Sunday, May 12, 2013

ዳግም ትንሣኤ

              ዳግም ትንሣኤ የተባለበት ምክንያት፡- በኣከባበር፥ በሥርዓት የመጀመሪውን ትንሣኤ ስለሚመስል ነው፡፡ የትንሣኤ ዕለት የሚባለው ቃለ እግዚአብሔር ሳይለወጥ፤ በሙሉ በዚህ ቀን ይደገማል፡፡ ከዚህም ሌላ ሁለት መጠሪያ ስሞች አሉት፡፡ እነዚህምፈጸምነ አግብኣተ ግብርይባላሉ፡፡ፈጸምነየተባለበትም፤ የሰሙነ ትንሣኤን በዓል አክብረን ፈጸምን ማለት ነው፡፡አግብዖተ ግብርየተባለበትም፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስአባ ወአቡየ ግብር ዘወሀብከኒ ፈጸምኩ...እኔ ልሠራው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር ላይ አከበርሁህያለውን ከቅዳሴ በኋላ ሊቃውንት በዚህ ቀን ስለሚዘምሩት ነው፡፡ ዮሐንስ ፲፯፥፬


     
በተጨማሪም የሐዋርያው ቶማስ ምስክርነት የሚታሰብበት ነው፡፡ ዳግመኛ ከስምንት ቀን በኋላ ደቀ መዛሙርቱ በዝግ ቤት ሳሉ፥ ቶማስም ከእነርሱ ጋር ሳለ ደጁም ተዘግቶ ሳለ፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ በመካከላቸው ቁሞ እንዴት ሰነበታችሁ! አስታረቅኋችሁአላቸው፡፡ ሁለት ሰዓት አሳልፎ ስለመጣእምድኅረ ሰሙንአለ እንጅ፥ በስምንተኛ ቀን ሲል ነው፡፡ በመጀመሪያው መገለጡ ያልተገኘው ሐዋርያው ቶማስ ትንሣኤውን አላመነም ነበርና፤ጣትህን ወደዚህ አምጣ እጆቼንም እይ፤ እመን እንጅ ተጠራጣሪ አትሁንአለው፡፡ ቶማስም መለሰጌታዬ አምላኬ ሆይአለ፡፡ መዳሰሱን ሲያይጌታዬ ማቃጠሉን ሲያይአምላኬአለ፡፡ ገቦ መለኮቱን የዳሰሰች እጁ ሕያዊት ሁና፤ (በሕይወት ትኖራለች) በሕንድ አገር ከታቦት ጋር በመንበሩ ላይ ያስቀምጧታል፡፡ በዓመት በዓመት በእመቤታችን በዓል በአሰተርእዮ ሊያጥኑ ሲገቡ፥ የሚሾመውን ወጥታ ቀኝ እጁን ትይዘዋለች፤ ዓመት አገልግሎ ያረፋል፤ እንዲሁ በዓመቱ የሚሾመውን ተራምዳ ትይዘዋለች፤ እንዲህ እያለች ትኖራለች፡፡ ይህም የሚያስተምረን የጌታን ተአምራት፤ የሐዋርያውን ሥልጣንና ብቃት ነው፡፡ጌታም ቶማስ ሆይ! ብታየኝ አመንክን? ሳያዩኝ የሚያምኑብኝ ብፁዓን ናቸው አለው፡፡ ዮሐ ፳፩፥፳፬-፳፱ ለብርሃነ ትንሣኤው ያደረሰን አምላካችን፥ እስከ ፍጻሜ ሕይወታችን በሃይማኖት የቀናን፤ በምግባር የጸናን ያድርገን! አሜን፡፡


                                         
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
                                              
ወለወላዲቱ ድንግል 

                                                      ወለመስቀሉ

Wednesday, May 8, 2013

ልደታ ለማርያም


https://www.youtube.com/watch?v=0sLPIlNzzXU&index=22&list=PL8EZ6DqhsFd6egHODWkiOYLhVqUnZ6RgD&t=1s









ጴጥርቃ እና ቴክታ የሚባሉ ሰዎች በኢየሩሳሌም በአንድነት ተጋብተው ይኖሩ ነበር:እነዚህም በእግዚአብሄር የሚያምኑ የተወደዱ ጻድቃን ደግ ሰዎች ነበሩ:እነዚህም ሰዎች በእግዚአብሄርም በሰውም ዘንድ የበቁ ባለጸጎች ነበሩ:ነገር ግን የሚወርሳቸው ልጅ አልነበራቸውምና መካን ነበሩ:አንድ ቀን ጴጥርቃም ቴክታን እህቴ ሆይ ይህን ሁሉ የሰበሰብነውን ገንዘባችንን ምን እናደርገዋለን ልጅ የለን የሚወርሰን:አንቺም መካን ነሽ እኔም ካንቺ በቀር ሌላ ሴት አላውቅም አላት:እርሱአም ወንድሜ ሆይ አምላከ እስራኤል ለኔ ልጅ ቢነሳኝ አንተም እንደኔው ሆነህ ትቀራለህን? ከሌላ ደርሰህ ውለድ እንጂ ብላ ብታሰናብተው እንደዚ ያለ ነገር እንኩአንስ ላደርገው በልቦናዬ እንዳላስበው አምላከ እስራኤል ያውቅብኛል አላት:እሱአም አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን የሚያውቅ የለም:ትላንትና ማታ በህልሜ ነጭ ጥጃ ከማህጸኔ ስትወጣ ያችም ነጭ ጥጃ ሌላ ነጭ ጥጃ ስትወልድ እንዲሁ እስከ 7ት ትውልድ ሲዋለድ ሰባተኛይቱ ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋም ፀሃይን ስትወልድ አየሁ አለችው::
እርሱም በጠዋት ከህልም ፈቺ ዘንድ ሂዶ የነገረችውን ሁሉ ነገረው:ያም ህልም ፈቺ እግዚአብሄር በምህረቱ አይቱአቹአል በሳህሉ መግቡአችሁአል 7 አንስት ጥጆች መውለዳቹ 7 ሴቶች ልጆች እና የልጅ ልጆች ትወልዳላቹ ከቤታቹ ሰባተኛይቱ ጨረቃ መውለዱአ ከሰው የበለጠች ከመላእክትም የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላቹ የፀሃይ ነገር ግን አልታወቀኝም አለው:እርሱም የነገረውን ሁሉ ሄዶ ነገራት እርሱአም እንጃ አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን ማን ያውቃል ብላ ዝም አለች:ከዛም ፀንሳ በ9 ወሩአ ሴት ልጅ ወለደች:ስሙአንም ሄሜን ብለው አወጡላት:ሄሜንም አድጋ ለአካለ መጠን ስደርስ አጋብተዋት ሴት ልጅ ወለደች በስምንተኛ ቀኑአም ደርዲ ብለው ስም አወጡላት:ደርዲም አድጋ እንዲሁ ሴት ወለደች እና ቶና አለቻት:ቶናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሲካር አለቻት;ሲካርም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሴትና አለቻት:ሴትናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሄርሜላ አለቻት:ሄርሜላም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ንጽህት ቅድስት ክብርት የምትሆን እመቤታችንን የምትወልደውን ሃናን ወለደች::
ከጴጥርቃና ከቴክታ የተወለዱ 67 ወንዶች ልጆች አሉ የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ትውልድ ለመቁጠር ትንቢት አልተነገረላቸውም ሱባኤ አልተቆተረላቸውምና አልተፃፈም:ይህቺም ሃና በስራት በቅጣት አደገች:ለአእምሮ ስትበቃ አካለ መጠን ስደርስ ከቤተ መንግስት ወገን ከነቅዱስ ዳዊት ወገን ከሆነው(መጽሃፍ ቅዱስ ይገልጸዋል) ከቅዱስ እያቄም ጋር አጋቡአት::እነዚህ ቅዱሳን እያቄም እና ሃና በአንድነት ተጋብተው ሲኖሩ ልጅ አጡ:ከእለታት አንድ ቀን ወደ ቤተ እግዚአብሄር ሂደው ሲፀልዩ ሲያዝኑ ዋሉ:ሃዘናቸው እንዴትስ ነው ቢሉ:እያቄም:-"አቤቱ ጌታዬ ያባቶቼ የእስራኤል አምላክ እኔ ባርያህ እለምንሃለው አትጣለኝ:አትናቀኝ:ፀሎተን ስማኝ ፈቃዴን ፈጽምልኝ:ለአይኔ ማረፊያ ለልቤ ተስፋ የሚሆን የተባረከ ወንድ ልጅ ስጠኝ" ብሎ ሲለምን ዋለ:ሃናም በበኩሉአ "አቤቱ ጌታዬ የአባቶቼ የእስራኤል አምላክ እኔ ባርያህ እለምንሃለው:ስማኝ ለአይኔ ማረፊያ ለልቤ ተስፋ የምትሆነኝ የተባረከች ሴት ልጅ የማህፀኔን ፍሬ ስጠኝ" ብላ ስትለምን ዋለች: እንዲ ብለው ስይዝኑ ሲጸልዩ ውለው ርግብ ከልጆቹአ ጋር ስትጫወት አይታ አቤቱ ጌታዬ ለዚች ግእዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሳኅኝ ብላ ምርር ብላ አለቀሰች:እንዲ ብለው ሲያዝኑ ሲፀልዩ ውለው ከዘካርያስ ከሊቀ ካህናቱ ሄደው አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሄርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን:ሴት ልጅም ብንወልድ ማይ ቀድታ መሶብ ወርቅ ሰፍታ መጋረጃ ፈትላ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን ብለው ስለት ገቡ::
ዘካርያስም እግዚአብሄር ጸሎታችሁን ይስማላቹ ስእለታችሁን ይቀበልላቹ ጻህቀ ልቦናችሁን ይፈጽምላቹ ብሎ አሳረገላቸው:
ከዚያም በሁአላ ቅድስት ሃና እና ቅዱስ እያቄም እለቱን ራእይ አይተው ነገር አግንተው አደሩ:ራእዩም እንዴት ነው ቢሉ ኢያቄም 7ቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ አላት:ወፍ የተባለው ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው:ነጭነቱ ንጽሃ ባህሪው ነው:ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ማለቱ:የኢያቄምን ባህርይ ባህርይ እንዳደረገው እወቅ ሲል ነው:7ቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ልዩ ልዩ ባህሪው:ምልአቱ:ስፍሃቱ:ርቀቱ:ልእልናው:ዕበዩ መንግስቱ ናቸው:ሃናም እኔም አየሁ አለችው:ምን አየሽ ቢላት:ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማህጸኔ ስትተኛ አየሁ አለችው::ርግብ የተባለች እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት:ነጭነቱአ ንጽህናዋ:ቅድስናዋ ድንግልናዋ ነው:ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማህጸኔ ስትተኛ አየሁ ማለቱአ ብስራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችንን መፀነሱአ ነው:ይህንኑም ራእይ ያዩት ሃምሌ 30 ዕለት ነው::
እነሱም እንዲ ያለ ራዕይ ካየን:ነገር ካገኘን ብለው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም:ፈቃደ እግዚአብሄር ቢሆን ብለው አዳምንና ሄዋንን ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት ብሎ ያበሰረ አምላክ ለኛስ ይልክልን የለምን? ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ 7 ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ:ነሃሴ በባተ በሰባተኛው ቀን ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ዓለሙ ሁሉ ተሰብስቦ ቢመዘን አንድ የራሱአን ፀጉር የማያህል ደግ ፍጥረት ትወልዳላቹህና ዛሬ በሩካቤ ስጋ ተገናኙ ብሎአቹሃል ጌታ ብሎ መልአኩ ለሃና ነገራት በፈቃደ እግዚአብሄር በብስራተ መልአክ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም እሁድ እለት ተፀነሰች(በኦሪት ስርአት እሁድ ዕለት ባል እና ሚስት መገናኘት ልማድ ነበርና):እመቤታችን የተፀነሰች ዕለት አይሁድ ቀንተው ተነሱባቸው ቅናቱ እንዴት ነው ቢሉ:ሳሚናስ የሚባል የጦሊቅ ልጅ ከኤዶቅ ካጎቱ ቤት ሄዶ ሞተ እነርሱም እንቀብራለን ብለው ባልጋ ይዘው ሲሄዱ ከመንገድ አሳረፉት:የሃናም የአጎቱአ ልጅ ነበርና ለማልቀስ ብትደርስ ዘመዶቹአ ሁሉ ተሰብስበው ሲላቀሱ ቆዩአት:እርሱአም አብራ እየዞረች ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ብድግ ብሎ ተነስቶ ስብሃት ለኪ ማርያም እሙ ለፀሃየ ጽድቅ ለአብ ሙሽራው ለወልድ ወላዲቱ ለመንፈስቅዱስ ጽርሃ ቤቱ ተፈስሂ ደስ ይበልሽ ብሎ ሰገደላት:አይሁድ ከዛ ነበሩና ምነው ሳሚናስ ምን አየህ? ምን ትላለህ? ቢሉት ከዚች ከሃና ማህፀን የምትወለደው ህፃን ሰማይ ምድርን:እመቅ አየርን የፈጠረ አምላክን ትወልዳለች እያሉ መላእክት ሁሉ ሲያመሰግኑአት ሰማሁአቸው እኔንም ያነሳችኝ የፈወሰችኝ ያዳነችኝ እርሱአ ናት አላቸው በል ተወው ሰማንህ ብለው ቅናት ጀመሩ::
""እመቤታችን እግዝትእነ ማርያም በተፀነሰች በ9 ወር ከአምስት ቀን የግንቦት መባቻ ዕለት ግንቦት 1 ተወለደች::""
እመቤታችን እግዝትእነ ማርያም የተወለደችበት እለት በአባት እናቱአ ቤት ፍስሃ ደስታ ተደረገበት ቤቱንም ብርሃን መላው በስምንተኛውም ቀን ""ማርያም"" ብለው አወጡላት::ስለምን ማርያም ብለው አወጡላት ቢሉ:እነሆ በዚ አለም ከሚመገቡት ሁሉ ምግብ ለአፍ የሚጥም ለልብ የሚመጥን "ማር" ነው:በገነትም በህይወት የተዘጋጁ ጻድቃን ቅዱሳን "ያም" የሚባል ምግብ አላቸው ::ከዚ ሁሉ የበለጥሽ የከበርሽ ነሽ ሲሉ ስለዚህ "ማርያም" ብለው አወጡላት::የእመቤታችን ማርያም ስም ተነቦ ሳይተረጎም ይቀር ዘንድ አይገባምና:-""ማ"" ማለት ማህደረ መለኮት: ""ር"" ማለት ርግብየ ይቤላ: ""ያ"" ማለት ያንቀዓዱ ኃቤኪ ኩሉ ፍጥረት:""ም"" ማለት ምስሃል ወምስጋድ ወምስትሥራየ ኃጥያት ማለት ነው::አንድም "ማርያም" ማለት ልዩ ከጣዖት:ክብርት እምፍጥረታት:ንጽህት እምሃጥያት:መልክ ከደም ግባት የተሰጣት ማለት ነው:ዳግመኛም "ማርያም" ማለት ተፈስሂ ቤተ ይሁዳ ወተሃሠዪ ቤተ እስራኤል ማለት ነው::
አንድም "ማርያም" ማለት መርህ ለመንግስተ ሰማያት ማለት ነው:ይህስ እንዴት ነው ቢሉ:እነሆ ዛሬ በዚህ አለም ለዕውር መሪ በትር እንዲሰጡት ሁሉ እርሱአም በፍቅሩአ:በጣዕመ ፍቅሩአ የሰውን ሁሉ ኃጥያት:ክፋት ፍቃ ከልጁአ ከወዳጁአ አስታርቃ ከገሃነመ እሳት አውጥታ መንግስተ ሰማያት የምታስገባ ስለሆነች ስለዚህ መርህ ለመንግስተ ሰማያት አሉአት::አንድም ማርያም ማለት ሰረገላ ፀሃይ ማለት ነው:አንድም ማርያም ማለት ተላኪተ እግዚአብሄር ወሰብእ ማለት ነው:አንድም ማርያም ማለት ውብህት(ስጥውት) ማለት ነው::
በዚህ በግንቦት አንድ ቀን እመቤታችን አለምን ልታስምር ከቅድስት ሃና እና ከቅዱስ እያቄም በብዙ ልመና ተገኘች::
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ፍቅሩአ ጣዕሙአ በረከቱአ ረድኤቱአ አማላጅነቱአ በእውነት በኛ አማላጅነቱአን በምናምን ልጆቹአ ላይ ይደርብን::

ከትንሣኤ እሁድ በኋላ ያሉ ዕለታት ስያሜ ...



ሰኞ- ማዕዶት ይባላል፡- ማዕዶት ማለት መሻገር፣ ማለፍ ማለት ነው፡፡ በዚህ ዕለት በፋሲካችን በክርስቶስ ትንሣኤ ከድቅድቅ ጨለማ ወደ ሚደነቅ ብርሃን፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከሲኦል ወደ ገነት፣ ከሃሳር ወደ ክብር መሻገራችንን እናስባለን፡፡

ማክሰኞ- ቶማስ ይባላል፡- በዚህ ዕለት ቶማስ ጌታን አይቶ ማመኑ፤ ጌታዬና አምላኬ ብሎ መመስከሩ ይዘከራል፡፡ ዮሐ. 20፡27-29

ረቡዕ- አልአዛር ይባላል፡- በዚህ ዕለት ትንሣኤና ሕይወት የሆነው ጌታ ኢየሱስ አልአዛርን ከሞት እንዳስነሳው እናስባለን፡፡ ክርስቶስ የሞትን ስልጣን የሻረ የሕይወት ራስ፤ የመቃብርን ሥርዓት ያጠፋ ትንሣኤ፡ በድልም ያረገ ንጉሥ መሆኑን እንመሰክራለን፡፡


ሐሙስ- አዳም ሐሙስ ይባላል፡- በዚህ ዕለት ለአዳም የተሰጠው ተስፋ እና የተገባለት ኪዳን እንደተፈጸመ አዳምና ልጆቹ ነጻ እንደወጣን እናስባለን፡፡


አርብ- ቅድስት ቤተክርስቲያን ይባላል፡- በዚህ ዕለት ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ስለመመስረቷ ይሰበካል፡፡ ክርስቶስ ስለ እርሷ ራሱን አሳልፎ ሰጥቶ ቤዛ ሆኖ በደሙ አንጽቶ በትንሣኤው ድል ሰጥቶ እንዳከበራት ይነገራል፡፡ ቤተክርስቲያን ስንል ሕንፃውን ሳይሆን አማኞችን ነው፤ ክርስቶስ ለሕንፃ አልሞተምና፡፡


ቅዳሜ- ቅዱሳት አንስት ይባላል፡- በዚህ ዕለት ቅዱሳት አንስት የክርስቶስን አካል ሽቶ ለመቀባት ጨለማ አቋርጠው ወደ መቃብር መምጣታቸውና ትንሣኤውንም ቀድመው ማየታቸው ይሰበካል፡፡


እሁድ- ዳግም ትንሣኤ ይባላል፡- በዚህ ዕለት ክርስቶስ ለሦስተኛ ጊዜ ለደቀመዛሙርቱ ተገልጦ ሰላምን መስበኩ እና ሥልጣንን መስጠቱ ይሰበካል፡፡

Sunday, May 5, 2013

እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤዉ በሰላም አደረሳቹ

ትንሣኤውን የምናከብረው ያጡትን በማሰብ ይሁን

የትንሣኤን በዓል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን ሞትን በመስቀል ላይ ከተቀበለ በኋላ በሦስተኛው ቀን መግነዝ ፍቱልኝ፣ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል ከሙታን ተለይቶ የተነሣበት ዕለት ነው፡፡

የትንሣኤውም ዓላማ የሰው ልጅ በመቃብር ፈርሶ በስብሶ አለመቅረቱን ለማስረዳት፣ ክርስቲያኖች ከሞት በኋላ ተስፋ ትንሣኤ እንዳለን ለማጠየቅና ከወደቅንበት ኃጢአት በንስሐ መነሣት እንዳለብን ለማስተማር መሆኑን መገንዘብ ይገባናል፡፡

በቤተክርስቲያናችንም እነዚህ ታላላቅ ዓላማዎች ያሉት የትንሣኤ በዓል በደመቀ ሁኔታ እንደሚከበር ይታወቃል፡፡ ምክንያቱም ጠላቶቻችን ሞትና ሰይጣን ድል የተነሡበት፣ የሰው ልጅም ከሰይጣን ባርነት ነጻ የወጣበት፣ በአዳምና በሔዋን ምክንያት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የነበረው የጥል ግድግዳ የፈረሰበት፣ የድል፣ የነጻነትና የሰላም ዕለት ስለሆነ ነው፡፡


ስለዚህም በቤተክርስቲያናችን የትንሣኤ ሰላምታ የተለየ ነው፡፡ ይኸውም፡-

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን. . . በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን
አሰሮ ለሰይጣን. . .  አጋዐዞ ለአዳም
ሰላም . . .  እም ይእዜሰ
ኮነ . . .  ፍስሐ ወሰላም  የሚል ነው፡፡

እንግዲህ ይህንን በዓል በየዓመቱ ስናከብር ዓላማውን ዘንግተን በዓሉን የምግብና የመጠጥ ብቻ እንዳናደርገው መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡

በልዩ ልዩ መንገድ በፈቃዱ የሰይጣን ባሪያ የሆነ፣ ከክርስቲያናዊ ምግባርና ትሩፋት የራቀ ሁሉ ራሱን እንዲመረምርና ለመልካም ሥራ እንዲነሣ የሚያደርግ በዓል መሆኑን ተረድተን ራሳችንን ልናስተካክል ያስፈልጋል፡፡

በዓለም በሥጋ ሥራ በመመላለስ የምንኖር ከዚህ ሥራችን በልቦና ትንሣኤ ተነሥተን የንስሐ ፍሬ የምናፈራበት እንዲሆን ልንተጋ ይገባናል፡፡

ክርስትናችን በስም ብቻ ተወስኖ በዓለም በሥጋ ሥራ የምንኖር ደግሞ ራሳችንን በመመርመር በንስሐ ታጥበንና ታጥነን ትንሣኤውን ቅዱስ ሥጋውን፣ ክቡር ደሙን በመቀበል እናክብረው፡፡
ሁልጊዜም በዓሉን ከነዳያን ጋር እየተካፈልን የምንኖር መልካም ልማድ ያለን የትሩፋት ሥራችንን እያሳደግን፣ በሃይማኖትና በምግባርም እየበረታን ልንሔድ ያስፈልጋል፡፡ ክርስትና ሠላሳ፣ ስድሳና መቶ ፍሬ የምናፈራበት የዕድገት ጉዞ እንጂ በምንሠራት ጥቂት የትሩፋት ሥራ ብቻ ረሥተን የምንቆምበት አይደለምና በትሩፋት ላይ ትሩፋት፣ በጸጋ ላይ ጸጋ እየጨመርን መሔድ ይገባናል፡፡

ትንሣኤውን በማሰብ ነዳያንን የምናስፈስከውም የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ማኅበራትም ሁልጊዜ በሬ እያረዱ ፋሲካውን ማክበር ብቻ ሳይሆን፤ ነዳያኑንና ወጥተው ለመለመን አፍረው በየቤቱ የተቀመጡ ወገኖቻችንን ጭምር በማስታወስ እንዲሁም በልማት የሚያሳትፍ ሥራ ወደመሥራት በማደግ ችግረኞቹን በዘላቂ ልማት ራሳቸውን እንዲችሉ ማድረግ ይገባናል፡፡

ከዚህም ሌላ ነዳያኑን በዚህ ዓለም በሥጋ ስላጡ በነፍሳቸው በመንፈሳዊ ሕይወት እውቀት አግኝተዋል ማለት ስላልሆነ፤ በነፍሳቸው የእግዚአብሔር መንግሥት ወራሾች እንዲሆኑ  መንፈሳዊውንም ምግብ ልንመግባቸው ያስፈልጋል፡፡

በአጠቃላይ በዓሉን በምናከብርባቸው ዕለታት ሁሉ ነገረ መስቀሉን በማሰብ፣ መልካም ሥራን በመሥራትና በትሩፋት ላይ ትሩፋት በመጨመር፣ በንስሐ እንዲሁም በንጽሕና ቅዱስ ሥጋውን፣ ክቡር ደሙን በመቀበል ይሁን፡፡ ለዚህም የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን

Sunday, April 28, 2013

ዕለታተ ሰሙነ ሕማማት ወምስጢራት

ዕለታተ ሰሙነ ሕማማት ወምስጢራት


ከአባታችን አዳም በደል ወይንም ስሕተት በኋላ በሕማማት፣ በደዌያት፣ በመቅሰፍታት፣ ወዘተ በብዙ መከራ የሰው ልጅ ሊኖርባቸው ግድ የሆነባቸው ዘመናት ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ ጥሮ ግሮ ወጥቶ ወርዶ ለፍቶ ማስኖ የዕለት ጉርስ የቀን ልብስ ማግኘት እጅግ አዳጋች ነበር፡፡ ሁልጊዜ የሰው ልጅ ቢያጠፋ ቢበድል ከሕገ እግዚአብሔር ቢወጣ እንኳ የዋህ፣ ታጋሽ፣ ቸር፣ አዛኝ የሆነ አምላክ የጠፋውን ሊፈለግ የተራበውን ሊያጠግብ የታረዘውን ሊያለብስ፣ ፍቅር ያጣውን ፍጹም ፍቅር ሊለግስ፣ ሰላም ለሌለው ፍጹም ሰላም ሊሰጥ፣ ተስፋ የሌለውን ተስፋ ሊያጐናጽፍ ከሰማይ ወረደ፤ ከድንግል ማርያም ተወለደ፤ በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና ሌሊት ጾመ፡፡ በጾሙም የኃጡአት ሥሮች ወይም ራሶች የተባሉትን ስስትን፣ ትዕቢትንና ፍቅረ ንዋይን ድል አደረገልን፡፡ እኛ እርሱ የጾመውን ጾም እንድናከብር እንድንጾም ምሳሌ ሆነን፡፡ ዲያብሎስን ድል አድርጐ ድል እንድንነሣው ኃይልና ምሳሌ ሆነን፡፡

ሰሙነ ሕማማት ምንድን ነው?

ሰመነ ስምንት /ሳምንት/ አደረገ ማለት ነው፡፡ ይኸውም ከዕለተ ሆሣዕና ሰርክ እስከ ትንሣኤ ሌሊት ያለውን ጊዜ ወይም ቀናት የሚያመለክት ነው፡፡ ሐመ ማለት ታመመ ማለት ሲሆን ይህም የሰውን ዘር ሁሉ ከዲያብሎስ ባርነት ነፃ ለማውጣት ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፈቃዱ የተቀበላቸውን ጸዋትወ መከራዎች የሚያሳስብ ነው፡፡ ዕለታቱ የዓመተ ኩነኔ ወይም የዓመተ ፍዳ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ክርስቲያኖች የክርስቶስን ውለታ እያሰቡ እጅግ የሚያዝኑበት፣ የሚያለቅሱበት፣ የሚሰግዱበት ቤት ንብረታቸውን ትተው ከሌላው ቀናትና ጊዜያት በተለየ መልኩ ቤተ ክርስቲያናቸውን የሚማጸኑበት፤ ጧት ማታ ደጅ የሚጠኑበት፤ ኃጢአታቸውን በቤተ ክርስቲያን አደባባይ ለካህኑ የሚናዘዙበት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ሳምንት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ብዙ አዝማደ መባልእት አይበሉም፤ ይልቁን በመራብ በመጠማት በመውጣት በመውረድ በመስገድ በመጸለይ በመጾም በየሰዓቱ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጸዋትወ መከራዎች በማሰብ አብዝቶ ይሰገዳል፡፡ መከራውን፣ ሕማሙን፣ ድካሙን የሚያስታውሱ ከቅዱሳት መጻሕፍት ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ መዝሙረ ዳዊት ግብረ ሕማማት ወዘተ በየሰዓቱ ይነበባል፡፡

መስቀል መሳለም የለም፡፡ ካህናትም እግዚአብሔር ይፍታህ አይሉም የሳምንቱ ሥርዓተ ፍትሐት አይደረግም፡፡ ይኸውም ይህ ሳምንት ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገርንበት ከጨለማ ወደ ብርሃን የተጓዝንበት የመሸጋገሪያ ወቅት ምሳሌ በመሆኑ ነው፡፡ በዕለተ ምጽአት መላእክት የመለከት ድምጽ በማሰማት የዳግም ምጽአትን ዕለት ለማሳሰብ ምእመናን ጥሪውን ሰምተው ለዚህም አስቀድመው ተዘጋጅተው የበዓሉ ታዳሚዎች መሆናቸውን በማጠየቅ በዚህ ሳምንት ዲያቆኑ ቃጭል እየመታ በየሰዓቱ ምእመናኑን ያሳስባል፡፡

በሰሙነ ሕማማት የሚገኙ ዕለታትና ስያሜያት

ዕለተ ሰኑይ /ሰኞ/


ይህ ዕለት አንጾሖተ ቤተ መቅደስ /የቤተ መቅደስ መንጻት/ እና መርገመ በለስ የተፈጸመበት ዕለት ነው፡፡ /ማር.11-11፣ ማቴ.21-18-22 ሉቃ.13-6-9/፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ «ወመሰለ ሎሙ ወይቤሎሙ አሐዱ ብእሲ በለሰ ቦቱ ውስተ አጸደ ወይኑ ወየሐውር ይንሣእ ፍሬሃ ወኢይረክብ ...»፤ ይህንም ምሳሌ አለ ለአንድ ሰው በወይኑ አትክልት የተተከለች በለስ ነበረችው ፍሬም ሊፈልግባት ወጥቶ ምንም አላገኘም፡፡ በማለት በበለስ ስለተመሰለ የሰው ልጅ ሕይወት በማሰብ እንዲመለስ ንስሐ እንዲገባ በሕይወትም እንዲኖር እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ማሳሰቡን ያጠይቃል፡፡ ንስሐ አልገባም አልመለስም ያለም በለሷ እንደጠወለገችና እንደተቆረጠች ሁሉ ፍሬ ባለማፍራታቸው እንደሚቆረጡ እንዲሁም ወደ እሳት እንደሚጣሉ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ያስረዳል፡፡ በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል ፍሬ የተባለ ደግሞ ሃይማኖትና ምግባርን ነው፡፡ ሁላችን ቤተ እስራኤላውያን ፍሬ ሃይማኖት ወምግባር አስተባብረን ይዘን መገኘት ይገባናል፡፡ ፍሬ አልባ እንዳንሆን ጌታ ሲመጣም እንዳናፍር የመጽሐፉን ቃል ልንጠብቅና ልንፈጽም ይገባናል፡፡ በዚህ የሕማማት የመጀመሪያ ቀን ዕለተ ሰኑይ የምናስበው የምንዘክረው የሰው ልጅ ሕይወት በከንቱ በቸልተኝነት እንዳይደክም እንዳይጠወለግ እንዳይደርቅ ወደ እሳትም እንዳይጣል ማድረግ ይገባናል፡፡

ዕለተ ሠሉስ /ማክሰኞ/



ይህ ቀን ጌታችን ሰኞ በተናገረውና ባደረገው ላይ አይሁድ ጥያቄ ያቀረቡበት እርሱም መልስ በመስጠት ያስተማረበት ዕለት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የጥያቄ እና የትምህርት ቀን በመባል ይታወቃል፡፡ ጥያቄውም ጌታ ባደረገው አንጽሖተ ቤተ መቅደስ ምክንያት ለጸሐፍትና ፈሪሳውያን ይኸውም ትምህርት ማስተማር፣ ተአምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታትን በማን ሥልጣን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ?» የሚል ነበር፡፡ /ማቴ.21-23-27/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ «ወይቤሎሙ ኢየሱስ አማን እብለክሙ ከመ መጸብሓውያን ወዘማውያት ይቀድሙክሙ ውስተ መንግሥተ እግዚአብሔር»፤ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው እውነት እላችኋለሁ ቀራጮችና ጋለሞቶች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሙአችኋል ሲል አስተምሯል፡፡ /ማቴ.21-28/

ዕለተ ረቡዕ

ይህ ዕለት ደግሞ የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንደሚችሉ ምክር የጀመሩበት ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዕለቱ የምክር ቀን በመባል ይጠራል፡፡

ዕለተ ሐሙስ


ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዕለት ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑን ለመግለጥ እና ለአርአያነት ጸሐፍት ፈሪሳውያን የአይሁድ ካህናት መጥተው እስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ በማደሩ ምክንያት ጸሎተ ሐሙስ በመባል ይታወቃል፡፡ ትሕትና ፍቅር መታዘዝ እንዲሁም የአገልግሎትን ትርጉም ለማስረዳትና ለማስገንዘብ የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠቡ ሕጽበተ ሐሙስ በመባልም እንደሚጠራ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይናገራሉ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስም «ወሶበ ኀፀቦሙ እገሪሆሙ ነሥአ አልባሲሁ ወረፈቀ ካዕበ ወይቤሎሙ አእመርክሙኑ ዘገበርኩ ለክሙ ... ወሶበ አነ እንከ ሊቅክሙ ወእግዚእክሙ ኀፀብኩክሙ እገሪክሙ ከማሁኬ አንትሙኒ ይደልወክሙ ትኅፅቡ እግረ ቢጽክሙ፡፡»፤ «እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ ተቀመጠ እንዲህም አላቸው ያደረግሁላችሁን ታስተውሉታላችሁን?... እንግዲህ እኔ ጌታና መምህር ስሆን እግራችሁን ካጠብሁ እናንተ ደግሞ እርስ በእርሳችሁ ትተጣጠቡ ዘንድ ይገባችኋል ሲል ተናግሯል፡፡ /ዮሐ.13-12-20/፡፡

ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው እንካችሁ ብሉ፤ ይህ ስለ እናንተ የሚፈስ ደሜ ነው ከእርሱ ጠጡ በማለት ምሥጢረ ቁርባንን የመሠረተበት ወይም ራሱ ምስጢረ ቁርባንን የጀመረበት ቀን በመሆኑ የምስጢር ቀን ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም የሰው ልጆች ሥጋውንና ደሙን ተቀብለን ከእርሱ ጋር አንድነትና ኅብረት እንዲኖረን ጥንተ ጠላት ዲለብሎስንም ፍጹም ድል ነሥተን ሰማያዊት ርስት መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ለማስቻል ነው፡፡ /ማቴ.26-26-29/፡፡

አይሁድ ጌታችንን ለመያዝ በእነርሱ ጥበብና ፍላጐት ቀስ ብለው መጥተው የያዙበት ቀን ስለሆነ በዚህ ዕለት በለሆሳስ /ብዙ የድምጽ ጩኸት ሳይሰማ/ የቅዳሴ ሥርዓት ይፈጸማል፡፡ ስለሆነም መላው ሕዝበ ክርስቲያን በዚህ የሕጽበት፣ የምስጢር፣ የጸሎት ቀን በተባለው በዚህ ዕለት በንስሓ ታጥበው ሥጋ ወደሙ እንዲቀበሉ ቤተ ክርስቲያን በአጽንኦት ታስተምራለች፡፡

ዕለተ ዐርብ


ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ «አውቀውስ ቢሆን የክብርን ጌታ ባልሰቀሉት» /1ቆሮ.1-18/፡፡ እንዳለ ይህ ዕለት የአይሁድ ካህናት ያለበደል ያለጥፋት ንጹሕና ጻድቅ የሆነውን ጌታ የሰቀሉበት ዕለት ነው፡፡ ዕለቱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ሁሉ መድኃኒት ለአዳምና ለልጆቹ ሲል በመልእልተ መስቀል በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ መዋሉን የምናስብበት ታላቅ ቀን ነው፡፡ /ማቴ.27-35-75/፡፡ በዚያን ጊዜ አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ ሠላሳውንም ብር ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች መልሶ ንጹሕ ደም አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ አለ፡፡ እነርሱ ግን እኛስ ምን አግዶን? አንተው ተጠንቀቅ አሉ፡፡ ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሔደና ታንቆ ሞተ፡፡ የካህናት አለቆችም ብሩን አንሥተው የደም ዋጋ ነውና ወደ መባ ልንጨምረው አልተፈቀደም አሉ፡፡ ተማክረውም የሸክላ ሠሪ መሬት ለእንግዶች መቃብር ገዙበት፡፡ ስለዚህ ያ መሬት እስከ ዛሬ ድረስ የደም መሬት ተባለ፡፡ /ማቴ.27-3-9/

የሰው ልጆች በዘር ኃጢአት /ቁራኝነት/ ይኖሩበት የነበረው የጨለማ ሕይወት ያከተመበት ፍጹም ድኅነት ያገኙባት ታላቅ ዕለት ናት፡፡ ክርስቲያኖች ሁልጊዜም ዕለተ ዓርብ ሲመጣ ሕማሙን ስቅለቱን ሞቱን የሚያስቡበት ጊዜ ነው፡፡ በሮማውያን ሕግና ሥርዓት መስቀል የወንጀለኞች መቅጫ ምልክት የሕይወት መቅጫ አርማ ሆኖ ሳለ ለእኛ የዲያብሎስ ድል መንሻ ስላደረገው በስቅለቱና በሞቱም ሕይወትን ስለአገኘን በዚህም ምክንያት መልካሙ ዓርብ በመባል እንደሚታወቅ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ያትታሉ፡፡

ቀዳሜ ስዑር


ዕለተ ቅዳሜ እግዚአብሔር የሚታዩትንና የማይታዩትን፣ በእግር የሚሄዱትን እና በክንፍ የሚበሩትን በባሕር የሚዋኙትን እንስሳትን በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ያረፈበት ዕለት ነች፡፡ ይህች የመጀመሪያው ቅዳሜ ለእግዚአብሔር የዕረፍት ዕለት ናት እግዚአብሔርን ሥነ ፍጥረት ፈጥሮ ስላረፈበት ሰንበት ዐባይ /ታላቋ ሰንበት/ ትባላለች ታላቋን ሰንበት እስራኤላውያን እንዲያከብሯት ታዟል፡፡ ዘፍ.1፡3፡፡

ዕለተ ቀዳሚት /ሰንበት ዐባይ/ በዘመነ ሐዲስም የተለየ የደኅነት ሥራ ተከናውኖባታል፡፡ ጥንት ሥነ ፈጥረትን በመፍጠር ዕረፍት እንደ ተደረገባት ሁሉ የፍጥረት ሁሉ ቁንጮ የሆነውን አዳምን ለማዳን ሕማምና ሞት የተቀበለው ቸሩ አምላክ በመቃብር አርፎባታል፡፡ ማቴ.27፡61፡፡

በዚህች ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሰ መቃብር ዐርፎ የዋለባት ዕለት በመሆኗ «ቀዳሜ ስዑር » ትሰኛለች፡፡ ስዑር ቀዳሜ የተባለችው በዓመት አንድ ቀን ስለ ምትጾም ነው፡፡ ምክንያቱም እናቱ ድንግል ማርያም ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታ ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት አንስተው ብርሃነ ትንሣኤውን እስኪያዩ ድረስ እህል ውኃ በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ ያደረጉት የነበረ አምላካቸው በመቃብር ስላረፈ ዕለቷን ሞቱን በማሰብ ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡

ከቅዱሳን ሐዋርያት ሲወርድ ሲወራረድ በመጣው ትውፊት መሠረት ቅዱሳን ሐዋርያት በማዘን በመጾምና በመጸለይ ዕለቷ እንዳከበሯት የተዋሕዶ ልጆች የተቻላቸው ከዓርብ ጀምረው የሚያከፍሉ /የሚጾሙ/ ለሁለት ቀን እህል ውኃ ሳይቀምሱ ያድራሉ ያልተቻላቸው ደግሞ ዓርብ ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡

በዚህ ዕለት ከሰኞ ከሆሣዕና ማግሥት ጀምረው እስከ ስቅለተ ዓርብ ድረስ በስግደት እና በጾም ያሳለፉ ምእመናን በዕለተ ቅዳሜ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ይሰበሰባሉ፡፡ የጠዋቱ ጸሎት ሲፈጸም ካህናቱ «ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፡-በመስቀሉ ሰላምን መሠረተ» የምሥራች እያሉ በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰቡት ምእመናን ቄጠማ ይታደላል ቄጠማው የምሥራች ምልክት ነው፡፡ ቄጠማው የምሥራች ምልክት ተደርጐ የተወሰደው በኖህ ዘመን ከተፈጸመው ታሪክ ጋር በማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሕዝቦች ከሕገ እግዚአብሔር ውጪ ሆነው እጅግ የሚያሳዝን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ በንፍር ውኃ ተጥለቅልቀዋል፡፡ በወቅቱ ጻድቁ ኖኅ ወደ መርከብ ይዞአቸው ከገባው እንስሳት መካከል የውኃውን መጉደል ለመረዳት ርግብን በመርከብ መስኮት አሾልኮ ይለቃታል፤ እርሷም ቄጠማ በአፍዋ ይዛ ትመልሳለች፡፡ ዘፍ.9-1-29፡፡ ኖኅም በዚህ ቄጠማ የውኃውን መድረቅ ተረድቶ ተደስቷል፡፡

«ቄጠማ»፣ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች መንገሪያ እንደሆነ አሁንም በክርስቶስ ሞት ሞተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ ስትል ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡ ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የሆነውን ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፡፡

የክርስቶስ ተከታዮች ሁሉ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሚያቃጥለው ዋዕየ ሲኦል /የሲኦል ቃጠሎ/ ወደ ልምላሜ ገነት ጥንተ ማኅደራቸው መመለሳቸውን በዚህ አኳሃን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡

ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን፡፡አሜን፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በዲ.ቸሬ አበበ

Source : http://www.eotc-mkidusan.org/






Friday, April 26, 2013

ሆሣዕና





ሆሣዕና ከስምንቱ የዐቢይ ጾም እሑዶች አንዱና የመጨረሻው ሳምንት ተብሎ የሚጠራው ከትንሣኤ ቀድሞ የሚገኝ የሕማማት መገቢያ ዋዜማ ነው። ሆሣዕና አስቀድሞ ካለው ረቡዕ ጀምሮ የሚታሰብ ታላቅ የቤተክርስቲያን የበዓል ቀን እንደሆነ ይታወቃል። ይህን ስም በዚሁ ሰንበትና በዋዜማዎቹ ዕለታት የሚዘመረው ጾመ ድጓ ‘ሆሣዕና በአርያም’’ ‘ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት’’ ‘ዕለተ ሆሣዕናሁ አርዓየ… ‘ ወዘተ. በማለት ሆሣዕና የሚለውን ቃል ቅዱስ ያሬድና ሌሎችም አባቶች በየቦታው እየጠቀሱና እየተዘመረለት በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ኢየሩሳሌም የገባበትን ሁኔታ እየተረከ ስለሚዘምር ይህ ሰንበት በጌትነትና በክብር በውዳሴና ቅዳሴ ሆሣዕና በአርአያም እየተባለ በሽማግሌዎችና በሕፃናት አንደበት በድንጋዮችም ልሳን ሳይቀር እየተመሰገነ ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በከብር ሲገባ ለሰጣቸው ለተቀደሰ ሰላሙና ፍቅሩ መታሰቢያ ሆኖ የተሰጠ ነው።


አስቀድሞም በነቢየ እግዚአብሔር ዘካሪያስ እንደተነገረው ‘አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ እጅግ ደስ ይበለሽ ፣አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ እልል በይ እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው ትሑትም ሆኖ በአህያም በአህያያቱም ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል… ሰላምን ይናገራል’’ ዘካ.9፣9። በማለት እንደሚመጣና የሠላምንም ብሥራት እንደሚያበሥር ተናገሮ ነበር። ሲመጣም ‘ሁሉም ፈጥነው ልብሳቸውን ወሰዱ በሰገነቱም መሰላል እርከን ላይ ከእግሩ በታች አነጠፉት።’’ በማለት ሊደረግለት የሚገባውን ገልጿል። 2ኛ ነገ. 9፣13 ። የሆሣዕና በዓል በቤተክርስቲያን ጌታ ወደ ቤተመቅደስ ሲገባ ሕዝቡ ፀበርት ወይም ዘንባባ በመያዝ ‘ቡርክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር - በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረክ ነው።’’ መዝ.117፣26 በማለት ስለተቀበሉት ይህን በማሰብና በማድረግ ቤተክርስቲያናችን ዘንባባ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ይታደላል። በቤተክርስቲያን በአራቱም ማዕዘናት ይህን በዓል የሚመለከቱ የቅዱስ ማቴዎስ (ማቴ. 21፣1-17)፤ የቅዱስ ማርቆስ፣(ማር.11፣1-10)፤ የቅዱስ ሉቃስና (ሉቃ.19፣29-38)፤ የቅዱስ ዮሐንስ (ዮሐ.12፣12-15) ወንጌላት ይነበባሉ ። ታዲያ አኛ ይህን ዐቢይ በዓል የምናከብረው እንዴት ነው? በነቢያቱ ከላይ እንደተገለጠው በወንጌላቱም አንደተፈጸመው እርሱ ወደ እኛ የሚመጣበት ጊዜ መቼ ነው? ሲመጣስ ምን እናድርግ? የእግዚአብሔርን መምጫ ጊዜ ማሰብና መዘጋጀት ያለብን እንዴት ነው? ምክንያቱም በዓሉ ከምንም በላይ የሚጠቅመን ለእኛ ነውና ። ስለዚህ ይህን በዓል ስናከብር ሰላምንና ፍቅርን የእርሱን የክብር አመጣጥ እያሰብን ልንተገብረው ይገባል። 


ለጌታ የማያስፈልግ ፍጥረት የለም ይልቁንም የክብር ዘውድ አድረጎ በመልኩ የፈጠረው ሰው ያስፈልገዋል።ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ የተፈጠረ ማንም የለም።እያንዳንዳችን በእግዚአብሔር ዓላማና ዐቅድ የተፈጠርን እንደመሆናችን መጠን እግዚአብሔር የሚከብርበትን ሥራ ልንሠራ ይገባል።አህያ በሰው ሰውኛ ሲታይ የንቀትና የውርደት ሲመስል ይችላል ።





የአህያን ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ ስንመለከት ግን 


1. በለዓም በሥጋዊ ገንዘብ መንፈሳዊ ዓይኑ ታውሮ እግዚአብሔር ያልረገማቸውን እስራኤላውያንን ሊራገም ሲሄድ እስራኤላውያንን እንዳይራገም ለመንገር ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከው መልአክ በሚሄድበት መንገድ ላይ ቆሞ ሳለ ከበለዓም ይልቅ ያየችው የበለዓም አህያ ነበረች ። አህያይቱም መልአኩን አክብራ መንገዱን እንደለቀቀችለት ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል። ዘኅ.22፣23። 


2. በትንቢተ ኢሳያስ 1፣3 ‘ሰማይ ስሚ ምድርም አድምጪ በሬ የገዢውን አህያም የጌታውን ጋጣ አወቀ እሥራኤል ግን አላወቀም’’ እንደተባለው ጌታ በተወለደ ጊዜ ትንቢቱን ምሳሌውን የሚያውቁ እሥራኤላውያን ባላወቁ ባለተቀበሉ ሰዓት በዚያ በብርድ ወራት እናቱ የምታለብሰው ልብስ አጥታ ቅጠል አልብሳው በነበረ ጊዜ ለጌታ ሙቀት የገበሩለት እረኞቻቸውን ተከትለው የመጡ ከበቶች ላሞችና አህዮች ናቸው። ‘ወአስተማወቅዎ አድግ ወላህም’’ እንዲል አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም።። 


3. በሆሣዕና ዕለት ከሌሎች እንስሳት ይለቅ ጌታን ለመሸከም ለከብር የተሸከመችው አህያ ናት። ጌታን የተሸከመችው አህያ ከዚያ በፊት ያላየችውና ያልተደረገላት ክብር ተደርጉላታል። አህያ ከዚህ በፊት ለኛ እህል ተሸክማ ስትሄድ ሂጂ እያልን በዱላ እንደበድባት ነበር፡ ነውም። ነገር ግን በሆሣዕና ዕለት እንኳን በዱላ ልትደበደብ ቀርቶ ሰዎች በእርሷ ላይ ለተቀመጠው ጌታ ሲሉ ልብሳቸውን ሁሉ እያነጠፉላት በንጣፍ ላይ ተራምዳለች ። 


ስለዚህ ክርስቶስ በአህያይቱ ላይ እንዲቀመጥባት ልብስም አንደ ተጎዘጎዘላት እኛም ጌታ በፀጋውና በረድኤቱ እንዲያድርብን ልባችንን ከኃጢአትና ከተንኮል አንጽተን ፍቅርንና ትሕትና ልንጎዘጎዝ ይገባል።ጌታ በኛ ላይ በፀጋው ሲያድር በእርሱና በቅዱሳኑ ዘንድ ያለን ክብርና ፀጋ ታላቅ ነው። በነገር ሁሉ መከናወን ይሆንልናል።ክርስቶስን በመሸከሟ የአህያይቱ ታሪክ እንደተለወጠ ሁሉ በክርስቶስ ማደሪያነታችን ያለፈው መጥፎ ታሪካችን ይለወጣል።እንግዲህ በእለተ ሆሣዕና ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄድ ሕዝቡ ሁሉ በደስታ በዝማሬ እንደ ንጉሰ እንደተቀበሉት እኛም ሀሴትን አድርገን ‘ሆሣዕና እምርት እንተ አቡነ ዳዊት…’’ በማለት እናመሰግናለን። ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን።አሜን።