜው ይሰጠናል።

፯፦ ፈቃደ እግዚአብሔርን እንዴት ማወቅ ይቻላል?

          «ፈቃደ እግዚአብሔርን እንዴት ማወቅ ይቻላልየሚለው የሰው ሁሉ ጥያቄ ነው። ብዙዎቻችን መመዘኛችን ሥጋ በመሆኑ ፈቃደ እግዚአብሔርን ለማወቅ፥ ለመቀበልም እንቸገራለን። የሚነገረው ሁሉ ለኅሊናችን መልስ ስለማይሆን አጥ ጋቢ መልስ አላገኘሁም እንላለን። ለምሳሌ፦ ከአይሁድ የተላኩ ካህናትና ሌዋውያን፦ መጥምቀ መለኰት ቅዱስ ዮሐንስን፦ «እንኪያስ አንተ ማነህ? አንተ ኤልያስ ነህንባሉት ጊዜ፦ «አይደለሁም » ብሏቸዋል። ዮሐ ፩፥፳፩። ነቢዩ ኤልያስ በእሳት ሠረገላ ወደ ሰማይ ቢያርግም በስሙ የተነገረ « እነሆ፥ ታላቋና የምታስፈራው የእግዚአብሔር ቀን ሳትመጣ ቴስብያዊው ኤል ያስን እልክላችኋለሁ።» የሚል ትንቢት አለ። ሚል ፬፥፭። ይኽንን ይዘው ነው፥ «ኤልያስ ነህንያሉት። ዮሐንስ «አዎን ነኝ፤» ማለት ይችል ነበር። ምክንያቱም ጌታችን «ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይህ ነው።» በማ ለት እንደመሰከረለት በሁሉ ኤልያስን ይመስለዋልና። ማቴ ፲፩፥፲፬። ነቢዩ ኤልያስ፦ ፀጉራም ፥ጸዋሚ ፥ተሐራሚ፥ ዝጉሐዊ፥ ባሕታዊ ድንግላዊ ነው። ቅዱስ ዮሐንስም ልብሱ  የግመል ፀጉር ሆኖ፦ ጸዋሚ ተሐራሚ ዝጉሐዊ ፥ባሕታዊ ድንግ ላዊ ነው። ይሁን እንጂ «አይደለሁም፤» ያለው፦ «ነኝ፤» የሚለው እውነት ለአይሁድ ለኅሊናቸው መልስ ስለማይሆን ነው። ለእኛም ስለ ፈቃደ እግዚአብሔር የሚነገረው እውነት ሁሉ ለኅሊናችን መልስ አይደለም።
          ፈቃደ እግዚአብሔርን ለማወቅ በሕግ በአምልኮ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ያስፈልጋል። ቅዱስ ዳዊት፦ «ወደ እር ቅረቡ ያበራላችሁማል ፥ፊታችሁም አያፍርም፤» ያለው ለዚህ ነው። መዝ ፴፫ ፥፭። ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብም፦ « እግ ዚአብሔርን ቅረቡት ይቀርባችሁማል፤» ብሏል። ያዕ ፬፣፰። ከዚህም ሌላ፦ የእኛ ሥጋዊ ፈቃድ ከእግዚአብሔር መንፈሳዊ ፈቃድ ፈጽሞ የተለየ መሆኑን ማስተዋል ያስፈልጋል። ይኽንን በተመለከተ ነቢዩ ኢሳይያስ፦ ሐሳቤ እንደ ሐሳባችሁ መን ገዴ እንደመንገዳችሁ አይደለምና ይላል እግዚአብሔር። ሰማይ ከምድር እንደሚርቅ እንዲሁ መንገዴ ከመንገዳችሁ ሐሳቤም ከሐሳባችሁ የራቀ ነው።» በማለት ከእግዚአብሔር የሰማውን ተናግሯል። ኢሳ ፶፭ ፰። በመሆኑም ለራሳችን ስንል፦ ፈቃደ ሥጋችንን እና የዓይን አምሮታችንን ትተን ለፈቃደ እግዚአብሔር መገዛት አለብን። ምክንያቱም ሁልጊዜ ፈቃደ እግዚአብሔርን እንዳናውቅ የሚጋርደን ፈቃደ ሥጋችን ነውና። ለበጎ ነገር ሁሉ አብነት የሆነን አምላክ ኢየሱስ ክርስ ቶስ «አባቴ ሆይ፥ የሚቻልስ ከሆነ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፤ ነገር ግን ፈቃድህ ይሁን እንጂ የእኔ ፈቃድ አይደለም።» ብሏ ል። ማቴ ፳፮፥፴፱። ይህም ለእኛ አብነት ለእኛ አርአያና ምሳሌ ሲሆን ነው። እንግዲህ ጌታ እንዳስተማረን የራሳችንን ፈቃ ስንተው ያን ጊዜ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የምናውቅበት ልቡና የምናይበት ዓይን የምንዳስስበት እጅ ይኖረናል። የእግ ዚአብሔር ፈቃድ ሁልጊዜ ለእኛ መልካም ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ « እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያ ሰጨንቃችሁን ሁሉ በእርሱ ላይ ጣሉ።» ያለው በጎ ፈቃዱን ነው። ፩ኛ ጴጥ ፭፥፯። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ፦ « እግዚአብሔር ቅርብ ነው፤ በምንም አትጨነቁ፤ ነገር ግን በሁሉ ነገር ጸልዩ ማልዱም፤ እያመሰገናችሁም ልመናችሁን ለእግ ዚአብሔር ግለጡ።» ብሏል። ፊል ፬፥፭።

          ፈቃደ እግዚአብሔርን ለማወቅ የምንጓዝበት መንገድ መንፈሳዊ መሆን አለበት። ኢያቡር የተባለ የአብርሃም ሎሌ ለይስሐቅ ሚስት አጭቶ እንዲያመጣ በተላከ ጊዜ፦ « የጌታዬ የአብርሃም አምላክ እግዚአብሔር ሆይ፥ እለምንሃለሁ፤ መንገዴን ዛሬ በፊቴ አቅናልኝ ለጌታዬ ለአብርሃም ምሕረትን አድርግ። እነሆ ፥በዚህ የውሃ ምንጭ አጠገብ እኔ ቆሜአለሁ የዚችም ከተማ ሴቶች ልጆች ውኃውን ሊቀዱ ይመጣሉ፤ ውኃ እጠጣ ዘንድ እንስራሽን አዘንብዪ የምላት፤ እርስዋም አንተ ጠጣ ግመሎችህን ደግሞ አጠጣለሁ የምትለኝ ቆንጆ እርስዋ ለባሪያህ ለይስሐቅ ያዘጋጀሃት ትሁን፤ በዚህም ለጌታዬ ምሕረትን እንዳደረግህ አውቃለሁ።» ሲለ ተንበርክኮ ጸለየ። ወዲያው ርብቃ መጣችና የተባለችውን ሁሉ በበጎ ኅሊና ፈጸመች። እርሱም ትክ ብሎ ይመለከታት ነበር። ማንነቷን እና በአባቷ ቤት ማደሪያ እንዳለ በጠየቃት ጊዜም፦ «እኔ ሚልካ ለናኮር የወለደችው የባቱኤል ልጅ ነኝ። በእኛ ዘንድ ገለባና ገፈራ የሚበቃ ያህል አለ፥ ለማደሪያም ደግም ሥፍራ አለን፤ » አለችው። ይህን ሁሉ ያደረገችው በበጎ ኅሊና በጎ መሥራት እንደሚገባ አምና እንጂ ለትዳር እመረጣለሁ ብላ አይደለም። እርሱም፦ «ቸርነቱንና እውነቱን ከጌታዬ ያላራቀ የጌታዬ የአብርሃም አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን እኔ በመንገድ ሳለሁ እግዚአብሔር ወደ ጌታዬ ወንድሞች መራኝ፤» ብሎ አመሰገነ። ዘፍ ፳፬፥፩-፳፯።

፰፦ ሦሰቱ ዓላማዎች፤

          ከላይ ለመግለጥ እንደሞከርነው የትዳር ዋና ዋና ዓላማዎች ሦስት ናቸው። በመሆኑም ሦስቱም መሟላት አለባ ቸው። ብዙ ሰዎች ወደ ትዳር ዓለም የሚገቡት በጎዶሎ ዓላማ ነው። ለምሳሌ፦ ትዳርን ለፍትወተ ሥጋ ብቻ የሚፈልጉ ሰዎ አሉ። በእነርሱ ዘንድ፦ መረዳዳትና ልጅ መውለድ ቦታ የለውም። ትዳርን ለፍትወተ ሥጋና ስም የሚያስጠራ ልጅ ለመው ለድ ብቻ የሚፈልጉ ሰዎች አሉ። በእነርሱ ዘንድ መረዳዳት ፈጽሞ አይታሰብም። ትዳርን እንደ ምንም ብለው ልጅ ለመውለ ብቻ የሚፈልጉ ሰዎች አሉ። በእነርሱ ዘንድ ፍትወተ ሥጋና መረዳዳት ትርፍ ነገር ነው። ትዳርን ተረዳድቶ ኑሮን ለማሸነፍ ብቻ የሚፈልጉ ሰዎች አሉ። በእነርሱ ዘንድ ፍትወተ ሥጋና ልጅ መውለድ እንደ ዋና ነገር አይታይም። በአብዛኛው ሰው ዘንድ  በፍትወተ ሥጋ ያለመስማማት ችግር አለ። አንደኛው ሲፈልግ ሌላኛው ግድየለሽ ይሆናል። በዚህን ጊዜ አለመተማመን ይነግሣል። ልጅ በመውለድም ጉዳይ አለመደማመጥ አለ። አንደኛው እንድገም ሲል ሌላው አንድ ወይም ሁለት ብቻ ይበቃናል ይላል። ከመረዳዳት አንፃርም ፍጹም የሆነ ስምምነት የለም። መረዳዳቱ ከራሳቸውም አልፎ እስከ ቤተሰብ ድረስ ስለሚዘልቅ፦ «ለራስህና ለቤተሰብህ ታደላለህ ለራስሽና ለቤተሰብሽ ታደያለሽ » የሚል ጭቅጭቅና ንዝንዝ ትዳሩን ሲኦል ያደርገዋል። ስለዚህ በሦስቱም የትዳር ዓላማዎች እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንደ ቃል ተናጋሪ ለመሆን ከላይ ከሰማይ እግዚአብሔርን መለመን ያስፈልጋል። ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ፦ «የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ አትሳቱ በጎ ስጦታ ሁሉ ፍጹምም በረከት ሁሉ ከላይ ናቸው።» ያለው ለዚህ ነው። ጋብቻንም ክቡር የሚያሰኘው ከላይ የሚሰጥ የእግዚአብሔር ስጦታ በመሆኑ ነው። ስለሆነም፦ «መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል።» የሚለውን ዘንግተን የልማድ ልናደርገው አይገባም። ዕብ ፲፫ ፬።



ምንጭ : http://www.betedejene.org
 

No comments:

Post a Comment