Thursday, May 23, 2013

ጻድቁ አቡነ አረጋዊ



እኚህ አባት ከተሰሐቱ ቅዱሳን (ከሮምና ኤሽያ ከመጡት ከ9 ቅዱሳን አባቶች አንዱ ሲሆኑ አባታቸው ይስሐቅ የሮም ንጉስ ነበር፡፡ እናታቸው ንገሰተ እደና ትባላለች፡፡ የመጀመሪያ ስማቸው ዘሚካኤል ነው፡፡ ጥበብ መንፈሳዊ ሲማሩ አድገው ወደ እሰከነድረያ ኮብልለው ገዳም ገቡ፡፡ አበምኔቱ አባ ጳኩሚስ በፈቃደ እግዚአብሔር የመጡ መሆናቸውነ አውቀው መዓርገ ምንኩስና ሰጥተዋቸዋል፡፡
ንጉስ የሆኑ ቤታቸው የሞቀ ቤተ ሰቦቻቸውነ ንቀው ትተው ገዳም ገብተው በምንኩስና ተወስነዋል፡፡ አበምኔቱም ወደዚህች የሕየወት መንገድ ስለመራሀን ብፁህ አረጋዊ መባል ይገባሃልብለዋቸዋል፡፡ አረጋዊ የተባሉት ከዚያ ወዲህ ነው፡፡ አባታችን በተጋድሏቸውም ከአባ እንጦንስ፣ ከአባ ጳውሊ እና ከአባ መቃርስ ቀጥሎ በአራተኛ መዐረግ አበ መነኮሳት ሆነው ተመርጠዋል። በገዳመ ዳውናስ 7 ዓመት ከቆዩ በኋላ ወደ ሮም ተመልሶ ሲያስተምሩየሀገራችንን ዜና ሰምተው ለመምጣት በ480 ዓ.ም ከአባ ፍሪሚናጦስ ቦ|ላ መንገድ ጀመሩ፡፡ ቅዱስ ሚካኤል በክነፉ ተሸክሞ አክሱ አድርሷቸዋል፡፡ ተመልሶ ሄደው ስለ ኢትዮጵያ ቅድስት ሀገር መስክረዋል፡፡ ሐዋርያ ሳይላክላት በሃይማኖት በምግባር ጸንታ ትኖራለች ብለው ለሰባቱ ዘመዶቻቸው አበውመነኮሳት ነገሯቸው፡፡ ስምንቱ ሁሉ ጓዛቸውን ጠቅልለው በሮም ነግሶ የነበሩ ይስሐቅን (አባ ገሪማን) ጨምረው ንጉስ አልአሜዳ በነገሰ በአምስተኛ ዓመት ማለትም በ480 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ራሳቸውን ዘጠኝ ሆነው መጥተዋል፡፡ አባ አረጋዊ እናታቸው ቅድስት እድናን ደቀመዝሙራቸውን ማትያስን አስከትለው እግረመንገዳቸውን እያስተማሩና ድውያንን እየፈወሱ ደብረ ዳሞ ደረሱ፡፡ ከእግረ ደብር ሆነው አሁን ይህን ተራራ በምን ልወጣው እችላለሁ እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ በንግግሩ ሐሰት የሌለበት አምላካችን በነቢዩ ዳዊት ላይ አድሮ በመዝሙር 90/91፡11-16 ላይ “በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል። በተኵላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ። እንዳለው የታዘዘ ዘንዶ መጥቶ ስደሳ ክንድ በሚያህል ጅራቱ ጠምጥሞ ቅዱስ ሚካኤል ሰይፈ እሳት ይዞ እየጠበቃቸው ከተራራው አናት አድርሷቸዋል፡፡
ወዲያው ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ብለው አመስግነዋል፡፡ ቦታውም ደብረ ሃሌ ሉያ ተብሏል፡፡ በዚያ ዕለት ግማሽ ህብስት በልተው ጠገቡ፤ ከዚያ በኋላ ግን ምድራዊ ሕብስት አልተመገቡም፡፡ በሰንበተ ክርስታያን ከቅዳሴ በኋላ ሕብስተ ሰማያዊ እያመጡላች ይመገቡ ነበር እንጂ፡፡ ኋላ ግን ዜና ጽድቃቸውን ሰምተው ከስድስት ሺህ ያላነሱ ደቀ መዛሙርት ተሰብስበውላቸዋል፡፡ ዘጠና ዘጠኝ አመት ሲሞላቸው ጌታ በመንፈቀ ለሊት ተገልጾ ምድራዊ መንግስትህን ትተህ ስላገለገልከኝ ህልፈት ሽረት የሌለባት ሰማያዊ መንግስቴን አወርሰሃለሁብሎ ቃልኪዳን ሰጣቸው፡፡ በስምህ የተማጸነውን እስከ አስራ አምስት ትውልድ ድረስ እምርልሃለሁ አንተም ከሞት ገጽ ትሰወራለህ ብሎ ተስፋቸውን ነገራቸው፡፡ እሳቸው መነኮሳቱን ሰብስበው ከእንግዲህ በሥጋ አታዩኝም ብለው ነግረዋቸው አበምኔት (የገዳም አባት ወይም አለቃ) ሾመውላቸው ጥቅምት አሥራ አራት ቀን በዚያው በደብረ ዳሞ ተራራ በስተምስራቅ አቅጣጫ እንደሄኖክ እንደ ኤልያስ ተሰውሯል፡፡

በረከታቸው፣ ቃልኪዳናቸው፣ አማላጅነታቸው በሁላችን ይደር አሜን።

No comments:

Post a Comment