Friday, May 31, 2013

ግንቦት 24

በዚህች ቀን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልጇን እግዚያብሔርን ይዛ ከዮሴፍና ከሶሎሜ ጋር ወደ ግብጽ የተሰደዱበት ቀን ነው፤ ይህን ቀን ቤተክርስቲያን በደማቁ አክብራው ትውላለች፤ በመዲናችን አዲስ አበባ እንጦጦ መንበረ ንግስት ቁስቋም ቤተክርስቲያን እንዲሁም ቅዱስ ዮሴፍ ቤተክርስቲያን ታቦተ ሕጉ ወጥቶ በደማቁ ተከብሮ ይውላል።እነሆ፥ የጌታ መል...አክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ። ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሣ፥ ሕፃኑንና እናቱንም ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ፥ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ አለው። እርሱም ተነሥቶ ሕፃኑንና እናቱን በሌሊት ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ። ልጄን ከግብፅ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብፅ ሄደ፥ ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ። ማቴ 213 በስደት የቆዩት ሦስት ዓመት ከመንፈቅ ነው የእመቤታችን ስደት ለኢትዮጵያ ታላቅ በረከት ነው የጣና ደሴቶችን የዋልድባ ገዳምን አክሱምና የትግራይ አውራጃዎችን፤ ድብረ ዓባይና የጎጃም ታላላቅ ገዳማትን በርካታ የኢትዮጵያ አውራጃዎችን በኪደተ እገራቸው ባርከውታል ቀድሰውታል።፤የኢትዮጵያ ድንኳኖች ሲጨነቁ አየሁ አለ ነብዩ ዕንባቆም፤ ዕንባቆም 37 ነብዩ ምን ማለቱ ነው ? መቼ ነው የኢትዮጰያ ድንኳኖች የተጨነቁት ? እመቤታችን በስደት ወደ ኢትዮጵያ ስትመጣም እይደል። ግን ግን ስደቷ ግንቦት 24 ከሆነ ለምን ከመስከረም 26 እስከ ህዳር 6 ቀን የጽጌ ጾም ብለን ስደቷን እናስባለን ካሉ፤ይህ ሊቃውንቱ የሰሩት ስርዓት ነው፤ ከመስከረም 26 እስከ ህዳር 25 በቤተክርስቲያናችን አስተምህሮ ዘመነ ጽጌ ይባላል የአበባ የልምላሜ ወቅት ነው፤ እመቤታችን ደግሞ በአበባ ትመሰላለች አበባ የፍሬ እናት ነው፡፡ እመቤታችንም የተባረከ ፍሬ መድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርሰቶስን ያስገኘች አማናዊቷ አበባ ናት፡ ስለዚህም ይህን የስደቷን ወራት በዘመነ ጽጌ ባሉት 40 ቀናት ከመስከረም 26 እስከ ህዳር 6 ቀን ታስቦ እንዲውል
የቤተክርስቲያን ሊቃውንት ስርዓትን ሰሩ።
 እግርሽ ጨረቃን የሚጫማ
 
በአሸዋ ስትሮጪ እግርሽ ደማ

ውቅያኖሶቹ ግራ ቀኙ የሚሰፈሩት በእፍኙ

ለእርሱ ለእርሱ ለዝናብ ጌታ ውኃ ነሱ።

ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን

Wednesday, May 29, 2013

ግንቦት 21



 ከእመቤታችን 33ቱ በዓላት አንዱ ነው፤በዚህ ቀን ግብጽ ደብረ ምጥማቅ በተባለ ቦታ በተሰራች ቤተክርስቲያን እመቤታችን ጻድቃንን መልአክትን አስከትላ ትገለጽላቸው ነበር፤እስላምም ክርስቲያንም በግልጽ ይመለከቷት ነበር። ከየአገሩ ያሉ ሰዎች ይሰበሰባሉ ድንኳን ተክለው ሰቀላ ሰርተው አጎበር ጥለው ይከትማሉ ፤ድንግልም ከግንቦት 21 ቀን ጀምሮ ለአምስት ተ...ከታታይ ቀናት ሳታቋርጥ ትገለጽላቸው ነበር፤ህዝቡ የተለያየ ጥያቄ ይጠይቃታል አዳም አባታችንን አሳይን ይሏታል ገሚሱ ነብዩ ዳዊትን ገሚሱ ቅዱስ ጊዮርጊስን አሳይን ይሏታል አንዳንዱም ከዚህ ቀደም የሞተ ዘመዱን እንድታሳየው ይጠይቃታል፤እርሷም ለሁሉም ፍቃዳቸውን ትፈጽምላቸው ነበር፤አዳምን ስትጠራው ከሔዋን ጋር ዳዊትን ስትጠራው ከበገናው ጋር ቅዱስ ጊዮርጊስን ስትጠራው ከጸአዳ ፈረሱ ጋር ነው። ወይ ግሩም ታዲያ ይህ በዚያ ደጉ ዘመን ነበር፤አሁን ግን ኃጢያታችን ሲበዛ በረድኤት ካልሆነ በገሃድስ ተገልጻ አትታይም ለበቁ ካልሆነ። ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን አባ መርትያኖስ አረፈ፤ ይህም በህጻንነቱ መንኩሶ ለ 67 ዓመት በፍጹም ተጋድሎ የኖረ ነው። ይህ ገድል ትሩፋቱ በሁሉ ዘንድ ተሰማ፤ እነሆ አንዲት በዝሙት ስራዋ እጅግ የምትታወቅ ሴት ዘንድ ወሬው ደረሰ፤ እርሱ እኮ የሴት ፊት ስላላየ ነው እንጂ በፍትዎት ይወድቃል ከክብሩም ይዋረዳል አለቻቸው ባልንጀሮቿም የለም በፍጹም አያደርገውም አሏት፤ እኔ በዝሙት ከጣልኩት ምን ትሰጡኛላችሁ አለቻቸው ብር እንሰጥሻለን አሏት፤በዚህ ተወራርደው ሄደች፤ ሽቶ ተቀባብታ አምራ ተውባ ሄደች፤ስንክሳሩ እጅግ ውብ መልከመልካም ነበረች ይላታል፤ እስኪመሽ ከገዳሙ አቅራቢያ ቆይታ በሩን አንኳኳች የመሸቢኝ እንግዳ ነኝ አሳድረኝ ትለዋለች፤ ነፍሱ ተጨነቀች ባስገባት የዝሙት ጦር ይነሳብኛል ብተዋት እንግዳ ሆኜ መጥቼ መቼ ተቀበላችሁኝ ብሎ ይፈርድቢኛል ደግሞም አውሬ ይበላታል ብሎ አሰበ፤ባስገባት ይሻለኛል ብሎ አስገባት የተቀበችው ሽቶ ዝሙት የሚቀሰቅስ ነው፤ ቀረበችው፤አባቴ በዚህ ማንም አያየንም አብረን እንተኛ አለችው፤እሳት እያነደደ ነበርና እሺ ምን ችግር አለው እዚህ አሳት ላይ ምንጣፍሽን አንጥፊና እንተኛለን አላት፤ አንድም እግሩን ወደ እሳቱ ማገደው ይላል አይንህ ብታሰናክልህ ካንተ አውጥተህ ጣላት አይደል የሚለው መጽሐፉ፤ ደነገጠች ምንድን ነው አባቴ አለችው፤ ይህ ያስደንቅሻልን የገሃነም እሳትን ታዲያ እንዴት ልትችይው ነው አላት እግሩ ስር ወድቃ ይቅር በለኝ አለችው እርሱም ሌሊቱን ሙሉ ሲያስተምራት አደረ፤ ሲነጋ አልተመለሰችም አመንኩሰኝ ከዚህ በኃላ ወደ ዓለም አልመለስም አለችው አመነኮሳት ከደናግል ገዳም ወስዶ ለእመምኔቷ አደራ ሰጣት፤የሚገርመው ይህች እናት ከብቃቷ የተነሳ የመፈወስ ሀብት ተሰጣት ብዙ በሽተኞች ወደርሷ እየመጡ ይፈወሱ ነበር፤ አባ መርትያኖስ ግን ድጋሚ ሌላ ሴት መጥታ እንዳትፈትነው ሰው የማይደርስበት ከባህር መካከል ባለች ደሴት ብቻውን መኖር ጀመረ፤ ከብዙ ዘመን በኃላ መርከብ ተሰብሮ ብዙዎች ሲሞቱ አንዲት ሴት በመርከቡ ስባሪ ተጣብቃ እርሱ ካለበት ደሴት ደረሰች ባያት ጊዜ ደነገጠ አደነቀም ከእርሷ ጋር በአንድነት ስለመኖሩም አዘነ፤ ይምትበላውን ሰጥቷት የምትለብሰውን አዘጋጅቶላት ሲያበቃ ተወርውሮ ወደ ባህሩ ገባ ዓሳ አንበሪም ተሸክሞ ወደ የብስ አደረሰው ከዚህ በኃላ በአንድ ቦታ ላለመቀመጥ ወስኖ በ108 አገሮች የሚገኙ ታላላቅ ገዳሞችን ዞረ በመጨረሻም በዛሬዋ ቀን በክብር አረፈ፤ እመቤታችንን ከሐና ማህጸን ፈጥሮ ከፍጥረተ ዓለም ለይቶ ከሁሉ አልቆ የእናት አማላጅ ትሁናችሁ ብሎ የሰጠን እግዚያብሔር ይመስገን፤ እኛንም ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

ግንቦት 17


በዚህች ቀን ታላቁ የቤተክርስቲያን አባት አባ ኤጲፋንዮስ አረፈ። ወላጆቹ ክርስቶስን የማያምኑ አይሁዳውያን ናቸው በዛ ላይ እጅግ በጣም ድሆች ፤አባ ኤጲፋንዮስ ክርስቶስን ያመነው ክርስትናን የተቀበለው ሁለት ታአምራቶችን አይቶ ነው፤ አንደኛው እርሱ እናቱና እህቱ ርሃብ ሲጠናባቸው የአባቱን አህያ ሊሸጥ ገብያ ሄደ አህያው በጣም አስቸጋሪ ነበርና አንዱን... ገብያተኛ ጭኑን ረግጦ ይገድለዋል፤በዚያ አካባቢ አባ ፊሎንዲስ የሚባል የበቃ ባህታዊ ነበር በመስቀል አማትቦ በክርስቶስ ስም ተነስ ይለዋል የሞተው ሰው ተነሳ፤ሁለተኛ ይኸው ባህታዊ መንገድ ሲሄድ ኤጲፋንዮስ ከኃላው ይከተለዋል አንድ ድሃ ቀርቦ ስመ እግዚያብሔርን ጠርቶ ምጽዋት ይጠይቀዋል የሚሰጠው ነገር ቢያጣ የለበሰውን ልብስ ( አጽፍ ) አውልቆ ሲሰጠው ወዲያውኑ ብርህት ልብስ ( አጽፍ ) ከሰማይ ሲወርድለት አየ፤ ከዚህ በኃላ ነው ኤጲፋንዮስ ቀርቦ አባቴ የሞተውን ሰው ያስነሳህበት አሀን ደግሞ ይህ ደሃ የክርስቶስን ስም ቢጠራብህ ልብስህን ስትሰጠው ከሰማይ ሌላ ልብስ የወረደለህ የኔ ዘመዶች ሩቅ ብእሲ ብለው ሰቅለው የገደሉት ክርስቶስ ነውን አለው አዎን ይለዋል አጥምቀኝ አለው አጠመቀው እንዳንተ መነኩሴ መሆን እፈልጋለሁ ይለዋል ካልክስ ብሎ ከሰው ተለይቶ በገዳም የሚኖር የበቃ አባት ነበር ኤላርዮስ ይባላል ወደ እርሱ ይልከዋል አመነኮሰው በተጋድሎም መኖር ጀመረ ትምህርት ታአምራቱም በተለያዩ አገሮች ተሰማ መናፍቃንን ተከራክሮም የሚረታ ሆነ ድውያንን የመፈወስ አጋንንትን የማውጣት ስልጣን ተሰጠው፤ ደግነቱን የተመለከቱ አባቶች የቆጵሮስ ኤጲስ ቆጶስ አድርገው ሾመውታል በዚህ በሹመቱ ወራት ብዙ ድርሳናትን ተግሳጻትን ጽፏል፤ አንድ ቅዳሴም ደርሷል ቅዳሴ ኤጲፋንዮስ የሚባል ይህ ቅዳሴ በተለይ በክረምት ወራት ቤተክርስቲያን የሚያዝወትሩ ከሆነ ደጋግመው ይሰሙታል ስለ ደመናት ስለ ነጎድጓድ ስለ ዝናብ በስፋት ይናገራል፤ ለጸሎተ ሐሙስም ይቀደሳል። ያ ደገኛ የተዋህዶ ኩራት ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ የድሃይቱን መበለት ርስት የነጠቀችውን ንግስት አውዶክስያን ከቤተክርስቲያን እንዳትገባ፤ እንዳትቆርብ፤ ከምዕመናን ጋር እንዳትገናኝ አውግዞ ሲለያት ለአባ ኤጲፋንዮስ መልዕክት ትልክበታለች ዮሐንስ አፈወርቅ ከግዝቱ ካልፈታኝ የአባቶቼን ዘመን እመልሳለሁ አብያተ ጣኦታት እንዲከፈቱ አብያተ ክርስቲያናት እንዲዘጉ ክርስቲያኖች እንዲሰደዱ አዋጅ አስነግራለሁ አለችው አባ ኤጲፋንዮስ ወደ ዮሐንስ አፈወርቅ ሄዶ እንዲህ ብላለች ሴትዮዋ ሰይጣን አድሮባታል ከማድረግ ወደ ኃላ አትልም ከግዝቷ ፍታት ይለዋል፤ እርሷ የአባቶቿን ዘመን ብትመልስ እኔስ ብሆን ልጆቼስ ምዕመናን ቢሆኑስ እንደአባቶቻችን በሰማዕትነት መሞት ያቅተናልን፤ ያሻትን ታድርግ ለእርሷ ይብስባታል ከግዝቷ አልፈታትም ይለዋል፤ከዚህ በኃላ አባ ኤጲፋንዮስ ዮሐንስን ተሰናብቶ ወደ አገሩ ሊመለስ ሲል አገርህ አትደርስም ከመንገድ አንበሳ ሰብሮህ ትሞታለህ ይለዋል፤ አባ ኤጲፋንዮስም አንተም እንጂ መቼ መሞት ይቀርልሃል በደሴተ አጥራክያ ተግዘህ ተንገላተህ ትሞታለህ ይለዋል፤ አሁን ሁለቱ ተጣልተው አይደለም ክብራቸውን ሲገልጽ እንጂ አንዱ የአንዱ ሞት ተገልጾለት እንዲህ ተናገሩ፤ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳለውም አባ ኤጲፋንዮስ መንገድ ላይ አንበሳ ገድሎታል ይህም ግንቦት 17 ቀን ነው ለ 40 ቀን አልተቀበረም የሚገርም መአዛ ግን ከስጋው ይወጣ ነበር ብዙ ድውያንም ተፈውሰዋል፤ዮሐንስ አፈወርቅም ንግስቲቱ በግዞት አሰቃይታ ገድላዋለች ይህም ግንቦት 12 ቀን ነው፤ ዮሐንስ አፈወርቅ ጠፍቶ የነበረውን የዮሐንስን ራእይ መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት ድጋሚ የጻፈው በዚህ በደሴተ አጥራክያ በግዞት ሳለ ነው። ከዮሐንስ ራእይ ውስጥ የዮሐንስ አፈወርቅ ቃል የሆነው ይህ ብቻ ነው “ማንምም በዚህ በትንቢት መጽሐፍ ከተጻፉት ቃሎች አንዳች ቢያጎድል፥ በዚህ መጽሐፍ ከተጻፉት ከሕይወት ዛፍና ከቅድስቲቱ ከተማ እግዚአብሔር ዕድሉን ያጎድልበታል።” ዮሐ 22፤19። ከአባቶቻችን በረከት ያሳትፈን።

Thursday, May 23, 2013

ጻድቁ አቡነ አረጋዊ



እኚህ አባት ከተሰሐቱ ቅዱሳን (ከሮምና ኤሽያ ከመጡት ከ9 ቅዱሳን አባቶች አንዱ ሲሆኑ አባታቸው ይስሐቅ የሮም ንጉስ ነበር፡፡ እናታቸው ንገሰተ እደና ትባላለች፡፡ የመጀመሪያ ስማቸው ዘሚካኤል ነው፡፡ ጥበብ መንፈሳዊ ሲማሩ አድገው ወደ እሰከነድረያ ኮብልለው ገዳም ገቡ፡፡ አበምኔቱ አባ ጳኩሚስ በፈቃደ እግዚአብሔር የመጡ መሆናቸውነ አውቀው መዓርገ ምንኩስና ሰጥተዋቸዋል፡፡
ንጉስ የሆኑ ቤታቸው የሞቀ ቤተ ሰቦቻቸውነ ንቀው ትተው ገዳም ገብተው በምንኩስና ተወስነዋል፡፡ አበምኔቱም ወደዚህች የሕየወት መንገድ ስለመራሀን ብፁህ አረጋዊ መባል ይገባሃልብለዋቸዋል፡፡ አረጋዊ የተባሉት ከዚያ ወዲህ ነው፡፡ አባታችን በተጋድሏቸውም ከአባ እንጦንስ፣ ከአባ ጳውሊ እና ከአባ መቃርስ ቀጥሎ በአራተኛ መዐረግ አበ መነኮሳት ሆነው ተመርጠዋል። በገዳመ ዳውናስ 7 ዓመት ከቆዩ በኋላ ወደ ሮም ተመልሶ ሲያስተምሩየሀገራችንን ዜና ሰምተው ለመምጣት በ480 ዓ.ም ከአባ ፍሪሚናጦስ ቦ|ላ መንገድ ጀመሩ፡፡ ቅዱስ ሚካኤል በክነፉ ተሸክሞ አክሱ አድርሷቸዋል፡፡ ተመልሶ ሄደው ስለ ኢትዮጵያ ቅድስት ሀገር መስክረዋል፡፡ ሐዋርያ ሳይላክላት በሃይማኖት በምግባር ጸንታ ትኖራለች ብለው ለሰባቱ ዘመዶቻቸው አበውመነኮሳት ነገሯቸው፡፡ ስምንቱ ሁሉ ጓዛቸውን ጠቅልለው በሮም ነግሶ የነበሩ ይስሐቅን (አባ ገሪማን) ጨምረው ንጉስ አልአሜዳ በነገሰ በአምስተኛ ዓመት ማለትም በ480 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ራሳቸውን ዘጠኝ ሆነው መጥተዋል፡፡ አባ አረጋዊ እናታቸው ቅድስት እድናን ደቀመዝሙራቸውን ማትያስን አስከትለው እግረመንገዳቸውን እያስተማሩና ድውያንን እየፈወሱ ደብረ ዳሞ ደረሱ፡፡ ከእግረ ደብር ሆነው አሁን ይህን ተራራ በምን ልወጣው እችላለሁ እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ በንግግሩ ሐሰት የሌለበት አምላካችን በነቢዩ ዳዊት ላይ አድሮ በመዝሙር 90/91፡11-16 ላይ “በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል። በተኵላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ። እንዳለው የታዘዘ ዘንዶ መጥቶ ስደሳ ክንድ በሚያህል ጅራቱ ጠምጥሞ ቅዱስ ሚካኤል ሰይፈ እሳት ይዞ እየጠበቃቸው ከተራራው አናት አድርሷቸዋል፡፡
ወዲያው ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ብለው አመስግነዋል፡፡ ቦታውም ደብረ ሃሌ ሉያ ተብሏል፡፡ በዚያ ዕለት ግማሽ ህብስት በልተው ጠገቡ፤ ከዚያ በኋላ ግን ምድራዊ ሕብስት አልተመገቡም፡፡ በሰንበተ ክርስታያን ከቅዳሴ በኋላ ሕብስተ ሰማያዊ እያመጡላች ይመገቡ ነበር እንጂ፡፡ ኋላ ግን ዜና ጽድቃቸውን ሰምተው ከስድስት ሺህ ያላነሱ ደቀ መዛሙርት ተሰብስበውላቸዋል፡፡ ዘጠና ዘጠኝ አመት ሲሞላቸው ጌታ በመንፈቀ ለሊት ተገልጾ ምድራዊ መንግስትህን ትተህ ስላገለገልከኝ ህልፈት ሽረት የሌለባት ሰማያዊ መንግስቴን አወርሰሃለሁብሎ ቃልኪዳን ሰጣቸው፡፡ በስምህ የተማጸነውን እስከ አስራ አምስት ትውልድ ድረስ እምርልሃለሁ አንተም ከሞት ገጽ ትሰወራለህ ብሎ ተስፋቸውን ነገራቸው፡፡ እሳቸው መነኮሳቱን ሰብስበው ከእንግዲህ በሥጋ አታዩኝም ብለው ነግረዋቸው አበምኔት (የገዳም አባት ወይም አለቃ) ሾመውላቸው ጥቅምት አሥራ አራት ቀን በዚያው በደብረ ዳሞ ተራራ በስተምስራቅ አቅጣጫ እንደሄኖክ እንደ ኤልያስ ተሰውሯል፡፡

በረከታቸው፣ ቃልኪዳናቸው፣ አማላጅነታቸው በሁላችን ይደር አሜን።

Sunday, May 19, 2013

ግንቦት 12







የአባታቸንና የኢትዮጵያ ፀሀይ የፃድቁ የተክለሀይማኖት ዐፅመ ፍልሰት ክብረ በዓል ግንቦት ፲፪ ከደብረ አሰቦ ወደ ደብረ ሊባኖስ አጽማቸው የፈለሰበት(ፍልሰተ አጽም) በዓለ ንግስናቸው ይከበራል። ይህም ማለት አባታችን 29 ዓመት ቆመው ሲጸልዩ 7ቱን ዓመት ደግሞ ባንድ እግራቸው የጸለዩና አፅማቸው በደብረ አስቦ ከተቀበረበት ወጥቶ አሁን ደብረ ሊባኖስ ገዳም የተሰራበት ቦታ ጋር የፈለሰበት ታላቅ በዓል በተለይ በደብረ ሊባኖስ በታላቅ ሀይማኖታዊ ስርዓት ይከበራል። ካህናት፣መዘምራን ሊቃውንት ሌሊቱን በማህሌት፣ጠዋት በቅዳሴ፣በወረብና፣በዝማሬ፣በስብከት ሊቃነ ጳጳሳት፣መነኮሳት፣ካህናት፣ዲያቆናትና ከዋክብተ ቤተክርስቲያን ምዕመናን በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ይከበራል።

የፃድቁ የአባታችን የተክለሀይማኖት በረከት በሁላችን ላይ ይደር፤ አገራችን ኢትዮጵያን ደግሞ ከክፉ ይጠብቃት፤ አሜን!!!
 

Thursday, May 16, 2013

ግንቦት 11


ግንቦት 11 በዚህች ቀን የዜማው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ወደ ብሔረ ሕያዋን የተሰወረበት ቀን ነው። ይህ ቅዱስ ከአባ ጌዴዎን ዘመዶች ወገን እርሱም በኢትዮጵያ አገር ከታነጹት አብያተ ክርስቲያናት ለምትቀድም ከአክሱም ካህናት ውስጥ ነው: እርሷም አስቀድሞ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት በውስጥዋ የተከበበ እና አምላክን በወለደች በእመቤታችን በከበረች ድንግል ማርያም ስም የከበረች ናት ::
የዚህ ቅዱስ አባት አዳም የእናቱም ስም ታውክሊያ ሲባሉ :በ512 ዓ ም በአክሱም ከተማ ተወለደ:: እናት እና አባቱም ልጃቸውን ለማስተማር ወደ ዘመዳቸው አባ ጌዴዎን ልከው እንዲማር አደረጉት : ይህም አባት አባ ጌዴዎን ትምህርትን ሊያስተምረው በጀመረ ግዜ መቀበልም ማጥናትም ተሳነው እስከ ብዙ ዘመንም መዝሙረ ዳዊትን ሲማር ኖረ ነገር ግን ከልቡ ማጥናትን እምቢ አለው:መምህሩም አብዝቶ ደበደበው ባሳመመውም ግዜ መታገስ ተሳነው ከአባቶቹ ቤትም ወቶ ዕብነ ሃኪም ወደተቀበረበት ገዳም ሄደ : በውስጡም የወርቅ የብር የልብስ መቀመጫዎች የተመሉ ናቸው: ከአንዲትም ዛፍ አጠገብ ደረሰ ከዚያም አረፈ ትልም ወደ ዛፏ ሲወጣ አየ :ወደ ዛፊቱም እኩሌታ ደርሶ ወደ ምድር ይወድቃል :ሁለተኛም ተመልሶ ወደ ላይ ይወጣል መጀመርያ ወደ ደረሰበት ሲደርስ ይወድቃል:ሲወጣ ሲወድቅ ብዙ ግዜ ያደርጋል : ወደ ሌላ ቦታም አይሄድም
ከዚህም በኋላ በብዙ ጥረት በብዙ ትጋት በብዙ ድካም በዚያ ከዛፏ ላይ ወጣ:ከዚያችም ከዛፏ ላይ ተቀምጦ በላ :ቅዱስ ያሬድም ወደዚያ ዛፍ ላይ ይወጣ ዘንድ እንደሚተጋ ብዙ ግዜም ከላይ ሳይደርስ ከመካከል እንደሚወድቅ ከዚያም በኋላ በጭንቅ ወደ አሰበው እንደደረሰ የፈለገውንም እንዳገኘ የትሉን ትጋት ባየ ግዜ ሰውነቱን ግርፋቱን እንደምን አትታገሺም ህማሙንስ እንደምን አትችይም አላት መታገስንስ አብዝተሽ ኖሮ ቢሆን እግዚአብሄር በገለጠልሽ ነበር ይንንም ብሎ አለቀሰ ወደ መምህሩ ወደ ጌዲዮን ተመለሰ አባት ሆይ ይቅር በለን እንደቀድሞ ንገረኝ አስተምረኝም አለው:መምህሩ ጌዲዮንም እንዳልከው ይሁን አለው 150ውን መዝሙረ ዳዊት:መሃልየ ነብያትን :መሃልየ መሃልይን :የእመቤታችን ድንግል ማርያምን ምስጋና ነገረው:81ዱ መጻህፍትን ትርጓሜ የሌሎች መጽሃፍትን ቁትር እና የመሳሰሉትን መጽሃፍተ ሊቃውንት ሁሉ በአንድ ቀን አጥንቶ ፈጸመ::
ከዚህ በኋላ በብዙ ለቅሶ ወደ እግዚአብሄር በለመነ ግዜ ልቡናው ብሩህ ሆኖለት በአጭር ግዜ የብሉይ እና የሃዲስ መጽሃፍትን ተምሮ ፈጸመና ዲቁና ተሾመ:በዚያም ወራት እንደዛሬ በከፍተኛ ቃል የመዝሙር ማህሌት የለም ነበር በትሁት እንጂ :: እግዚአብሄርም መታሰቢያ ሊያቆምለት በወደደ ግዜ ከኤዶም ገነት 3 አእዋፍን ላከለት እነርሱም በሰው አንደበት ተናግረውት ወደ እየሩሳሌም ሰማያዊት ከእነሱ ጋር አወጡት በዚያም 24ቱ ካህናተ ሰማይ የሚያመሰግኑበትን ማህሌት ተማረ::
ወደ አነዋወሩ ወደ ምድርም በተመለሰ ግዜ በአክሱም ዳር ወደ ከበረች ቤተ ክርስቲያን በ3 ሰዓት ገባ በታላቅም ቃል ሃሌ ሉያ ለአብ:ሃሌ ሉያ ለወልድ: ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ :የፅዮንም ደገኛዋ ሰማይን ፈጠረ ዳግመኛም እንዴት እንደሚሰራት የድንኳንን አሰራር ለሙሴ አሳየው አስተማረው አለ:: ይህቺም ምስጋና አርያም ብሎ ጠራት:የቃሉንም ድምጽ በሰሙ ግዜ ንጉሱም ንግስቲቱም ጳጳሱም ከካህናቱ ሁሉ ጋር የመንግስት ታላላቆች እና ህዝቡ ሁሉ ወደ እርሱ ሮጡ:ሲሰሙትም ዋሉ ከዚህም በኋላ ከአመት እስከ አመት በየክፍለ ዘመኑ በክረምት እና በበጋ:በመጸው እና በጸደይ:በአጽዋማት እና በባእላት :በሰንበታትም እንዲሁም በመላእክት በአል በነብያት እና በሃዋርያት በጻድቃን እና በሰማእታት በደናግልም በአል የሚሆን አድርጎ በሶስቱ ዜማው ሰራ :ይህውም ግዕዝ ዕዝል አራራይ ነው::
የሰው ንግግር የአእዋፍ የእንሥሳትና የአራዊት ጩሀት ከነዚህ ከሶስቱ ዜማ አይወጣም :በአንዲት እለትም ቅዱስ ያሬድ ከንጉስ ገበረመስቀል እግር በታች ቆሞ ሲዘምር ንጉሱም የያሬድን ድምጽ እያዳመጠ ልቡ ተመስጦ የብረት ዘንጉን ወይም መቋምያውን በያሬድ እግር ላይ ተከለው ከእርሱም ደምና ውሃ ፈሰሰ ያሬድም መሃሌቱን እስከሚፈጽም አልተሰማውም ነበር ንጉሱም አይቶ ደነገጠ በትሩንም ከእግሩ ላይ ነቀለ ስለፈሰሰው የደምህ ዋጋ የፈለከውን ለምነኝ ብሎ ለያሬድ ተናገረው ያሬድም ላትከለክለኝ ማልልኝ አለው ንጉስም በማለለት ግዜ ወደ ገዳም ሄጄ እመነኩስ ዘንድ አሰናብተኝ አለው ንጉሱም ሰምቶ ከመኳንንቱ ጋር እጅግ አዘነ ተከዘም እንዳይከለክለውም መሃላውን አሰበ እያዘነም አሰናበተው ከዚ በኋላም ቅዱስ ያሬድ ወደ በተክርስቲያን ገብቶ በታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ ፈጽሞ የከበርሽ እና የተመሰገንሽ ከፍ ከፍ ያልሽ የብርሃን መውጫ የህይወት ማዕረግ የሆንሽ የሚለውን ምስጋና (አንቀጸ ብርሃን) እስከመጨረሻ በተናገረ ግዜ ክንድ ያህል ከምድር ከፍ ከፍ አለ::
ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን ሃገር ሄዶ በጾም በጸሎት ተወስኖ ስጋውን እጅግ እያደከመ ኖሮ ገድሉን በዚያ ፈጸመ እግዚአብሄር ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው ከዚ በኋላ ግንቦት 11 ቀን የተሰወረበት ቦታ በሰሜን ጠለምት ደብረ ሐዊ በተባለው ተራራ ነው፤ በዚህ ቦታ በስሙ የታነጸለት አስደናቂ ገዳም አለው፤ በመዲናችን አዲስ አበባም መስቀል ፍላዎር አካባቢ ግሩም ቤተክርስቲያን አለው ዛሬ ታቦተ ህጉ ውጥቶ በደማቁ ተከብሮ. በአንድ ወቅት እመቤ...ታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አባ ሕርያቆስን ከብሕንሳ፤ ቅዱስ ኤፍሬምን ደግሞ ከሶርያ ይዛ ለቅዱስ ያሬድ አክሱም ላይ ተገለጸችለት እንዲህም አለቻቸው በሉ አንተ ቅዳሴዬን አንተ ደግሞ ውዳሴዬን ንገሩትና በዜማ ይድረስው አለቻቸው፤ እነርሱም ነገሩት እርሱም የሚጣፍጥ ዜማ ደረሰ፤ዛሬም ድረስ ጠዋትና ማታ ቤተክርስቲያን ድምጿን ከፍ አድርጋ ይምታሰማው እነዚህ ሶስት ግሩማን አባቶች የተባበሩበትን ምስጋና ነው። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን። የአባታችን የአምሳለ ሱራፌል የሊቁ ማህሌታይ የቅዱስ ያሬድ ጸሎቱ በረከቱ ረድኤቱ በኛ በህዝበ ክርስቲያኑ ላይ በሃገራችን በኢትዮጵያ ላይ ለዘላለም በእውነት ይደርብን !!!!!አሜን