Sunday, July 13, 2014

ሐምሌ 2

በዚህች ቀን ከ 12ቱ ሐዋርያት አንዱ የሆነው ሐዋርያው ታዲዎስ አረፈ። ዓለምን ዞራችሁ ለፍጥረት ሁሉ ወንጌልን ስበኩ በተባሉት መሰረት ሐዋርያት ዓለምን በእጣ ሲከፋፈሉ ለዚህ ሐዋርያ ሶርያ ደረሰችው፤ ዛሬ የእርስ በእርስ እልቂት ያለባት አገር፤ ይህ ሐዋርያ እጅግ ድንቅ ታአምራት በሶርያ ምድር አድርጓል፤ ነገሩ እንዲህ ነው፤ አንድ ትዕቢተኛ ሰይጣን ያደረበት ባለጸጋ ቀርቦት መምህር ሆይ በመጽሐፍ ቅዱሳችሁ ሀብታም መንግስተሰማያት ከሚገባ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል ይላል፤ እስኪ መጽሐፍ ቅዱሳችሁ እውነት ከሆነ አድርገህ አሳየን ይለዋል፤ ሐዋርያው ታዲዎስም መርፌ የሚሰራ ባልንጀራ ነበረውና መርፌ እንዲልክለት ሰው ይሰዳል ያ መርፌ ሰሪም ሐዋርያውን ለመርዳት አስቦ ቀዳዳውን ትንሽ አስፍቶ ይልክለታ፤ ታዲዎስም ፈገግ አለ የመርፌ ቀዳዳ ምን ቢሰፋ እንዴት ግመል ያሳልፋል ስለውለታህ አመሰግናለው ትክክለኛውን መርፌ ላክሊኝ ብሎ ይመልስለታል እርሱ ድጋሚ አስተካክሎ ይልክለታል፤ ከዚህ በኃላ አገሬው በአደባባይ ተሰበሰበ ጭነት የያዘች ግመልና አንድ ነጋዴም ተዘጋጁ ሐዋርያው ዓይኑን ወደ ሰማይ ቀና አድርጎ አምላኬ ሆይ ይህን የማደርገው ክብርህ እንዲገለጽ እንጂ ክብሬ እንዲገለጽ ብዬ አይደለም ጸሎቴን ስለሰማኸኝ አመሰግንሃለው አለ፤ ጸሎቱን እንደጨረሰ ጭነት የተሸከመችውን ግመል እንድታልፍ አደረጋት ሰው ሁሉ እያያ በመርፌው ቀዳዳ ሾለከች አገሬው እልልታውን አቀለጠው ለሁለተኛ ጊዜ ለሶስተኛ ጊዜም እንድትሾልክ አደረገ፤ ህዝቡ ይህን የእግዚያብሔር ድንቅ ተአምራት አይቶ ብዙዎች አመኑ ተጠመቁም፤ ዓለም ከተፈጠረ ዘመን ከተቆጠረ እንደዚህ ያለ ተአምራት ያየ ማን አለ እኛ ግን ከሶርያ ህዝብ ጋር አየን ተመለከትን፤ በመጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ እንዳለ " በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ያደርጋል ከእኔም በላይ ያደርጋል" ግሩም ነው የፈጣሪ ስራ። ሐዋርያው ቅዱስ ታዲዎስ በብዙ አገር ተዘዋውሮ ሲያስተምር ጣኦት አምላኪዎች ይዘው አሰቃዩት በዛሬዋ ቀንም ገድለውታል እርሱም የሰማዕትነት አክሊል ተቀብሏል። ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ከሐዋርያው በረከት ያሳትፈን። ስንክሳር፤ ገድለ ሐዋርያት።

No comments:

Post a Comment