Wednesday, May 29, 2013

ግንቦት 17


በዚህች ቀን ታላቁ የቤተክርስቲያን አባት አባ ኤጲፋንዮስ አረፈ። ወላጆቹ ክርስቶስን የማያምኑ አይሁዳውያን ናቸው በዛ ላይ እጅግ በጣም ድሆች ፤አባ ኤጲፋንዮስ ክርስቶስን ያመነው ክርስትናን የተቀበለው ሁለት ታአምራቶችን አይቶ ነው፤ አንደኛው እርሱ እናቱና እህቱ ርሃብ ሲጠናባቸው የአባቱን አህያ ሊሸጥ ገብያ ሄደ አህያው በጣም አስቸጋሪ ነበርና አንዱን... ገብያተኛ ጭኑን ረግጦ ይገድለዋል፤በዚያ አካባቢ አባ ፊሎንዲስ የሚባል የበቃ ባህታዊ ነበር በመስቀል አማትቦ በክርስቶስ ስም ተነስ ይለዋል የሞተው ሰው ተነሳ፤ሁለተኛ ይኸው ባህታዊ መንገድ ሲሄድ ኤጲፋንዮስ ከኃላው ይከተለዋል አንድ ድሃ ቀርቦ ስመ እግዚያብሔርን ጠርቶ ምጽዋት ይጠይቀዋል የሚሰጠው ነገር ቢያጣ የለበሰውን ልብስ ( አጽፍ ) አውልቆ ሲሰጠው ወዲያውኑ ብርህት ልብስ ( አጽፍ ) ከሰማይ ሲወርድለት አየ፤ ከዚህ በኃላ ነው ኤጲፋንዮስ ቀርቦ አባቴ የሞተውን ሰው ያስነሳህበት አሀን ደግሞ ይህ ደሃ የክርስቶስን ስም ቢጠራብህ ልብስህን ስትሰጠው ከሰማይ ሌላ ልብስ የወረደለህ የኔ ዘመዶች ሩቅ ብእሲ ብለው ሰቅለው የገደሉት ክርስቶስ ነውን አለው አዎን ይለዋል አጥምቀኝ አለው አጠመቀው እንዳንተ መነኩሴ መሆን እፈልጋለሁ ይለዋል ካልክስ ብሎ ከሰው ተለይቶ በገዳም የሚኖር የበቃ አባት ነበር ኤላርዮስ ይባላል ወደ እርሱ ይልከዋል አመነኮሰው በተጋድሎም መኖር ጀመረ ትምህርት ታአምራቱም በተለያዩ አገሮች ተሰማ መናፍቃንን ተከራክሮም የሚረታ ሆነ ድውያንን የመፈወስ አጋንንትን የማውጣት ስልጣን ተሰጠው፤ ደግነቱን የተመለከቱ አባቶች የቆጵሮስ ኤጲስ ቆጶስ አድርገው ሾመውታል በዚህ በሹመቱ ወራት ብዙ ድርሳናትን ተግሳጻትን ጽፏል፤ አንድ ቅዳሴም ደርሷል ቅዳሴ ኤጲፋንዮስ የሚባል ይህ ቅዳሴ በተለይ በክረምት ወራት ቤተክርስቲያን የሚያዝወትሩ ከሆነ ደጋግመው ይሰሙታል ስለ ደመናት ስለ ነጎድጓድ ስለ ዝናብ በስፋት ይናገራል፤ ለጸሎተ ሐሙስም ይቀደሳል። ያ ደገኛ የተዋህዶ ኩራት ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ የድሃይቱን መበለት ርስት የነጠቀችውን ንግስት አውዶክስያን ከቤተክርስቲያን እንዳትገባ፤ እንዳትቆርብ፤ ከምዕመናን ጋር እንዳትገናኝ አውግዞ ሲለያት ለአባ ኤጲፋንዮስ መልዕክት ትልክበታለች ዮሐንስ አፈወርቅ ከግዝቱ ካልፈታኝ የአባቶቼን ዘመን እመልሳለሁ አብያተ ጣኦታት እንዲከፈቱ አብያተ ክርስቲያናት እንዲዘጉ ክርስቲያኖች እንዲሰደዱ አዋጅ አስነግራለሁ አለችው አባ ኤጲፋንዮስ ወደ ዮሐንስ አፈወርቅ ሄዶ እንዲህ ብላለች ሴትዮዋ ሰይጣን አድሮባታል ከማድረግ ወደ ኃላ አትልም ከግዝቷ ፍታት ይለዋል፤ እርሷ የአባቶቿን ዘመን ብትመልስ እኔስ ብሆን ልጆቼስ ምዕመናን ቢሆኑስ እንደአባቶቻችን በሰማዕትነት መሞት ያቅተናልን፤ ያሻትን ታድርግ ለእርሷ ይብስባታል ከግዝቷ አልፈታትም ይለዋል፤ከዚህ በኃላ አባ ኤጲፋንዮስ ዮሐንስን ተሰናብቶ ወደ አገሩ ሊመለስ ሲል አገርህ አትደርስም ከመንገድ አንበሳ ሰብሮህ ትሞታለህ ይለዋል፤ አባ ኤጲፋንዮስም አንተም እንጂ መቼ መሞት ይቀርልሃል በደሴተ አጥራክያ ተግዘህ ተንገላተህ ትሞታለህ ይለዋል፤ አሁን ሁለቱ ተጣልተው አይደለም ክብራቸውን ሲገልጽ እንጂ አንዱ የአንዱ ሞት ተገልጾለት እንዲህ ተናገሩ፤ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳለውም አባ ኤጲፋንዮስ መንገድ ላይ አንበሳ ገድሎታል ይህም ግንቦት 17 ቀን ነው ለ 40 ቀን አልተቀበረም የሚገርም መአዛ ግን ከስጋው ይወጣ ነበር ብዙ ድውያንም ተፈውሰዋል፤ዮሐንስ አፈወርቅም ንግስቲቱ በግዞት አሰቃይታ ገድላዋለች ይህም ግንቦት 12 ቀን ነው፤ ዮሐንስ አፈወርቅ ጠፍቶ የነበረውን የዮሐንስን ራእይ መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት ድጋሚ የጻፈው በዚህ በደሴተ አጥራክያ በግዞት ሳለ ነው። ከዮሐንስ ራእይ ውስጥ የዮሐንስ አፈወርቅ ቃል የሆነው ይህ ብቻ ነው “ማንምም በዚህ በትንቢት መጽሐፍ ከተጻፉት ቃሎች አንዳች ቢያጎድል፥ በዚህ መጽሐፍ ከተጻፉት ከሕይወት ዛፍና ከቅድስቲቱ ከተማ እግዚአብሔር ዕድሉን ያጎድልበታል።” ዮሐ 22፤19። ከአባቶቻችን በረከት ያሳትፈን።

No comments:

Post a Comment